Thursday, January 30, 2014

ድንበር የማይቀዘቅዝ ትኩስ ደም ነው። የኢትዮጵያ እና የሱዳን የድንበር ውል ዝርዝር ጉዳይ ከሕዝብ ሊደበቅ አይገባም።

አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ከሁለት ሳምንት በፊት በሱዳን ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወቃል።በእዚህ ጉብኝት ላይ አቶ ኃይለማርያም ''እጅግ ለም የሆነ የኢትዮጵያ መሬት ለሱዳን ለመስጠት ተስማምተዋል አሁን የቀረው ችካል ማስቀመጥ ነው'' የሚል ዜና በኢሳት ሲዘገብ ቀናት ነጉደዋል።ትናንት ታህሳስ 16/2006 ኢሳት በአለም አቀፍ ራድዮ ስርጭቱ ላይ የኢትዮጵያ የድንበር ጉዳይ የሚከታተሉ 'የኢትዮጵያ ድንበር ኮሚቴ' የተሰኘ ኮሚቴ አባላትን በቃለ መጠይቅ አቅርቦ ነበር።እንደ ኮሚቴው ገለፃ ከሆነ አሁን መንግስት ለሱዳን መንግስት ለመስጠት መስማማቱ የሚነገረው መሬት ከቀድሞ ጀምሮ በኢትዮጵያ ይዞታ ላይ ያለ አሁንም ገበሬዎች የሚገኙበት እና ባዶው ቦታን ጨምሮ በትንሹ ካለምንም ማጋነን 15 ሚልዮን ሕዝብ አስፍሮ መመገብ የሚችል ቦታ ነው።15 ሚልዮን ልብ በሉ! በሕዝብ ስም የሚደረግ ማንኛውም ውል ከህዝብ ሊደበቅ አይገባውም።ድንበር የማይቀዘቅዝ ትኩስ ደም ነው።ይህ ደም ደግሞ ለዘመናት የኢትዮጵያ አባቶች እና እናቶች ያፈሰሱት ደም ነው።ማንም መንግስት በሕዝብ ደም ሊደራደርም ሆነ ድንበር ሊሰጥ አይችልም።ለአንድ 'ኩርማ' መሬት ለባድሜ በሺዎች ያረገፈ ጦርነት ክተት ያወጀ መንግስት 15 ሚልዮን ሕዝብ የሚያሰፍር መሬት ለሱዳን ስለመስጠቱም ሆነ ስለ ውሉ ጉዳይ ዝርዝር ማብራርያ ለሕዝብ ሊሰጥ ይገባል።በትዊተር በብዛት የሚታዩት ባለስልጣናት ከሌላው ዜና ይልቅ የእዚህ አይነቱን ቅድምያ ሊሰጡት በተገባ ነበር።ድንበር የማይቀዘቅዝ ትኩስ ደም ነው። ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG

No comments:

Post a Comment