Thursday, January 23, 2014

አልበሺር እና የኢትዮ ኤርትራ የሰላም ጥረት


የሱዳኑ ፕሬዚደንት ኦማር ሀሰን አልበሺር በኤርትራ ያደረጉት ጉብኝት የሁለቱን ኣጎራባች ኣገሮች ግንኙነት ከማጎልበት ጎንለጎን በአካባቢያዊ እና ዓለም ዓቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ መሆኑ ተገለጸ። ኣልበሺር ከኤርትራው አቻቸው ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር ባደረጉት የሶስት ቀናት ቆይታ የደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ሁኔታን ጨምሮ
በተለይም የኢትዮ ኤርትራን የሰላም ንግግር ስመልክቶ መነጋገራቸውን ምንጮች ኣመልክቷል።
የኣሁኑ ውይይት በሁለቱ ተደራዳሪ ኣገሮች በኩል ሊቀርቡ በሚችሉ ቅድመ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ነበርም ተብሏል።
የሱዳኑ መሪ ኦመር ሓሰን ኣልበሺር፣ ባለፈው ሳምንት በኤርትራ ያደረጉት የሶስት ቀናት ጉብኝት፤ የሱዳኑ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ኬርቲ ለዜና ወኪሎች እንዳስረዱት፤ የሁለቱን ኣጎራባች ኣገሮች ግንኙነት በማጎልበት ላይ ያተኮረ ነበር። የኣልበሺር ጉብኝት ባለፈው ህዳር ወር የኤርትራው ኢሳያስ አፈወርቂ በሱዳን ያደረጉትን ጉብኝት ተከትሎ የተደረገ መሆኑን የጠቀሱት የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ኬርቲ በዚህ ግንኙነት ሁለቱ መሪዎች ከዚህ ቀደም የተፈረሙ የውል ስምምነቶች ሊተገበሩ ስለሚችሉባቸው ዝርዝር ጉዳዮች ላይ መምከራቸውንም ኣስረድቷል።
ባለፈው ማክሰኞ ኤርትራ ሲገቡ ደማቅ ኣቀባበል የተደረገላቸው ኣልበሺር ከኣስመራ ውጪ ያሉ ኣንዳንድ ከተሞችንም የጎበኙ ሲሆን በኤርትራ 21ኛ ዓመት የነጻነት በዓል ላይም ተገኝተው ነበር። ሁለቱ መሪዎች፣ ኣልበሺር እና ኢሳያስ፣ የዔርትራው ገዢ ፓርቲ የፖለቲካ ጉዳዮች የበላይ፣ የማነ ገ/ዓብ፣ ለዜና ምንጮች እንደገለጹት፣ የደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ሁኔታን ጨምሮ በበርካታ አካባቢያዊ እና ዓለም ዓቀፋዊ ጉዳዮች ላይ የመከሩ ሲሆን ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ደግሞ ኣንዱና ዋናው የመሪዎቹ አጀንዳ የኢትዮ ኤርትራ የሰላም ንግግር ነው ተብሏል።
በኖርዌይ ኣገር፣ ስታቫንገር ዩኑቨርሲቲ፣ የፖለቲካል ሳይንስ እና ዓለም ዓቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር ግሩም ዘለቀ እንደሚሉትም የኣልበሺር የኣስመራ ጉብኝት የሰላም ንግግሩ የመጀመሪያው ምዕራፍ ሲሆን በሁለቱ ወገኖች በኩል ሊቀርቡ በሚችሉ ቅድመ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል።
እርቀ ሰላም መውረዱ ለሁለቱም ኣገሮች በተለይ ም ደግሞ ዶ/ር ግሩም እንደሚሉት ለኤርትራ ከፍተኛ ጠቀሜታ ነው ያለው።
ከኤርትራ በኩል በጉዳዩ ላይ እስከ ኣሁን ይፋ የሆነ መግለጫ ባይኖርም በኢትዮጵያ በኩል ግን፤ የጠ/ሚኒስትሩ ቃ/አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ እንደሚሉት፣ ቀደም ሲል የተቀመጡት ቅድመ ሁኔታዎች እንደተጠበቁ ሆነው ለመደራደር ግን መንግስት ዝግጁ ነው።
በዚህ የሰላም ንግግር፤ ከተሳካ ማለት ነው፤ ተጠቃሚዎቹ በዋናነት ሁለቱ ኣገሮች ቢሆኑም ዶ/ር ግሩም ዘለቀ እንደሚሉት ደግሞ ኣልበሺርም ቢሆኑ በግልም ጭምር ተጠቃሚ መሆናቸው መዘንጋት የለበትም።
ከተገንጣዩዋ የደቡብ ሱዳን መንግስት ጋር ካለባቸው የግዛት ይገባኛል ውዝግብ በተጨማሪም የዳርፉር ቀውስን ጨምሮ በሰሜን ኩርዱፋን እና በብሉ ናይል ግዛቶችም በውስጥ ችግሮች ተጠምደው የሚገኙት ኣልበሺር ምንም እንኳን ከኣፍሪካ ህብረት በኩል አንጻራዊ ተቀባይነት ቢኖራቸውም በምዕራባውያኑ ዘንድ እንደ ወንጀለኛ መፈረጃቸው ይታወቃል። በዚሁ የተነሳም ዓለም ዓቀፉ ፍ/ቤት ICC የእስር ማዘዣ እንደቆረጠባቸው ይገኛሉ።
ጃፈር ዓሊ
ኂሩት መለሰ

No comments:

Post a Comment