Tuesday, January 28, 2014

በ6 የሱዳን ወጣቶች የተደፈረችው ኢትዮጵያዊት በእስር ላይ እንደምትገኝ ታወቀ



ጥር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ቀድሪያ እንድሪስ የተባለች ኢትዮጵያዊት ወጣት በ6 የሱዳን ወጣቶች እጅግ አሰቃቂ በሆነ መንገድ ስትደፈር የሚያሳይ ቪዲዮ ኢሳት የደረሰው ሲሆን ፣ ካርቱም የሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ የዲያስፖራ ክፍል ሃላፊ የሆኑት አቶ አረጋ ልጂቷ መደፈሩዋን አምነው ተጨማሪ መረጃ ለመስጠት ግን ከፍተኛ ባለስልጣኖች መፍቀድ አለባቸው በሚል ዝርዝር ጥያቄዎችን ለመመለስ ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።

ጥቅምት ወር አካባቢ ቤት ለመከራየት በአካባቢው የነበሩትን ወጣቶች የጠየቀችው ኢትዮጵያዊት፣ ወጣቶችም ” እኛ የሚከራይ ቤት እናሳይሻለን” ብለው በመውሰድ በአሰቃቂ ሁኔታ እየደፈሩ በእርቃኑ ላይ የተለያዩ አስጸያፊ ስራዎችን እየሰሩ በቪዲዮ እየቀረጹ ተጫውተውባታል።

ለራሱ ምስል የተጠነቀቀው የሱዳን መንግስት ቀድሪያንና ሞርጋን ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ አስሮአት እንደሚገኝ ኢሳት ከኢምባሲው የውስጥ ምንጮች መረጃ የደረሰው ሲሆን፣ የኢምባሲው የዲያስፖራ ሃላፊ ግን ልጅቱ በጥሩ ሁኔታ ላይ ትገኛለች ብሎአል። የሱዳን ፍርድ ቤት ድርጊቱ ሲፈጸም በወቅቱ ለምን ሪፖርት አላደረግሽም በሚል ወጣቷንም ተጠያቂ ለማድረግና የአገሪቱን መንግስት ከተጠያቂነት ለማውጣት እንቅስቃሴ መጀመሩን የውስጥ ምንጮች የገለጹ ሲሆን፣ ወጣቷ በበኩሏ ” መረጃውን የምታወጪው ከሆነ እንገድልሻለን ስለተባለች በፍርሃት በወቅቱ ሪፖርት ለማድረግ እንዳልቻለች ገልጻለች።” በአሁኑ ጊዜ ወጣቷ ከማንኛውም ሰው ጋር እንዳትገናኝ በመደረጓ ኢሳት ለማነጋገር ሳይችል ቀርቷል። ወጣቷን በእስር ቤት ለማነጋገር የሚፈልጉ ሰዎች ልዩ ወረቀት ከኢትዮጵያ ኤምባሲ ማምጣት የሚኖርባቸው ሲሆን፣ አንዳንድ የሰብአዊ መብት ተቆርቋሪ ድርጅት ወጣቷን ለመጠየቅ ፈልጎ በወረቀት ክልከላ ምክንያት ሳይችል ቀርቷል።

በወንጀል ከሚፈለጉት ወረበሎች መካከል የተወሰኑት የታሰሩ ቢሆንም ሌሎች ደፋሪዎች ግን እስካሁን አለመታሰራቸው ታውቋል። በሱዳን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጉዳዩን እየተከታተልኩት ነው ቢልም እስካሁን በእስር ላይ የምትገኘዋን ወጣት ለማስፈታት አልቻለም።

ወጣቷ በአሁኑ ጊዜ ነፍሰጡር ስትሆን፣ የእርግዝናዋ ምክንያት ከመደፈሩዋ ጋር የተያያዘ ይሁን አይሁን የታወቀ ነገር የለም

No comments:

Post a Comment