Thursday, January 30, 2014

ሆድ ያባውን ንግግር ያወጣዋል''- የጀዋር መሐመድ እና መሰሎቹ ፅንፈኛ 'ሜጫዊ' አስተሳሰብ አላማው ህዝብን ማፋጀት ነው!

ሆድ ያባውን ንግግር ያወጣዋል''- የጀዋር መሐመድ እና መሰሎቹ ፅንፈኛ 'ሜጫዊ' አስተሳሰብ አላማው ህዝብን ማፋጀት ነው! ('ሜጫ' የሚለውን ቃል ከጀዋር ንግግር አገባብ መረዳት እንደሚቻለው ካራ፣ጎራዴ ለማለት ተጠቅሞበታል) በአሜሪካዋ ሚኒሶታ ግዛት ሁለቱ ''አክቲቪስት'' ጀዋር መሐመድ እና ሃጂ ነጂብ መሐመድ ያደረጉት ንግግር አስደንጋጭ እና አሳሳቢ ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ በመጪው ግዚያት የሚገጥሟትን ተግዳሮቶች የሚያመላክትም ጭምር ነው። የጀዋር መሐመድ ''ሙስሊም ያልሆነውን'' እንደርሱ አገላለፅ እርሱ በተወለደበት አካባቢ ''በሜጫ አንገቱን እንደሚቀላ'' የተናገረበት እና ሃጅ ነጂብ መሐመድም በተራቸው ''ከኦሮሞ ተወላጅ ባብዛኛው (ከ80% በላይ) ሙስሊም ነው .....በኢትዮጵያም እንዲሁ ከ ሃምሳ ሚልዮን በላይ ነን.....'' ሲሉ ተደምጠዋል። ሁለቱም የሜኖሰታ ተናጋሪዎች ከእዚህ ቀደም በሙስሊም ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ላይ እየደረሰ ያሉትን መንግስታዊ የአስተዳደር በደሎች ለማስተጋባት ''ድምፃችን ይሰማ'' በሚሉ መድረኮችም ሆኑ ሌሎች መድረኮች በማስተጋባት መታወቃቸው ብዙ ግን አስፈላጊ ጥያቄዎች እንዲነሱ በር ከፍቷል። በሀገራችን ካለው የፖለቲካ፣የሃይማኖት፣ወዘተ በደሎች አንፃር የእስልምና ወንድሞቻችን የሚያነሱዋቸው ጥያቄዎች በትክክለኛ በኢትዮጵያ አንድነት፣ነፃነት እና ዲሞክራሲ በሚያምኑ ወገኖች አማካይነት ሲነሳ እና ሲመራ ማየት የሁሉም ሀገር ወዳድ ወገን ፍላጎት ነው።ከእዚህ በዘለለ ግን ጉዳዩ የአክራሪነት እና የፅንፈኝነት ስሜት በያዙ ወገኖች እሳት ዳር እንደሚጫወት ሕፃን ያሻቸውን ሲያደርጉ መመልከት ደግሞ ተገቢ አይደለም። ጉዳያችን ጡመራ ባለፈው አመት ጥቅምት 2004 ዓም ላይ ''የሙስሊሙ ጉዳይ'' በሚለው ርዕስ ስር እንቅስቃሴው ወዴት ሊያመራ ይችላል? በሚል ከእዚህ በታች ያለውን ሁለት ስጋቶች አስቀምጣ ነበር። ''ጉዳያችን ጡመራ'' ቀ 27 ወራት በፊት (ጥቅምት/2004 ዓም) የነበራት ስጋት ''የ ሙስሊም ፅንፈኛ ቡድን'' የ ሙስሊሙን ጥያቄ የመሪነት ሚና ለመያዝ ቀና ማለት አልፎ አልፎ ብቅ ሲል የነበረው በ ሙስሊሙ ሃይማኖት ስም የሚንቀሳቀሰው ''የ ሙስሊም ፅንፈኛ ቡድን'' ከ ቢጫ ቀጥሎ ይወሰዳል ለተባለው እርምጃ የመሪነት ሚናውን ለመያዝ ቀና ቀና ማለቱ አይቀርም።በ ኢትዮጵያ ከ ቅርብ አመታት ወዲህ በ ጅማ፣ሐረር፣እልባቦር እርሲ ወዘተ እነኝህ ፅንፈኛ ቡድኖች በ አብያተ ክርስትያናት እና ምእመናን ላይ ጥቃት ሲፈፅሙ እንደነበር ይታወሳል።በመሆኑም የ ሙስሊም ወንድሞቻችን እና እህቶቻችንን የማይወክሉ ግን ለ እራሳቸውም እንግዳ ትምህርት ይዘው የመጡባቸው ክፍሎች የ እዚህ አይነቱን ቀይ ካርድ መምጣት ''ሰርግ እና ምላሽ '' አርገው እንደሚመለከቱት ሳይታለም የተፈታ ነው። እዚህ ላይ በ ነሐሴ ወር ላይ የ ''አልሸባብ'' ሰዎች ሳይሆኑ አይቀሩም የተባሉ በ ከፍተኛ ደረጃ የታጠቁ ቡድኖች በሞያሌ ከተማ ላይ ያደረጉት ጥቃት አይዘነጋም። በ አፍሪካ ቀንድ ለዘመናት ችግር ሲፈጥር የነበረው አለም አቀፍ አክራሪ እስልምና መነቃቃት ይጀምራል። በ አፍሪካ ቀንድ ለዘመናት ችግር ሲፈጥር የነበረው አለም አቀፍ አክራሪ እስልምና በመነቃቃት ለ ኢትዮጵያውያን የ ፅንፈኝነት አስተሳሰብ ያላቸውንሙስሊሞች የ መንግስት ስልጣን ጥያቄ እንዲያነሱ እና ኢትዮጵያ ''እስላማዊ መንግስት'' እንዲኖራት ወደሚል ግብ እንዲሄዱ ይህን ካደረጉ ብቻ ከ ጎናቸውእንደሚቆም ግፊቱን ሊያደርግ ይችላል። ይህንን ደግሞ ብዙ ሙስሊም ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን አይደግፉትም። ለ እዚህም ነው ጥያቂያቸውን በጥንቃቄ እና በ ሰላማዊ መንገድ ብቻ በ ማቅረብ ብዙውን ሕዝብ ያስደመሙት። ከ እዚህ በተጨማሪ የ አለም አቀፍ ፅንፈኛ የ እስልምና እንቅስቃሴ በኢትዮጵያ ቦታ ካገኘ ሁለት መሰረታዊ ክስተቶች በ ሀገራችን ላይ ሊያመጣ ይችላል። እነርሱም አንድ የ ሃያላኑ መንግሥታት ጣልቃ ገብነት ቢያንስ በ ቁሳቁስእና በ ቴክኒክ እርዳታ ነገሩን ማወሳሰብ እና ሁለተኛው ከ እስልምና ውጭ በሆነው ኢትዮጵያዊ ጋር ከፍተኛ ፍጥጫ ውስጥ መክተቱ የሚሉት ይጠቀሳሉ።'' ዛሬ ጀዋርም ሆነ ሃጅ ነጂብ መሐመድ እያመላከቱን ያሉት ይህንኑ ነው።የዲሞክራሲ ጥያቄን በድምር የመመለስ አባዜ ማለትም ችግሩ የብሔር እገሌን ችግር መፍታት፣የሃይማኖት እገሌን ችግር መፍታታ፣ ወዘተ የሚሉ የአምባገነንነትን መጫኛ ፈረስ ማዘጋጀት የተበላ ዕቁብ ከመሆን አያልፍም።ጀዋርም ሆኑ ሃጅ ነጂብ መሐመድ በመኖሶታው መድረክ ሊነግሩን የፈለጉት ''ውሃ ቢወቅጡት እምቦጭ'' መሰል ላለፉት ሃያ አንድ አመት ስንሰማው የነበረውን ''ኢትዮጵያን በብሄር ከፋፍሎ አላማን ማሳካት'' የሚለውን ያፈጀ መዝሙር መሰል ማላዘን ነው።እነርሱ የጨመሩበት ነገር ቢኖር ''በኦሮሞ ስም የታሸ አዲስ እስልምና'' ያለ መሆኑን ለመናገር ደፋርነት ማሳየታቸው ነው። ይህ ሂደት በእራሱ በወንድማማችነት የኖረውን የእስልምናውን ሃይማኖት የሚጣረስ እና በሃይማኖቱ ብሔር ብቻ ሳይሆን የሀገር ድንበር የማይገድበውን በአለማችን ካሉት ታላልቅ አምነቶች አንዱ -እስልምናን እንደነርሱ አገላለፅ ''በኦሮሞነት'' ስር መሸበብ ነው። በመሰረቱ የኢትዮጵያ የእውነተኛ ዲሞክራሲ ጥያቄ በግለሰቦች ''ሜጫዊ'' ''ቁረጠው!ፍለጠው!'' ንግግር እና ጣልያን ኢትዮጵያን ሲወር በተጠቀበት መርዛማ ንግግር ብሄርን ከብሄር አልያም የሃይማኖት ተከታይን ከሃይማኖት ተከታይ በማበላለጥ አይሰናከልም። በብሄር እና በሃይማኖት ለመከፋፈል የቆሙ የመኖራቸውን ያህል ለኢትዮጵያ አንድነት እና ለእምነቶች መከባበር የቆሙ ሚሊዮኖች ኢትዮጵያ እንዳላት መዘንጋት አይገባም።የጀዋር መሐመድ እና የሃጅ ነጂብ መሐመድ ንግግር ግን የመብት፣የዲሞክራሲ እና የአንድነት ትግሉን ጠልፎ ወደ አለተፈለገ አቅጣጫ የመግፋት የግል ስሜታቸውን ከመግለፅ ባለፈ የሚያመጣው አዲስ ነገር አይኖርም። ይልቁን ''ሆድ ያባውን ንግግር ያወጣዋል'' የሚል ስያሜ መስጠት ግን የሁለቱን ንግግሮች በበቂም ባይሆን በመጠኑ የሚገልፀው ይመለኛል። በመጨረሻም የጀዋር መሐመድ እና የሀጂ ነጂብ መሐመድን ንግግር ይመልከቱ። (ጉዳያችን ጡመራ ጥቅምት/2004 ዓም http://gudayachn.blogspot.no/2012/10/blog-post_5.html )

No comments:

Post a Comment