Tuesday, January 21, 2014

የወያኔ ነፍስ በበረከት ስምዖን በኩል ስትቃዥ


ነፃነት ዘለቀ (አዲስ አበባ)
Bereket Simon, Woyanne propaganda chiefአንደኛው መስከረም ጠብቶ ሌላኛው መስከረም እስኪጠባ ድረስ ባሉት የ365.25 ቀናት ውስጥ ስንት ጉድ መስማት እንዳለብን የሚጠቁም አሃዛዊ መረጃ ሊኖር እንደማይችል መቼም ግልጥ ነው፤ ነገር ግን የዘመናችን ኢትዮጵያ የታሪክ ጎርፍ ያመጣብን ከወያኔና መሰሎቹ በስተቀር ሌሎቻችን ያልጠበቅነው ዱብዕዳ ክስተት ምሥጋና ይንሳውና በዬቀኑ የማንሰማውና የማናየው ዕንቆቅልሽ እንዳይኖረን ሆነናል፡፡ በዚህ መልክ በተለይ ባለፉት 22.8 ዓመታት ውስጥ የታዘብነው የታሪክ ምፀትና ወኔያዊ የውሸት ስንክሳር በረጂሙ ታሪካችን ታይቶም ሆነ ተሰምቶ እንደማያውቅ ማንም ጤናማ ኅሊና ያለው ዜጋ የሚመሰክረው ይመስለኛል፡፡ ለዛሬ አንዱን የወያኔ ነጭ ውሸት እንመለከታለን፡፡
በነገራችን ላይ ወያኔና እውነት ዐይንና ናጫ መሆናቸውን የማይረዳ ወገን እንደማይኖር እገምታለሁ፡፡ የወያኔን ተፈጥሮ ወያኔ ራሱን ጨምሮ ሁሉም ያውቃል፤ የወያኔ እውነት፣ የእውነት ግልባጭ የሆነችው ሀሰት ናት፡፡ ለወያኔ ውሸት ማለት እውነት ናት፡፡ ለወያኔ እንደእውነት የሚመርና የሚያቅር ነገር የለም፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ለወያኔ እንደሀሰት የሚጣፍጥ ምንም ነገር የለም፡፡ ወያኔና እውነት በሂሳባዊ አገላለጽ ‘asymptote’ ናቸው – መቼም ሊገናኙ የማይችሉ ተጻራሪ ኑባሬያት በመሆናቸው፡፡ ወያኔ የሀሰት የህግ ባል ነው፤ የሚለያዩት ወይም የሚፋቱት ከሁለት አንድኛቸው ወይም ሁለቱም ሲሞቱ ብቻ ነው፡፡ ሀሰት ግን እስከዓለም ፍጻሜ ስለምትኖር ወያኔ ካልጠፋ ከውሸታምነቱና ከሀገር አጥፊነቱ ተፈጥሯዊ ባሕርይው ሊፋታ አይቻለውም፡፡ ታሪክ ግን ሥራውን የማይረሣ ቆፍጣና ገበሬ በመሆኑ ጊዜውን ጠብቆ እነዚህን ጉግማንጉጎች ወደማይቀረው መቃብራቸው እንደሚሰዳቸው የታመነ ነውና መፍረስ የጀመረው የበሰበሰ ሥርዓታቸው ከነሰንኮፉ ተገርስሶ ሀገራችን በቅርቡ ነጻ እንደምትወጣ በሙሉ ልብ አምናለሁ፡፡ በዚህች መንደርደሪያ ወደሰሞነኛው የበረከት ስምዖን ውሽከታ እንለፍ፡፡
“የኢትዮጵያ አርሶ አደር እስካሁን በተደረገለት ሥራ በሚገባ የረካ ስለሆነ ‹መንግሥት ሰልፍ ውጣ ቢለው ይወጣል፤ መንግሥት ተኛ ቢለው ይተኛል፤ ግፍ ብንፈጽም እንኳን አርሶ አደሩ ይህንን መንግሥት ይሸከመዋል እንጂ ምንም አይለውም፡፡”
ይህን የብፃይ በረከት ንግግር በዓይነቱ ልዩ የሚያደርገው የተባበሩት መንግሥታት ሰሞኑን ባወጣው አንድ ጥናታዊ ዘገባ ላይ በአፍሪካ ፈጣን ዕድገት ከሚያሳዩ አሥር ሀገሮች ውስጥ ኢትዮጵያ አለመካተቷና በተጓዳኝም ይህቺው ኢትዮጵያ – ይህቺው ወያኔን በጫንቃዋ እንደምትሸከም በረከት አፉን ሞልቶ የመሰከረላት ጉደኛዋ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ጠኔ ጓዙን ጠቅልሎ ከመሸገባቸው አምስት የመጨረሻ ድሃ ሀገራት ውስጥ መመደቧ ነው – (በረከት ይህን ሪፖርት ሳያነብ መሆን አለበት ያን በህልሙ የደረሰውን ጅሎችን የማሞኛ ተምኔታዊ(utopian) ቧልታይና ድንቃይ ድርሰቱን የደሰኮረው!)፡፡ በነገራችን ላይ በአምባገነንነትና በድህነት በወያኔ መንግሥት ሳይቀር የምትታማዋ ኤርትራ በነዚህ ዘገባዎች አልተካተተችም(እንዲያውም ዘገባው ኢትዮጵያን ይግረማት ብሎ ከአሥሩ በፍጥነት እያደጉ ካሉ የአፍሪካ ሀገራት ውስጥ አንዷ ኤርትራ እንደሆነች የገለጠ መሰለኝ)፡፡ ኢትዮጵያ ቻድን ብቻ በልጣ በአፍሪካ በርሀብተኝነት ሁለተኛ ስትወጣ ኤርትራ ከአምስቱ የባሰባቸው ሀገራት ውስጥ አልገባችም፡፡ የርሷ መግባት አለመግባት የኔ ራስ ምታት አይደለም፡፡ ነገር ግን ይህች በማዕቀብና በልዩ ልዩ የማሰቃያ መንገዶች የተወጠረች የቀድሞ የኢትዮጵያ ግዛት ከኢትዮጵያ የተሻለች መሆንዋን በመረጃ በተደገፈ ዘገባ የሚረዳ ጤናማ ሰው የወያኔን ሚዲያ አስችሎት እንዴት ሊከታተል እንደሚችል ይታያችሁ፡፡ ክርስቶስ ‹አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ› አለ፡፡ ወያኔም ይህችን የክርስቶስ አባባል ቀምቶ በማንሻፈፍ ‹አፌን በሀሰትና ዕብለት እከፍታለሁ› አለና ነጋ ጠባ የማያቅመን የሀሰት ወሬ የማይነጥፍበት አስገራሚ ፍጡር ሆነ፡፡
መዋሸት የማይሰለቸው ‹ልማታዊው መንግሥታችን› በሚዲያው የሚያሳየን ኢትዮጵያና እኛ በግልጥ የምናያት ኢትዮጵያ ተለያይተውብን ተቸግረናል፡፡ እነሱ ‹ኢትዮጵያ በልማት ጎዳና እየተመመች ናት፤ የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ራዕይ ለማሳካት በየፈርጁ የምናካሂደው የልማት ግስጋሴ ግቡን እየመታ ነው፤ የኢትዮጵያ ልማት ማንም በማይወዳደረው ሁኔታ ወደፊት እየተምዘገዘገ ነው፡፡ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓታችንን በማይነቃነቅ ዓለት ላይ ገምብተናል፤ የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች መብት ሳይሸራረፍ የተከበረባትና በሕዝቦች መፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ አንድነት እውን የሆነባት አዲሲቷ ኢትዮጵያ ተፈጥራለች፡፡ አሁን ዋናው ጠላታችን ድህነት ነው፡፡ እሱንም እየተዋጋነው ነው…›እያሉ በቲቪያቸው እያላገጡብን ነው – ድህነትን ለመዋጋትና ለማሸነፍ ደግሞ ስንት አሥር ዓመቶች እንደሚያስፈልጉን እነሱው ናቸው የሚያውቁት፤ ለመልካም አስተዳደር እኮ አንድ የመኸር ወቅትም ትልቅ ጊዜ ነው – እንኳንስ 23 ዓመታት፡፡ ወያኔዎች ግን በድህነት ላይ እንደዛቱና ወደታሪክነት እንለውጠዋለን እንዳሉ ሦስት ዐሠርት ዓመታትን ሊደፍኑ ነው፤ አያፍሩም፡፡ በማከያው ግን ዕድሜ ለወያኔው ጉጅሌ በምግብ “ሞልቶ መትረፍረፍ” ከአፍሪካ አንዲት ሀገር ብቻ በልጠን በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቻችን የተንጣለሉ የአስፋልት መንገዶችንና በአብዛኛው የትግራይ ተወላጆች የሆኑ ኢንቬስተሮች የገነቧቸውን ሕንፃዎች “እየተመገቡና እየጠገቡ” መሆናቸው እየተነገረን ነው፤ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ያጡ የነጡ ዜጎቻችንም ከዬቆሻሻ ገንዳዎች የሀብታም ፍርፋሪና የሙዝ ልጣጭ ለመሻማት ቀን ከሌሊት ሲራኮቱ ይታያሉ፡፡ የወያኔ ዕድገት ይህ ነው፡፡ የወያኔ ‹ልማታዊ ጋዜጠኞች›ም በበኩላቸው የሕዝቡን ሰቆቃ እንዳይመለከቱና እንዳይዘግቡ እንደአቃቂ ፈረስ ዐይኖቻቸውን በወያኔ ተከልለው በብድርና በዕርዳታ በተገነቡ መንገዶችና ድልድዮች ላይ ካሜራዎቻቸውን በመደቀን ሌት ከቀን በተመሳሳይ ዜናዎችና ሀተታዎች ማደንቆራቸውን ተያይዘውታል፡፡ እኛን እሚያሳክከን ሆዳችን ላይ እነሱ እሚያኩልን እግራችንን፡፡ የሚገርሙ ጋዜጠኞችና የሚገርም የማፊያዎች መንግሥት፡፡
ወደበረከት ንግግር እንመለስ፡፡ እንደእውነቱ በረከት ከፍ ሲል የተናገረውን ነገር ለምን እንደተናገረው አልገባኝም፡፡ ምን ማለት እንደፈለገ ለመረዳት አስተርጓሚ ሳያስፈልግ አይቀርም፡፡  አማርኛ ቋንቋን አውቃለሁ ብዬ ደረቴን ነፍቼ እናገራለሁ፡፡ ነገር ግን ይህንን የበረከትን ንግግር እንደመሰለኝ ተርጉሜ እንዲገባኝ ጥረት አደረግሁ እንጂ በቅጡ ልረዳው አልተቻለኝም፤ እርሱም ቢሆን ጎንደር ውስጥ ብዙ ዓመታትን ስለኖረ አማርኛን ከአፍ መፍቻው ባልተናነሰ ያውቃል ብዬ እገምታለሁና ‹ምን ማለት እንደፈለገ ሳይገባው እንዲህ ያለ የተወነዣበረ ንግግር በአደባባይ ተናግሮ የሰው መሣቂያ ለመሆን አይደፍርም› ብዬ ለማመንም በጣም ተቸገርኩ፡፡
ይህን ንግግር በብዙ መልኩ መገንዘብ እንደሚቻል አምናለሁ፤ በአማርኛው “የጊዮርጊስን ግብር የበላ ሳይነኩት ይለፈልፋል” ወይም በሌላ ፈሊጣዊ አገላለጽ “የምላስ ወለምታ” የምንላቸው ምሥል ከሳች አባባሎች አሉ፡፡ በፈረንጅኛው “Fruedian slip” የሚባል በሥነ ልቦና የትምህርት ዘርፍ የሚጠቀስ ሐረግ አለ፡፡ ይህ ሰው የተናገረውን ከነዚህ ጽንሰ ሃሳባዊ ዕይታዎች አንጻር ብንመለከተው ወያኔ ከመጃጀቱና በወንጀል ድርጊቶች ከመጨመላለቁ የተነሣ ነፍሱ እየቃዠች መሆኗን መረዳት አያዳግተንም፡፡ አለበለዚያ ግፍ በመሥራት ላይ የቆመ የወሮበሎች መንግሥት  “ገበሬው ግፍ ብንፈጽምበትም ይሸከመናል” ብሎ መናገሩ ምን ትርጉም ይኖረዋል? አንድ ጤነኛ ሰው ከመሬት ተነስቶ “በጥፊ ባጮልህና ዐይንህን በጉጠት ባወጣውም እንደማትቀየመኝ አውቃለሁ! ከኔ በበለጠ ሊያሰቃይህ የሚችል ወገን እንደሌለ ስለማውቅ ለስቃይ ለስቃይ እኔው እሻልሃለሁና ምርጫህ እኔው ብቻ ልሆን ይገባኛል” ብሎ እንዴት ሊናገር ይችላል? እንዲህ ብሎ የሚናገር ሰው ካለ ደግሞ እንደበረከት የለዬለት በሽተኛ እንጂ ጤናማ ሰው ሊሆን አይችልም፡፡ ከወፈፌና በሽተኞች ንግግር ይሠውረን፡፡ “ዱባ ካላበደ ቅል አይጥልም” አሉ? የሚገርም በረከት ነው የሆነብኝ እባካችሁን፡፡
ይህን ንግግር በቁሙ መረዳት እንደሚቻለው በረከት ማለት ቅል ራስና እሚናገረውን እንኳን የማያውቅ ገልቱ ሰው ነው፡፡ ለመደዴ የቃላት አጠቃቀሜ ይቅርታ ይደረግልኝና እንደዚህ ያለ ድፍን ቅልና ባልጩት ራስ የኢትዮጵያ አንዱ ባለሥልጣን እንደነበረ በነገው የታሪክ መዝገባችን ሠፍሮ ሲታይ በቀጣይ ትውልዶቻችን ዘንድ በእጅጉ ከምናፍርባቸው የታሪክ ስብራቶቻችን መካከል አንዱና ትልቁ ነው፡፡ ሰው ምን ቢጃጃል እንደዚህ አይናገርም ወይም አይጽፍም፤ አለበለዚያም አብዷል ማለት ነው፡፡ “አፍ ሲከፈት ጭንቅላት ይታያል” የሚባለው እኮ እንደዚህ ያለ በደናቁርት አስተሳሰብ የተለወሰ የአነጋገር ጭቅቅት ሲያጋጥም ነው፡፡ ተመልከቱልኝ፡-
“መንግሥት ሠልፍ ውጣ ቢለው ይወጣል፤ ተኛ ቢለው ይተኛል፡፡”
ምን ማለት ነው? ገበሬውን በማስገደድም ይሁን በማታለል ሠልፍ ማስወጣት ይቻል ይሆናል፡፡ ነገር ግን እንዴት ነው እንደሕጻን ልጅ ገበሬውን በትዕዛዝ አባብሎ ማስተኛት የሚቻለው? ምን ዓይነት ዕብሪትና ትምክህት ነው? ምን ዓይነት የድንቁርና አነጋገር ነው? ለነገሩ ወያኔዎች ከአለቃቸው ከመለስ ጀምሮ ለአነጋገራቸው ደንታ የላቸውም፤ የሚያስቡት እንደጤናማ ሰው በጭንቅላት ሣይሆን እንደ አውሬ በጡንቻ ሣይሆን አይቀርም – አውሬ በጡንቻው ካሰበ፡፡ ሀገር፣ ታሪክና ወገን አለን ብለው ራሳቸው ስለራሳቸው የሚያምኑ አይደሉም፤ ባህል የላቸውም፤ ሞራል ወይም ‘ethical values’  ብሎ ነገር አያውቁም፤ ምናልባት ከሴቴኒዝም በስተቀር ሁነኛ ሃይማኖትም ያላቸው አይመስሉም (ለዚህም ይመስላል ወንጀለኝነት የሚያዝናናቸውና በሰዎች ስቃይ የሚደሰቱት)፤ በትውፊትና በወግ ልማድ አያምኑም፤ ባጭሩ ወፍዘራሽ የመርገምት ውጤቶች ናቸው፡፡ ከሁሉም ነገር የወጡና ከዜሮ መጀመር የሚወዱ በፈረንጅኛው አገላለጽ nihilists ናቸው – hedonist የሚል ምርቃትም ማከል ይቻላል፡፡ ታሪክን ማጥፋትና ነባር ባህልን ማውደም ያረካቸዋልና፡፡
ወያኔዎች ማለት ባጭሩ ማሊ በምትባለዋ አፍሪካዊት ሀገር ‹አዛዋድ› በሚል ራሳቸው በፈጠሩት አዲስ ግዛት ውስጥ ፈረንሣይ ድምጥማጣቸውን እስክታጠፋቸው ድረስ ለተወሰነ ጊዜ በሼሪዓ ህግ የሚተዳደር እስላማዊ መንግሥት መሥርተው እንደነበሩት የቱዋሬግ አማፅያን  የሚመሰሉ ናቸው – ወያኔዎች እንደሶማሊያው አልሻባብ ዓይነትም ናቸው – ነገር ግን መንግሥት ስለያዙ ደፍሮ በአሸባሪነት የፈረጃቸው ዓለም አቀፍ ኃይል ሊገኝ አልቻለም፡፡ ለነገሩ ወያኔዎች ሀገራዊ አጀንዳ ስለሌላቸውና የማንንም ፀረ-ኢትዮጵያ የሆነ አጀንዳ አንከርፍፈው በተባባሪነት ስለሚጓዙ ለዓለም አቀፍ ታዋቂ ኃይሎች እስትራቴጃዊ ጠቀሜታ እስከሰጡ ድረስ በአጋርነት የሚያስጠጋቸውና ሙሉ ድጋፍ የሚሰጣቸው አያጡም(ኢትዮጵያውያንን ለጊዜውም ቢሆን እያስቸገረን ያለው ይህን መሰሉ የወያኔ እስስታዊ ተፈጥሮ ነው)፡፡ እነዚያ የአልቃኢዳ የአፍሪካ ክንፍ የሆኑ አማጽያን በቲምቡክቱ ውስጥ የነበሩ ዕድሜያቸው በሺዎች ዓመታት የሚገመት የታሪክ ቅርሶችን በዶማና አካፋ እንዲሁም በግሬደር በአጭር ጊዜ የሥልጣን ቆይታቸው ውስጥ ድራሻቸውን ማጥፋታቸውን የቅርብ ጊዜ ትዝታ በመሆኑ ከዐይነ ልቦናችን ገና አልተሰወረም፡፡ ወያኔዎችም እያዋዙ በእስከዛሬው የኃይል አገዛዛቸው እጅግ በርካታ የኢትዮጵያ ቅርሶችንና ታሪኮችን አጥፍተዋል – ከሁሉም የሚብስ ጥፋታቸው ግን ከቁሣዊው ይልቅ ሥነ ልቦናዊውና  ኅሊናዊ ወመንፈሣዊው አጠቃላይ ውድመት የበለጠ ኪሣራ ያደረሰብንና ለማገገምም ብዙ ጊዜ የሚወስድብን ከባዱ ጥፋት ይመስለኛል፡፡ እነዚህ ናቸው እንግዲህ ጅብ እማያውቁት ሀገር ሄዶ ቁርበት አንጥፉልኝ እንደሚል በምናውቃቸው ምሥኪን ዜጎች መሀል ሆነው ገበሬው የነሱ እንደሆነ የሚሰብኩን፡፡ ለነገሩ ጅብ እንኳን በማያውቁት ሀገር ነበር ተናገረው የተባለውን የተናገረው፡፡ ወያኔዎች ግን ዐይናቸውን በጨው አጥበው እኛው ፊት ሸፍጣቸውንና የሀሰት ቱሪናፋቸውን ካለተቀናቃኝ ለብቻቸው በተቆጣጠሩት ሚዲያቸው ያናፉብናል፡፡
የኢትዮጵያ ገበሬ ኑሮው ምን ይመስላል?
በአሁኑ ወቅት በወያኔ ሥርዓት እንደገበሬው የሚማረር የለም፡፡ የወያኔን የውሸት ፕሮፓጋንዳ ለወያኔና ወያኔያውያን ትተን እውነቱን ብቻ እናውራ ካልን የገበሬው ኑሮም ሆነ የአጠቃላዩ የሀገሪቱ ሕዝብ ሕይወት ያሳዝናል ብቻ ሳይሆን ያስለቅሳል፡፡ እኔ ይህን መልእክት የምጽፍላችሁ ዜጋ በሀገር ቤት የምኖርና አልፎ አልፎ ወደገጠር ለሥራ ጉዳይ ወጣ የምል በዚያም ምክንያት የብዙ አካባቢዎችን ነዋሪዎች ሰቆቃና የዕለት ከለት ውጣ ውረድ የምታዘብ ሰው ነኝ፡፡ ስለዚህም የምለው ነገር በስማ በለው የተገኘ ሳይሆን በራሴም ሕይወት እየደረሰ ያለ እውነተኛ ሰቆቃ መሆኑን ላስታውስ እፈልጋለሁ፡፡ የገበሬው ኑሮ ከእኛ ከከተሜዎቹ የባሰ እንጂ የተሻለ እንዳልሆነ በውነት እመሰክራለሁ፡፡
የአንድ አምባገነን መንግሥት ትልቁ ሕዝብን የመግዣ መሣሪያ ሌላ ሳይሆን በማይምነትና በድንቁርና ሸብቦ በማስፈራራትና በማስራብ አንቀጥቅጦ ወደተናጋሪ እንስሳነት መለወጥ ነው፡፡ ወያኔም እያደረገ ያለው ይህንኑ ነው፡፡ በየትኛውም የኢትዮጵያ አካባቢ ብትሄዱ ለይስሙላ ትምህርት ቤቶች ይሠሩ እንጂ ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት ባለመኖሩ መማር ካለመማር የሚለይበትን መሠረታዊ ነጥብ ፈልጋችሁ ልታገኙ አትችሉም፡፡ በመሆኑም ገበሬው ከትምህርት ርቋል፤ የጨለማ አዘቅት ውስጥም ከገባ ቆይቷል፡፡ በማይምነት አለንጋ እየተገረፈ፣ በብጥቅጣቂ እርሻ ላይ በሚዘራት አነስተኛ ሰብል እየተሰቃዬ፣ ከዚያችም ሰብል ላይ ከፍተኛ ግብር እንዲከፍል እየተገደደና ከብቱንና ንብረቱን ሸጦ ግብር እንዲያስገባ እየተጠየቀ የሚገኝ ገበሬ ወያኔን ጣዕረሞት ሲይዘው “በፍቅርና በትግስት ይሸከመዋል” ሳይሆን “የወያኔን ሬሣ ተሸክሞ ወደመቃብሩ ይሸኘዋል” ቢባል ነው ትክክለኛው፡፡  ገበሬው በቀን አንድ ጊዜም የሚቀምሰው በሌለበት ሁኔታ፣ ገበሬው የልጁን ወስፋት የሚሸነግልበት አንዳችም እህልና ጥሪት አልባ በሆነበት ሁኔታ፣ ገበሬው ከገጠር እየፈለሰ ወደከተሞች በመግባት ለወያኔ ሕንጻና ፋብሪካ ግንባታዎች የቀን ሠራተኛ እየሆነ ባለበት ሁኔታ፣ ገበሬው ልጆቹ ወደዐረብ ሀገር እየተሰደዱ ለዐረብ ጀማላ የሠይፍ እራትና የአስገድዶ መድፈር ሲሳይ እየሆኑ ባሉበት ሁኔታ፣ ገበሬው በማዳበሪያ ዕዳ የስንግ ተይዞ ኤሎሄ እያለ በሚገኝበት ሁኔታ፣ ገበሬው በአድሎኣዊ የመሬት ሥሪት ምክንያት መድሎ እየተሠራበት ማለፊያው የውሃ መሬት ለካድሬዎችና ለወያኔዎች እየተሰጠ ጭንጫውና መናኛው መሬት ግን ለድሃ ገበሬ እየተሸነሸነ ባለበት ሁኔታ፣ገበሬው ከማሳውና ከመኖሪያው እየተፈናቀለ መሬቱ በልማት ስም ለወያኔ ከበርቴዎች እየተቃረጠ ባለበት ሁኔታ፣ አህያ የተጫነችውን እንደማትበላ ሁሉ ገበሬውም ያመረተውን ምርት ለዕዳ ክፍያ ሲል ለጠገቡ የወያኔ ‹ልማታዊ ባለሀብቶች› በርካሽ እንዲሸጥና ጨርቁ በላዩ ላይ አልቆ በባዶ እግሩ እየሄደ በእሾህና በእንቅፋት አሣሩን እንዲበላ ተፈርዶበት ባለበት ሁኔታ፣ … በረከት የተናገረውን መስማት በርግጥም ተዓምር እንጂ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል? በቀደመው ዘመን “እስመ አልቦ ነገር ዘይሰአኖ ለእግዚአብሔር” ነበር ሲባል እምንሰማ፡፡ አሁን ደግሞ “እስመአልቦ ነገር ዘይሰኣኖ ለወያኔ”ብንል እንሳሳት ይሆን? ወያኔ ጥቁሩን ነጭ፣ ነጩን ጥቁር፤ ልቅሶን ሠርግ፣ መርዶን ብሥራት ማድረግ የሚችል ልዩ ምትሃት ያለውና በአፍ ጤፍ የሚቆላ ፍጡር ነው፡፡ ወያኔን ለሚያውቅ የወያኔ ዲስኩርና ፕሮፓጋንዳ  ችግር የለውም – በወያኔ ፕሮፓጋንዳ የሚጃጃል ወያኔን የማያውቅ ወይም ማወቅ የማይፈልግ ብቻ ነው፡፡ ‹ብታምኑም ባታምኑም የኢትዮጵያ ሕዝብ ወያኔን ከእግር እስከራሱ ጠንቅቆ ያውቀዋል!›፡፡ እናም በተለይ በአሁኑ ወቅት ወያኔ ማንንም ሊያታልል በማይችልበት ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ሞቶ በሞቶ እርግጠኛ ሆኜ እናገራችኋለሁኝ፡፡
እናም ወያኔ ስለገበሬው የሚያወራውና እኛ ስለገበሬው የምናውኧው፣ ገበሬውም ስለወያኔ የሚለውና ስለራሱም ከራሱ ኑሮ የሚስተዋለው ለዬቅል መሆናቸውን ልብ ማለት ይገባል፡፡ ‹ይሉሽን በሰማሽ ገበያ ባልወጣሽ› ይባላል፡፡ በረከት የሚናገረው ለሌሎች ብቻም ሳይሆን ለራሱም ሀሰት መሆኑን ማንም አያጣውም፡፡ በረከትን በማታው ‹ክብ ጠረጴዛ› አግኝተን “ምነው ወዲ ስምዖን፣ እንደዚያ ያለ ነጭ ውሸት ማናፈስ ደግ ነው እንዴ ? ለመሆኑ አንተስ ታምንበታለህ? ኅሊናስ የሚባል ነገር የለ(ህ)ም እንዴ?” ብንለው መልሱ ቀላል ነው፡፡ “ወንድሜ፣ በፖለቲካ ኅሊና ብሎ ነገር የለም፡፡ ዋናው ማምለጥ ነው፡፡ የምታደርገውን አድርገህ፣ የምትናገረውን ተናግረህ በፊትህ ከተደቀነብህ ችግር ማፈትለክ እንጂ ስለምትናገረው ነገር እውነትነት ከተጨነቅህ ፖለቲካ ውስጥ ቀድሞውን መግባት የለብህም፡፡ በተለይ እንደኛ ዓይነቱን ችግር ለጠላትም አይስጥ ወንድሜ፡፡ የገባንበት አጣብቂኝ በቀላሉ የሚወጡት አይደለም፡፡ መጥኖ መደቆስ አስቀድሞ ነበር ወዳጄ፡፡ በደም ጨቅይተናል፤ በሙስና በክተናል፤ በዘረኝነቱም ረገድ ያጠፋነውን ጥፋትም ቆም ብለው ሲያስተነትኑት የአንጎልን ሚዛን የሚያዛባና የሚያሳብድ ነው፤ ወደትግል ከገባንበት ጊዜ ጀምሮ የገደልነውና ለስደትና ለእሥራት የዳረግነው ዜጋ የኅሊና ዕረፍት እያሳጣ መቆሚያ መቀመጫ ያሳጣናል፤ ለዚህም ነው ብዙዎቻችን ቢሯችን ውስጥ ሣይቀር በብርጭቆ ውስጥ መደበቅን የምንመርጠው፡፡ ሰው ወዶና ፈቅዶ ጉበቱን በመጠጥ ቦጫጭቆ ሞትን በራሱ አይጋብዝም፡፡ ታዲያ አሁን ምን እናድርግ? ነገር የተበላሸው ዱሮ ነው፤ አሁን ሁሉም ነገር ጠርዝ ከለቀቀ በኋላ ከመዋሸትና ከማምታታት ውጪ ምን አማራጭ አለን? አንድ ነገር ሲገቡበት ቀላል ነው፤ ለመውጣት ግን ከባድ ነው፡፡ የኛ ወደዚህ ሥፍራ መምጣትና አንድ ሰው ወደአደንዛዥ ዕፅ ሱስ መግባት ሂደቱ ተመሳሳይ ነው፤ ሁለታችንም እንደዋዛ እንገባለን – እንደዋዛ መውጣት ግን ለሁለታችንም ከባድ ነው፡፡…” አዎ፣ በረከት በዊስኪ ጨዋታው ለሁነኛው ልክ እንደዚህ እንደሚያጫውተው ‘subconscious’-ኡን በርቀት በማንበብ መረዳት ይቻላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ለወደቀም ማዘን ተገቢ ነው፤ ‹ለሚወድቅ› ብላችሁ ልታሻሽሉትም ትችላላችሁ፡፡ እንደኔ ግን ወያኔዎች ሲነሱ ነው የወደቁት፡፡ ሰው ሲወለድ ነው የሞተው እንደምንል መሆኑ ነው፡፡ ወያኔዎችም ክፋትን መሥራት ሲጀምሩ፣ በቂም በቀል የተቃኘ የጥላቻ አገዛዛቸውን በስፋት ሲያጧጡፉ፣ ሀገርን ሲሸጡና ሲለውጡ፣ ምድርን በደም ረግረግ ሲሞሉ፣ አማራን ከትግሬ፣ ትግሬን ከኦሮሞ እዬለዩ አንዱን መጥቀምን ሌላውን መጉዳትን ባህላቸው ሲያደርጉ፣ ዳር ድንበርን እንዳወጣ ለባዕድ ሀገራት ሲቸበችቡ፣ ሀገርን ካለመውጫ በር ዘግተው የሚሊዮኖችን እስትንፋስ ሲዘጉ፣ … ያኔ ነው ወያኔዎች ገና በጧት ሳይወለዱ የሞቱት፡፡ እዚህ ላይ የሞት ዓይነት ብዙ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ እንጂ የአሁኑ እስትንፋሳቸውማ በ“ሥልጣን” ካሳለፉት ጊዜ አንጻር ሲታይ የደቂቃዎች ያህል ጊዜ ብቻ የቀራቸው ጉድጓዳቸው የተማሰ ልጣቸውም የተራሰ ስለመሆኑ ጨረቃና ፀሐያቸውን በማየት ብቻ የምንረዳው ነው – ዘመናቸው አልቋል፡፡ … የኔ አይደለም …የርሱ እንጂ፡፡ የፍርድ ሂደቱና ብያኔው ከታች አይደለም – ከላይ እንጂ፡፡
የኢትዮጵያን ገበሬ ኑሮ በረከት አያውቀውም ማለት ዘበት ነው፡፡ የኢትዮጵያን ገበሬ ወያኔ አያውቀውም ብሎ በዚህ ሰውዬ ንግግር መደመምም ከንቱ ነው፡፡ በገበሬው መቀለድ አምሯቸው እንጂ የሚናገሩት ነገር እውነቱ የተገላቢጦሽ መሆኑን አጥተውት አይደለም፡፡
ስለሆነም በረከት የሚለው ነገር “አይሰማም!” እንላቸዋለን ፡፡ በረከት ልፋ ብሎት ተናገረ የተባለውን ይናገር እንጂ የራሱ ስብሰባ አባላት ሳይቀሩ ሲችሉ በግልጥ ሳይችሉ ደግሞ በውስጣቸው ይስቁበታል፡፡ ለዚያውም ከትከት ብለው ነው እሚስቁበት – እንደጅል በመቁጠር፡፡ እርግጥ ነው – በረከት ጅል አይደለም፡፡ ጅል ለመምሰል የቆረጠው ግን ምርጫ በማጣት ይመስለኛል፡፡ አንድ ሰው ፀሐይ የሞቀውን እውነት ለመሸፈን በመሞከር በግልባጩ ለማውራት ከተገደደ አንድም ያስጨነቀው ነገር አለ ማለት ነው፤ አለበለዚያም የመዋሸት ተፈጥሯዊ ጠባይ  አለበት ማለት ነው – ልክ እንደመለስ ዜናዊ፡፡ መለስ ዜናዊ በሣይንስ የተረጋገጠ ላይሆን ይችላል እንጂ በእንግሊዝኛው ‘pathological liar’  የሚባል ዓይነት ግለሰብ እንደነበር መረዳት አይቸግርም፡፡ እርሱ በቲቪ ቀርቦ የሚናገራቸውን ንግግሮችና መሬት ላይ ይታይ የነበረውን እውነት በማስተያየት የዚህን ሰው ውሸት በመናገር የመርካት ጠባይ ወይም የተዛባ ተፈጥሯዊ ባሕርይ በቀላሉ መገንዘብ ይቻል ነበር፡፡ በዚህ መልክ ይህ ተጋቦታዊ ደዌ በትግል አጋርነትና በጥቅም ተጋሪነት ምክንያት ለበረከትም ተርፎ ይሄውና በረከትም አንድም ሰው ላያምነው – አንድም የራሱ ሰው ሳይቀር አምኖ ላይቀበለው – እንዲሁ ድከም ብሎት ሲወሻክት እናደምጠዋለን፡፡ እስከመቼ እየወሻከተ በሰው ስቃይ ሲደሰትና የሰውን ስቃይ ለሚዲያ ፍጆታ ያህል ለከንቱዎች በመሸጥ እንደሚኖር ገና የምናየው ይሆናል፡፡ ወደኅሊናው የሚመለስ አይመስለኝም እንጂ ከተመለሰ ግን የገበሬውም ሆነ የአጠቃላዩ የኢትዮጵያ ሕዝብ ካሉት በታች ከሞቱት በላይ የሆነ የሰቆቃ ሕይወት በሚያሳድርበት የእርግማን መዘዝ እንደይሁዳ ራሱን ሰቅሎ እንደሚገድል አምናለሁ፡፡ ያ ቀን ደግሞ በጣም ቀርቧል፤ ምን አለ በሉኝ እነዚህ ጉዶች የሥራቸውን የሚከፈሉበት ጊዜ በብርሃን ፍጥነት እየገሰገሰ በመምጣት ላይ መሆኑ ይሰማኛል፡፡ ቋቱ ሞልቷል፤ የሚቀረው የሚጠራርጋቸውን ማዕበል የሚያስነሣው የፈጣሪ ፊሽካ ብቻ ነው፡፡
የኃጢኣት ትንሽና ትልቅ ባይኖረውም አንድ ሰው ሰርቆ ቢበላ እርቦት ሊሆን ይችላልና ምንም አይደለም ሊባል ይችላል፤ ቢሳደብ ተናድዶ ሊሆን ይችላል በሚል ይቅርታ ሊደረግለት ቢችል ምንም አይደለም፡፡ ነገር ግን በመንግሥት ሠራሽ ርሀብና በግፈኛ አገዛዝ እያለቀሰ የሚኖርን ገበሬ በሚያስለቅሰው ዘረኛ ሥርዓት ተደስቶና ደልቶት እንደሚኖር በሚያስገርም አነጋገር ሰይጣናዊ ስብከትን በመገናኛ ብዙኃን መልቀቅ ከይቅርታ በላይ ነው፡፡ ብሶቱን ችሎ፣ የሚደርስበትን ግፍና መከራ ተቋቁሞ በሞትና በሕይወት እየተንጠራወዘ በሚኖር ሕዝብ ላይ ይህን የመሰለ ቀልድና ድራማ እየሠሩ መሣለቅ ለዘር የሚተርፍ መራራ ቅጣት ሊያስከትል እንደሚችል በረከትም ሆነ ግብረ አበሮቹ መረዳት አለባቸው፡፡ ይህ መሪር ቀልዳቸው ዛሬና ለነሱ ምንም ላይመስል ይችላል፡፡ ይሁንና እያንዳንዷ የምናደርጋት መጥፎ ነገር ሁሉ ትልቅ ዋጋ ሳታስከፍል እንዲሁ የምትቀር እንዳልሆነች ቀልደኞቹና በኢቲቪ የሚገኙ ሆዳም ወናፎች ሁሉ ሊገነዘቡት ይገባል፡፡ ዛሬ ገበሬውም ሆነ ከተሜው አንደበቱ ተለጉሟል፤ አይናገርም፤ ሊናገርም አይፈልግም፡፡ ሰሚ ስለሌለውና ፈጣሪው ፊቱን እንዳዞረበት ስለተረዳ ሁሉም በዝምታ  ተቀምጧል፡፡ ይህ ማለት ግን ዘመን አይለወጥም፣ ዝም ያለም ሁሉ ደንቆሮና አላዋቂ ነው  ማለት አይደለም፡፡ ወያኔ እንዳልነበር ሁሉ የማይኖርበት ጊዜ ሲመጣ ሊከሰት የሚችለውን ትዕይንት አለማየት ነው፡፡ ያኔ እንደዛሬው እዩኝ እዩኝ እንደተባለ ሁሉ ደብቁኝ ደብቁኝ የሚባልበት ጊዜ መድረኩን ይረከባል፡፡ ጥጋብ ደግሞ ወደራብ መንዳቱ ያለና የነበረ ነው፡፡ የጠገበ የሚራብ የማይመስለው የመሆኑ መጥፎ አጋጣሚ ግን አሳዛኝ የታሪክ ግጥምጥሞሽ እንደሆነ እስካሁን አለ – ሲገርም፡፡ አንዱ ከአንዱ ገመና ትምህርት ቢገበይ፣ የሚነሣው ከሚወድቀው ቢማር ግና የችግሮቻችን መንስኤዎች እንደጤዛ በረገፉ፣ እንደጉምም በበነኑ ነበር፡፡ ይህ አለመታደል እስከመቼ እንደሕግ ሆኖ እንደሚበጠብጠን አላውቅም፤ እስኪ የመጨረሻችን ያድርግልን፡፡
በማጠቃለያዬ ማሳሰብ የምፈልገው ነገር አለኝ፡፡ በረከትም ሆንክ ሌላ ጊዜ ሰጠኝ የምትል ባለሥልጣን ሁሉ ካለፈው ታሪክ ተማር፡፡ የሚያሳዝነኝ ነገር አፄዎቹ ከቀደሙት አፄዎች መማር ሳይፈልጉ ቀሩ፤ ቀሩናም ሕዝብን ሲንቁ ሲንቁ ቆይተው በናቁት ሕዝብ እርግማንና አመፅ ምክንያት እንዳልሆኑ ሆኑ – ዘር እንኳን አልወጣላቸውም፡፡ ደርግም ፈጣሪን ሣይቀር ከድቶና አስከድቶ ራሱን የፈጣሪን ያህል በመቁጠር ሕዝብን ሲንቅና ሲያዋርድ ቆይቶ በናቀውና ባዋረደው ሕዝብ እርግማንና ሁለንተናዊ የእምቢታ አመፅ ሰበብ እንደባቢሎን አይሆኑ ሆኖ ተንኮታኮተ – ስንትና ስንት ዘመናዊ ትጥቅ እያለው አንዱም አላዳነውም፤ ይንቃቸው በነበሩ መናኛ የጫካ ወሮበሎች በቀላሉ ተገፍትሮ ወደቀ፡- መጽሐፉ ‹ንጉሥ በሠራዊቱ ብዛት አይድንም› እንደሚል መዘንጋት አይገባም፡፡ እነዚህኞቹ ፀረ-ኢትዮጵያ ጉጂሌዎችም አይነጋ መስሏቸው የኢትዮጵያ ታሪክ መዝገብና ሕዝቡ ሊሸከሙት ያልተቻላቸው ግፍና በደል በሀገርና በሕዝብ ሠሩ፤ ዋናዎቹ የአገዛዙ ቁንጮዎች በሣምንታት ልዩነት ወደማይቀሩበት የሲዖል ሥፍራቸው ተጓዙ፤ ቀሪዎቹም በመኖርና ባለመኖር አጣብቂኝ ውስጥ ተሰንቅረው ያደርጉትን በማጣት ፈጣሪ ሩህያቸውን ጨርሶ እስኪወስዳት እየተንጠራወዙ ይገኛሉ – ይህን እውነት ማስተሃቀር ፈጽሞውን የሚቻል አይደለም፡፡ ለውስጥ አዋቂዎች ወያኔዎች በሕይወት እንደሌሉ ከገባን ቆይተናል፡፡ በሕይወት ያሉ እንዲመስሉ የሆነው ምናልባት ለበጎ ነው፡፡ እንጂ እንደእውነቱ ወያኔ አከርካሪው የተመታው ዋናውን የሥርዓቱን መሃንዲስ መለስ ዜናዊን ፈጣሪ ባልተጠበቀ ወቅት ገና በ‹ማለዳ ዕድሜ›ው ሲጠራው ነው፡፡ ልብ ከተገኘ “ሁሉም ከእያንዳንዱ፣ እያንዳንዱም ከሁሉም እንዲማር ጊዜ ለመስጠት ተብሎ ነው የወያኔ የማይቀር ኅልፈት አዝጋሚ እንዲሆን የተደረገው” ብሎ ማሰብም ይቻላል – ምንም ነገር ማሰብ በማንም አልተከለከለምና (ወያኔዎች ግን ይህንንም ተፈጥሯዊ መብት ሊነፍጉን ይቃጣቸዋል፤ ኢትዮጵያ ውስጥ እየኖርክ ወያኔን ስለመጣል ወይም በሀገሪቷና በሕዝቡ ላይ የጣሉትን ግፈኛ የአገዛዝ ቀምበር ስለመቃወም “ማሰብ”ም አትችልም – ማሰብህ በዐይነ ውኃህ የፊት-ንባብ ከተደረሰበት በአሸባሪነት ተጠርንፈህ ዘብጥያ ትወርዳለህ)፡፡ ማሰብ በቻልንበት ሃሳብ ውስጥ በጊዜ ሰጪነት የምንጠረጥረውን አካል ደግሞ ለሁላችንም እኩል በሚገባን ቋንቋ አቶ ታሪክ ልንለው እንችላለን፡፡ ታሪክ የሚያዳላ ይመስለናል እንጂ ለማንምና ለምንም በጭራሽ አያዳላም – የራሱ የጊዜ ቀመር እንዳለው ግን ማጤን ተገቢ ነው (እርግጥ ነው – ‹መብሰሉ ለማይቀረው ጭንቅላት እንጨት ይፈጃል› እንደሚባለው አንድ ታሪካዊ ኹነት ተከናውኖ ቀጣዩ ሌላ ኹነት እስኪከናወን የሚኖረው የጊዜ እርዝማኔ በትግስታችንና በሃይማኖታችን ጭምር አሉታዊ ጥላውን ማጥላቱ የማናልፈው የዘመን ቅጣት ይመስላል፤ ማን ነበረች – አዎ፣ ሜሪ አርምዴ – “ፍቅር ያዘኝ ብለሽ አትበይ ደንበር ገተር፤ እኛም አንድ ሰሞን እንደሱ አ’ርጎን ነበር፤› ያለችውን የዘፈን ግጥም አለመዘንጋት የአጽናኝነት ጠቀሜታ አለውና እናስታውሰው፡፡) ዕድሜ ይስጠን ሁሉን እናያለን፡፡ ሌላ ዘፋኝም “እናያለን ገና” ብሏል፡፡ ይህንኑ ዘፈን ልጋብዛችሁና እንለያይ፡፡ ጣሊያኖች ሲለያዩ “አሪቬዴርቺ” ይላሉ – በ“ሰላም ያገናኘን” ለማለት፡፡
ሰበር መርዶ!
ይህን ጦማር ጽፌ የጨረስኩት ሌሊት ነው፡፡ ጧት ወደሥራ ልሄድ ስነሳ እንደወትሮው ሁሉ ቤቴ አጠገብ የሚገኙ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎቻቸውን ወደዬክፍላቸውን ከማስገባታቸው በፊት ሰንደቁ አጠገብ አሠልፈው ብሔራዊ መዝሙር በቴፕ ከፍተው ሲያጮኹ ሰማሁ፡፡ ይሄኔ ኮምፒውተሬን ከፍቼ ይህችን ሃሳብ በሰበር መርዶነት ለመሰንቀር ወደድኩ፡፡ የሀገር ሞት ከዚህ በላይ የለም፡፡ በጥንት ጊዜ ብሔራዊ መዝሙር ተማሪው ነበር በስሜት ተውጦ በመዘመር ወደክፍሉ የሚገባው፡፡ አሁን ዕድሜ ለወያኔ አዲሱ መዝሙር ሊያውም በመሣሪያ ብቻ የተቀነባበረው በቴፕ ይዘፈንና ወደክፍል ይገባል፡፡ ዛሬ ዛሬ የኢትዮጵያን ብሔራዊ መዝሙርና ባንዴራ የሚያውቅ ትውልድ እየጠፋ ነው፡፡ ራሱ መለስ ዜናዊ (በሕይወት ኖሮ) ይህን መዝሙር ውጣው ቢባል የሚችለው አይመስለኝም፡፡ ሌሎቹ የወያኔ ባለሥልጣናት ቢጠየቁም የሚያውቁት ስለመሆናቸው እርግጠኛ መሆን አይቻልም – ብቸኛ ዘመዳቸው ሆዳቸው በመሆኑ ስለሀገር ምንነት የሚያውቁት ነገር የለም ማለት ይቻላል፡፡ የሚሰቀለው ባንዴራ ደግሞ የተቀዳደደ፣ የነተበ፣ ቀለሙን የለወጠ፣ ከተሰቀለ የማይወርድና ተበጣጥሶ እስኪያልቅ 24 ሰዓት የሚውለበለብ የማን ሀገር ባንዴራ መሆኑም የማይታወቅ ነው፤ የጥንቱን የባንዴራ አሰቃቀልና አወራረድ ሥርዓት የሚያስታውስ ዜጋ የአሁኑን ሲያይ ያለቅሳል፡፡ ከአዲስ አበባ ወጣ በሚል ቦታ ደግሞ የኦሮሚያ ባንዴራና የኦሮሚያ ብሔራዊ መዝሙር በትምህርት ቤቶች እንደዚሁ በቴፕ ሲዘመር ወይም ልጆች በግዴታ አጥንተው እንዲዘምሩት ሲደረግ ታያላችሁ፡፡ ይህችን የነፃነት ምኩራብ የሆነች የታሪክ አምባ ሀገራችንን እንዲህ ባለቤት ያሳጧት የሰይጣን ልጆች ዋጋቸውን ሳያገኙ ከቀሩ በርግጥም ኢትዮጵያ ፈጣሪ የላትም፡፡ አላስችል ብሎኝ አሁን በእግረ መንገድ ትንሽ ለመናገር ፈለግሁ እንጂ ይህ ጉዳይ ብዙ የሚያናግር ነው – የጋራ የሚባለል አንዳችም ነገር እንዳይኖረን ከፍተኛ የጥፋት ሥራዎች በመሠራታቸው አሁንና ለጊዜው ጠፍተናል፤ አለን እንላለን እንጂ በርግጥም በወኔያዎች ደባና ሤራ የአብሮነት ኅልውናችን አደጋ ላይ ወድቋል – ብዙ የትስስር ገመዶች ተበጣጥሰዋል፡- የጋራ ቋንቋ፣ የጋራ መሪ(ዎች)፣ የጋራ የመከላከያ ጦር፣ የጋራ የፖሊስ ሠራዊት፣ የጋራ ድንበር፣ የጋራ ባህል፣ የጋራ ትውፊት፣ የጋራ ሥነቃልና ሥነ ጽሑፍ፣ የጋራ ቤተ መንግሥት፣ የጋራ መንግሥታዊ መዋቅር፣ የጋራ… የጋራ… የጋራ… የምንለው ነገር እንዳይኖረን ተደርገን አንዳችን አንዳችንን የጎሪጥ እንድናይና እንድንፈራራ ተደርገናል፡፡ ሌላው ሁሉ ቀርቶ የጋራ ስብዕና ወይም የሰውነት ደረጃ እንኳን የለንም፤ አንዱ ከሌላው የበለጠ ሰው ነው – ሌላውም ከአንዱ ያነሰ ሰው ነው፡፡ አንዱ የሰው ዘር ከሌላው በተለዬ ምርጥ ነው – ሌላው ደግሞ ውዳቂና ቢገድሉት የበቃ ነፍሱ ከእንስሳት ነፍስም ሳይቀር ያነሰ ዋጋ ያለው ነው – ሩቅ ተመልካቹ ጆርጅ ኦርዌል ጨርሶታል – “All animals are equal, but some are more equal than the others.”፡፡ በዚህ መልክ በፈረጁን ሰዎች ነው እንግዲህ አጥንታችን ድረስ ዘልቆ በሚጠዘጥዝ መሪር ፈረዖናዊ አገዛዝ እየተቀጠቀጥን የምንገኘው፡፡
ያን ደገኛ ኢትዮጵያዊ የአንድነት መንፈስ ለማምጣት እነቴዲ አፍሮን የመሰሉ የቁርጥ ቀን ልጆች ብቻ ሣይሆኑ ሁላችንም የየበኩላችንን ጥረት ማድረግ ይኖርብናል – ለራሳችንና ለልጆቻችን ስንል፡፡ ከራስ ወዳድነትና ከአህያይቷ የ‹እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል› ያረጀ ያፈጀ አስተሳሰብም ባፋጣኝ እንውጣ፡፡ አርቀን መመልከትን ባህላችን እናድርግ፡፡ ጎርፉ ሳይደርስብን ራሳችንን በኅሊና ጸጸት አጥበን ለመጪው መልካም ኢትዮጵያዊ ዘመን ዝግጁ ሆነን ለመጠበቅ እንሞክር፡፡ በየድረ ገጹ የሚታዬው ዘረኝነት ላይ የተመሠረተ ወያኔያዊ የዱባ ጥጋብ መሰል ቡራከረዩና ወንዝ የማያሻግር ከፋፋይ ፕሮፓጋንዳ ዘመኑን እያገባደደ በመሆኑ የአንዲት እናት ልጆች ነንና እንሶብር፡፡ ወያኔ የጋተንን ብርብራና መቅመቆ ማርከሻ እንፈልግለት፤ “ስሜት-ወለድ” ማስጠንቀቂያየን እዚህም ላይ ልድገመው – “እዩዩኝ ያለ ደብቁኝ ደብቁኝ ይላል”፡፡

No comments:

Post a Comment