Sunday, January 5, 2014

አቶ አያሌው ጎበዜ ከአማራ ክልል ፕሬዝዳንትነታቸው ለምን ተነሱ?

Zehabesha Amharic


ከአቡዛብር ተገኝ


ፋክት መፅሄት (በታህሳስ 2006፣ ቁጥር 26 እትሙ) የአማራ ክልል ፕሬዝዳንት የነበሩት አቶ አያሌው ጎበዜ በምን ምክንያት ከስልጣን እንደ ተነሱ ያሰፈራቸውን መላምቶች አንብቤያለሁ፡፡ ብዙዎቹ በግምትና በይሆናል ላይ የተመሰረቱ ከመሆናቸውም በላይ ለግለሰቡ ከፕሬዝዳንትነት መነሳት በዋና ምክንያትነት ሊመደቡ የሚችሉ አይደሉም፡፡ ለዚህም ነው ለመፃፍ መነሳቴ፡፡
አቶ አያሌው ከአማራ ክልል ፕሬዝዳንትነት የተነሱበት ዋና ምክንያት ምንድነው?
ከዜናው ሀሳብ በመነሳት በአንድምታ የምንረዳው እውነታ ስላለ፣ በኢቲቪ ከቀረበው የአቶ አያሌው ዱላ የማቀበል ዜና ልጀምር፡- በኢቲቪ ዜና መሰረት አቶ አያሌው ጎበዜ ከአማራ ክልል ፕሬዝዳንትነት ስልጣናቸው የተነሱት በፍቃዳቸው ነው፤ “በቃኝ፣ ዱላውን ላቀብል” ብለው፡፡ እንኳንስ ከክልል ፕሬዝዳንትነት ስልጣን ላይ ይቅርና ከተራው የሹመት ስልጣን (ለምሳሌ ምክትል ቢሮ ሀላፊ፣ ከዚያም ዝቅ ሲል “ፕሮሰስ ኦውነር”) ላይ በራሱ ፈቃድ “ልውረድ” ያለን የፖለቲካ ተሿሚ፣ ኢህአዴግ “‘በቃኝ’ ካልክማ እሰዬ” ብሎ ቶሎ የመልቀቅ ልምድ የለውም፤ ኢህአዴግ እንደ ገብስ ቆሎ ሳያሽ የማውረድ ባህል የለውም፡፡ ኢህአዴግ፣ አፍ አውጥቶ “ሹሙኝ-ሹሙኝ” ያለን ወይም በጣም “በሚያስበላ” ሁኔታ እንዲሾም የቋመጠን ሰው የስልጣን መንበሩ የማያቀምሰውን ያህል፣ “ስልጣን በቃኝ” ያለን አባል፣ ተንደርድሮ አያወርድም – ለዚያውም የክልል ፕሬዝዳንት ያህልን ሰው፣ ለዚያውም አስቸኳይ መደበኛ የምክር ቤት ስብሰባ ጠርቶ፡፡
አያሌው ጎበዜ
አያሌው ጎበዜ

ስለሆነም ኢቲቪ አቶ አያሌው ጎበዜ በራሳቸው ፈቃድ “የመተካካት መርሁ በ’ኔም ላይ ይተግበርልኝ” ብለው ከፕሬዝዳንትነታቸው ስለመልቀቃቸው የነገረን ዜና ታእማኒነት የሌለው፣ የተለመደ የኢህአዴግ ድራማ ለመሆኑ አንድ ማሳያ ነው፡፡ ሌላው ማሳያ ግለሰቡ አስቸኳይ መደበኛ የምክር ቤት ስብሰባ ከስልጣን በለለቁበት እለት፣ ሙሉ አምባሳደር ሆነው የመሾማቸው “ትንግርት” ነው፡፡ የአማራው ክልል የምክር ቤት አስቸኳይ መደበኛ ስብሰባ የተጠራው፣ በአቶ አያሌው የቀረበውን “የመተካካት መርሁ በ’ኔም ላይ ይተግበርልኝ” ጥያቄ አዳምጦ ካመነበት ከፕሬዝዳንትነታቸው ሊያነሳቸው፣ ካላመነበት ደግሞ ጥያቄውን ውድቅ ሊያደርግ ነው፡፡ ወይም ደግሞ ጥያቄያቸውን በመሰረታዊ ሀሳብነት ተቀብሎ ከፕሬዝዳንትነታቸው የሚያነሳበትን ወቅት ግን የተወሰነ ጊዜ ሊያራዝም ይችላል፡፡
ከአምባሳደርነት ሹመታቸው የምንረዳው ግን ሁሉም ነገር ቀድሞ ያለቀ መሆኑን ነው፡፡ ግለሰቡ መነሳታቸውም፣ መሾማቸውም ያለቀ ነገር ነበር፡፡ መቼም ምክር ቤት ተብዬው የመወሰን ሙሉ ቀርቶ እንጥፍጣፊ ስልጣን እንኳን ቢኖረው፣ በአምባሳደርነት የተሾመን ግለሰብ ከፕሬዝዳንትነት ስለማውረድ፣ አለማውረድ ጉዳይ እንዲወያይ ባልተደረገ ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር አቶ አያሌ ጎበዜ ከፕሬዝዳንትነታቸው እንዲነሱ ለምክር ቤቱ ሀሳባቸውን ካቀረቡበት እለት በፊት አምባሳደር ሆነው ተሹመዋል፡፡ ስለሆነም ቢያንስ በዚያች እለት ግለሰቡ ሁለት ጥምር ስልጣን በትከሻቸው ላይ ነበር – የአማራ ክልል ፕሬዝዳንትም፣ በቱርክ የኢትዮጵያ ሙሉ አምባሳደርም ነበሩ፡፡ ስለዚህም የአማራው ክልል ም/ቤት አስቸኳይ መደበኛ ስብሰባ ተጠርቶ ሲወያይ የነበረው፣ ቀድሞውኑ ከፕሬዝዳንትነቱ በተነሳና አምባሳደር ሆኖ በተሸመ ግለሰብ (አቶ አያሌው) ጉዳይ ላይ ነበር፡፡ (የኢህአዴግ ድራማ እንዴት ደስ ይላል¡)
ድራማው ግን በዚህ አያበቃም፡፡ አቶ አያሌው ለምን ከፕሬዝዳንትነታቸው እንዲነሱ ተደረገ? ፋክት መፅሄት ከተወሰኑ መላምቶች አንፃር በማየት ስለግለሰቡ አነሳስ ምክንያት ለማቅረብ ሞክራለች፡፡ ሆኖም አንዳንዶቹ መላምቶች የተሳሳቱና እጅግ የተጋነኑ ስለሆነ፣ እኔ ለክልሉ ባለስልጣናት ካለኝ ቅርበት አንፃር የተወሰኑት ላይ ማስተካካያ ለመስጠትና ለግለሰቡ ከስልጣን መነሳት ዋናውን ምክንያት ለመጠቆም እፈልጋለሁ፡፡
አቶ አያሌው ከስልጣን የተነሱት ለሱዳን ከተሰጠ የወሰን አካባቢ ቦታ ጋር የተያያዘ መሆኑን አንዳንድ ሰዎች ይናገራሉ፡፡ ከዚህ በፊትም አቶ አያሌው “አልፈርምም አለ” ተብሎ መናፈሱ ይታወቃል፡፡ ይህ ግን ስህተት ነው፡፡ አቶ አያሌ በዙሪያቸው ያሰባሰቧቸው የወንዝ ልጆች በስፋት የለቀቁት ተራ ፕሮፓጋናዳ ነው፡፡ አንደኛ መለስን እንኳንስ “የቁርጥ ቀን ልጅ” በሚፈለግበት እንዲህ ባለው ሁኔታ ቀርቶ፣ ቀላል በሚባሉት ጉዳዮችም “ይህን እኔ አልሰራም” የሚል ባለስልጣን ኢትዮጵያ አልነበራትም (ያማ ቢሆን ኖሮ፣ የተሸከምነው መከራ በግማሽ እንኳን በቀነሰልን ነበር)፡፡ እንዲያውም አቶ መለስ በአንድ ወቅት አቶ አያሌውን “አንተ የማትጠቅም፣ የማትጎዳም ነህ” ብለው በመተቸታቸው በድርጅቱ ትልልቆቹ አባላት ውስጥ ዜናው በስፋት ተናፍሶ ነበር፡፡ ባጭሩ አቶ አያሌው “እምቢ” የማለት ወኔው የላቸውም፡፡ (በሱዳኑ ፊርማ ላይ አቶ ደመቀ መኮንን እንዲሳተፉ የተደረገው፣ ሙስሊም ስለሆኑ/ኢስላማዊ ዳራ ስላላቸው የሱዳኖችን ስነልቦና “ለመግዛት” ኢህአዴግ የቀየሰው ስልት ከመሆን አይዘልም፣ ወደ አንዳንድ አረብ አገራት ዲፕሎማቶችን ሲመድብ ተመሳሳይ መንገድ ስለሚከተል፡፡)
እና አቶ አያሌው ለምን ከፕሬዝዳንትነታቸው እንዲነሱ ተደረገ? የአቶ አያሌው ከፕሬዝዳንትነት መነሳት ለብዙዎች ድንገታዊ ሊመስል ይችላል፤ አንደኛ አቶ አያሌው “የመተካካት መርሁ በ’ኔም ላይ ይተግበርልኝ” ብለው እንዲጠይቁና ይቺው ቃላቸውም ሳትጨመር-ሳትቀነስ በኢቲቪ እንድትተላለፍ ተደርጓል፡፡ ሁለተኛ “ከስልጣን አውርዱኝ” ጥያቆያቸውን ያየው ም/ቤት ጉዳዩን የተወያየበት በ“አስቸኳይ መደበኛ ስብሰባ” ነው፡፡ ሆኖም ግን ሀቁ ሌላነው፡፡ (እነዚህ ግርግሮች ሌላው የድራማው አካል ናቸው)፡፡
አቶ አያሌውን ከፕሬዝዳንትነት የስልጣን ኮርቻ የማንሳቱ እቅድ የተዘረጋው ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር (አቶ መለስ) በነበሩበት ወቅት ነው፡፡ አቶ መለስ በመሩትና ባህር ዳር ላይ በተካሄደ የኢህአዴግ ስብሰባ ላይ አቶ አያሌ ተገምግመዋል፡፡ በዋናነት የቀረበባቸውና የተቀበሉት ክስም በክልሉ ባሉ የተለያዩ የስልጣን/የሹመት እርከኖች ላይ የራሳቸውን አካባቢ ሰዎች እጅግ በተደራጀ መንገድ ማሰባሰባቸው ነው፡፡ አንዳንዶች ሂደቱን “ጎጃማይዜሽን” ይሉታል፤ ሌሎች ደግሞ “ማርቆሳይዜሽን” በማለት ይጠሩታል፡፡
አቶ አያሌው ሹመት የሚሰጡበት ቀመር በጣም ግልፅ ነው፡፡ እሳቸው ከመጡበት ከደብረ ማርቆስና አካባቢው የተማረ ከተገኘ ያለ ምንም ጥርጥር ይሾማል፡፡ ማርቆሴ እያለ ሌላ ሰው በምንም ሁኔታ አይሾምም፡፡ ማርቆሴ ከጠፋ፣ የአቶ አያሌው ሁለተኛው የሹመት ቀመር ስራ ላይ ይውላል፤ ጎጃሜ የሆነ ሰው ተፈልጎ ይሾማል፡፡ ማርቆሴ ሁሉ ጎጃሜ ቢሆንም፣ ጎጃሜ ሁሉ ግን ማርቆሴ አይደለም፡፡ ሆኖም ማርቆሴ ያልሆነ ጎጃሜን መሾም፣ ጎንደሬን፣ ወሎዬን ወይም የሰሜን ሸዋ ሰው ከመሾም እጅግ የተሻለ ነው፤ ምክንያቱም ጎንደሬም፣ የሸዋ ሰውም ሆነ ወሎዬ መቼም ቢሆን ጎጃሜ አይደለምና፡፡ ይህ የአቶ አያሌው የሹመት ቀመር ከስልጣን በሚወርዲት ላይም ስራ ላይ ይውላል፤ ባብዛኛው ከስልጣን የሚወርድ ተሿሚ ማርቆሴ ወይም ጎጃሜ አይደለም፤ ባጋጣሚ ነገሩ ከፍቶ ከስልጣን ከተነሳም ወይ የተሻለ ቦታ ይሰጠዋል፤ ካልሆነም በያዘው ደረጃና ደመወዝ የአቶ አያሌው አማካሪ ሆኖ ይሾማል (ፉገራ በሚወዱ ካድሬዎች አነጋገር Recycle Bin ውስጥ ይገባል፡፡ ይህ ማለት እንደ ገና የሚሾምበት ጊዜ አለ ማለት ነው፤ አቶ አያሌው ማዘናጋት የሚገባቸውን ካዘናጉ በኋላ፡፡ የቀመሩን ዘረኝነት (racist) ልብ ይሏል፡፡)
ይህም በመሆኑ አሁን በአማራ ክልል ርእሰ ከተማ -በባህር ዳር- ብዙዎቹን የመንግስት ተቋማት የሚመሩት ባለስልጣኖችና ምክትሎቻቸው፣ ዝቅ ሲልም የምክትሎቹ ምክትሎች (ፕሮሰስ ኦውነር፣ መምሪያ ሀላፊ፣ ወዘተ) በዚህ የአቶ አያሌው የሹመት አሰጣጥ ቀመር ወደ ስልጣን የመጡ ናቸው፡፡ ይህ የአቶ አያሌ የሹመት ቀመር በቀጥታ በማይመሩት በባህር ዩኒቨርስቲ ጭምር ስራ ላይ እየዋለ እንደ ሆነ ይነገራል፤ ዩኒቨርስቲው በፌደራል ትምህርት ሚኒስቴር የሚመራና ያሉት መምህራንም ከአገሪቱ ብሄር ብሄረሰቦች የተገኙ ሆነው እያለ፤ የፕሬዝዳንት፣ ምክትል ፕሬዝዳንቶችና ዲን ስልጣን (ወረድ ሲልም ከፕሮግራም ሀላፊ) በአብዛኛው በመጀመሪያ ደረጃ በማርቆሴዎች፣ ከዚያም በጎጃሜዎች “ቡድን” እንዲያዝ ተደርጓል፡፡ የአቶ አያሌው የጎጠኝነትና የዘረኝነት እጅ ይሄን ያህል ረጅም ነው፡፡
ይህ ድርጊታቸው ማለትም ክልሉን የጎጠኞች አምባ ማድረጋቸው አቶ አያሌውን ክፉኛ አስገምግሟቸዋል – በአቶ መለስና በሌሎቹም የኢህአዴግ ቁንጮ አባላት፡፡ ሆኖም አቶ መለስ በሀይል የወቀሷቸውን፣ የሰደቧቸውን፣ ያንቋሸሿቸውን ያህል አቶ አያሌውን ሮጥ ብለው ከስልጥን ማንሳት አልሆነላቸውም፡፡ በአቶ አያሌው ድርጊት “የበገኑትን” ያህል የይስሙላውን የአማራ ክልል ም/ቤት አስቸኳይ መደበኛ ስብሰባ አስጠርተው ግለሰቡን ከፕሬዝዳንትነታቸው በማስወረድ “የትምህን ግባ” ማለት አልቻሉም፡፡ ያን የመሰለ ባለ ራእይ መሪ ይህን ማድረግ ለምን ተሳነው?
ምክንያቱ ግልፅ ነው፡፡ አቶ አያሌው ዙሪያቸውን ያሰለፉት የጎጥ ሀይል ቀላል አይደለም፡፡ ከላይኛው የክልል ካቢኔ ጀምሮ፣ የቢሮ ሀላፊዎች፣ ምክትሎቻቸው፣ ከምክትሎቹ ስር ያሉ ሌሎች ሀላፊዎች ከ95 በመቶ በላይ ከፍ ሲል የተገለፀውን የአቶ አያሌውን የሹመት ቀመር ተከትለው የመጡ ናቸው፡፡ (እዚህ ላይ ከምክትል ቢሮ ሀላፊዎች በታች ባለ የስልጣን ሹመት ላይ አቶ አያሌ ቀጥተኛ ሚና የላቸውም፡፡ ሆኖም በሹመት ቀመራቸው ያመጧቸውን የራሳቸውን የወንዝ ልጆች በሳቸው ቀመር እንዲመሩ ማድረግ አይሳናቸውም፤ አድርገውታልም፤ ተገምግመውበታልም፡፡)
ስለሆነም አቶ አያሌውን በድንገት እንደ ሙጀሌ ፍንቅል ማድረግ አደጋ እንዳለው ኢህአዴግ አመነበት፡፡ እዚያ ክልል ላይ የሰፈረውን አብዛኛውን ባለስልጣን አስኮርፎ ክልሉን መምራት (እንደፈለጉ ማሽከርከር) እንደማይቻል ኢህአዴግ ልብ አለ፡፡ ምናልባት ቅሬታው ስር ሰዶ በተለይም ደብረ ማርቆስ ወደሚገኘው ህዝብ ሊደርስና ያልተፈለገ መነሳነሳት/ብጥብጥ ሊያስከትል እንደሚችል እነመለስ ሰጉ፡፡ ስለሆነም ግለሰቡን በረጅም ጊዜ ለማውረድ መስራት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ሆነ፡፡
እናም በክልሉ መስተዳድር መዋቅር ውስጥ የሌለ አደረጃጀት ኢህአዴግ ፈጠረና ከፕሬዝዳንቱ ሰር ሁለት ምክትሎች እንዲኖሩ ተደረገ፡፡ ሁለቱ ምክትሎችም በአቶ አያሌው ዙሪያ ካሰፈሰፉት የጎጥ ቡድኖች ውጭ እንዲሆኑ ተደረገ፤ አቶ አህመድ አብተውና አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ሁለት ምክትል ፕሬዝዳንቶች ሆነው ተሸሙ፤ ሁለቱም ከወሎ፡፡ ስለሆነም አቶ አያሌው የነበራቸው ያሹትን የማድረግ ስልጣን በእጅጉ ተገድበ፤ ባጭሩ ተንሳፈፉ፡፡
የተዘረጋውን ጠንካራ የማርቆሴ መዋቅርና የአቶ አያሌውን ተፅእኖ የማዳከሙ ስራ እንደ ተሳካ ሲታወቅ የይስሙላው የአማራ ክልል ም/ቤት ተጠራ፤ የይስሙላውን የአቶ አያሌው ዱላ ላቀብል የሚል ምክንያት አዳመጠ፤ አፅድቅ የተባለውን አፀደቀ፡፡ በቃ- የሆነው ይኼው ነው፡፡
በነገራችን ላይ ኢቲቪ በአንድ የዜና ስርጭት ላይ፣ የአቶ አያሌውን ከስልጣን መውረድ “ካረዳ” በኋላ፣ ወዲያው በማስከተል በሙሉ አምባሳደርነት መሾማቸውን “ማብሰሩ” ሰውዬው ከፕሬዝዳንትነት በመነሳቱ ቅር የሚላቸውን መገኖች (የማርቆሴ ቡድን) ስሜት ለማከም መሆኑን ልብ ይሏል፤ ኢህአዴግ እንዲህ ነው መፍራት ሲጀምር ልክ የለውም፣ መድፈር ሲያበዛ ልክ እንደሌለው ሁሉ፡፡
ሌላው ለአቶ አያሌው ከስልጣን መሳነት እንደ ተጨማሪ ምክንያት ሊቀርብ የሚችለው፣ የምስራቅ ጎጃም በተለይም በሞጣ የአዲስ አበባ መንገድ አቅጣጫ ያለው ህዝብ ተደጋጋሚ ቅሬታና አቤቱታ ነው፡፡ የአዲስአበባ-ሞጣ-ባህር ዳር የጠጠር መንገድ በአስፋልት እንዲሰራ የአካባቢው ህዝብ ለዘመናት ጠያቄ ሲያቅርብ ኖሯል፡፡ ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር – አቶ መለስ – ለህዝቡ ቃል የገቡ ቢሆነም እስካሁን ድረስ የመንገድ ስራው ሊጀመር አልቻለም፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋናው ተጠያቂ፣ የአካባቢው ህዝብ እንደሚናገረው፣ አቶ አያሌው ናቸው፤ “አቶ አያሌው በስልጣን እያለ የኛ መንገድ አይሰራም” በማለት ቅሬታቸውን በምሬት ይናገራሉ፡፡ በቅርቡ ሰላማዊ ሰልፍ ሁሉ ወጥተዋል፡፡ ግን አቶ አያሌው ለምን ችክ ብለው መንገድ ግንባታውን ያሰናክላሉ?
የአካባቢው ተወላጅ ምሁራን እንደሚሉት የሞጣው መንገድ መሰራት ከአዲስ አበባ-ባህር ዳር ያለውን ርቀት ቢያንስ በ70 ኪሎ ሜትር ስለሚያሳጥረው፣ በነባሩ መስመር ማለትም በቡሬ በኩል ባሉት ከተሞች ላይ ከፍተኛ የሆነ አሉታዊ ተፅኖ ይኖረዋል፤ ያለ ጥርጥር ብዙዎቹ ተሸከርካሪዎች በሞጣው መስመር ስለሚሄዱ የቡሬ መስመር ነጋዴዎች በተለይም ሆቴሎች ገቢ ትርጉም ባለው ሁኔታ ማሽቆልቆሉ አይቀሬ ነው፡፡ ደብረ ማርቆስ ያለችው ደግሞ በዚሁ የቡሬ መስመር ነው፡፡ አቶ አያሌው ደግሞ ከዚህች አካባቢ ምሁራን ብቻ ሳይሆን ከከተማዋ ጋር ያላቸው ፍቅር ወደር የለውም፡፡ እናም ለጎጣቸው ሲሉ የጎረቤታቸውን ጎጥ መልማት ሲከላከሉ ነው የኖሩት፡፡
እና ኢህአዴግ እኒህን ሰው ከስልጣን ማንሳት ይነሰው?

No comments:

Post a Comment