Saturday, January 11, 2014

የቀደምቶቹን ወንጀል ለማጋለጥ መቃብር ሲምስ የኖረው ወያኔ በራሱ ጦር ካምፕ ውስጥ የተገኘውን አስከሬን መደበቅ ለምን አሰፈለገው?

January 11, 2014
Ginbot 7 weekly editorialአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ፈረንሳይ ለጋሲዮን በሚገኘው የክብርዘበኛ ጦር ካምፕ ውስጥ ማንነታቸው ያልታወቁ የ6 ዜጎች አስከሬን ለመንገድ ሥራ በተሠማሩ ቆፋሪዎች አማካኝነት መገኘቱ የሰሞኑ አሳዛኝ ዜና ነው።
አንድ አይነት ቀለም ባላቸው ብርድ ልብሶች ተጠቅልለው ከተገኙ 6 አስከሬኖች የመጀመሪያዎቹ ሁለት ሰለባዎች ታስረውበት የነበረው የእጅ ሰንሰለታቸው እንኳ እንዳልወለቀና ከተቀሩት የአንዱ እጆች ደግሞ የፍጥኝ ወደ ኋላ እንደታሰሩ መገኘታችው ግድያው በቅርብ እንደተፈፀም አንዱ አስረጂ ነው።
በእንዲህ አይነት ጭካኔ የተገደሉ ዜጎች አስከሬን መገኘት በመንግሥት ተብየው አካል ካለመገለጹም በላይ ግቢውን በማስተዳደር ላይ የሚገኘው 3ኛ ክፈለ ጦርም ሆነ በግብር ከፋይ ገንዘብ የሚተዳደሩ መገናኛ ብዙሃን እስከዛሬ አንድም ቃል መተንፈስ አለመፈለጋቸው ጉዳዩን እጅግ የሚያሳዝን ብቻ ሳይሆን የሚያስገርምም አድርጎታል። ይባስ ተብሎም በመንገድ ሥራ ቁፋሮው የበለጠ አስከሬን ሊወጣ ይችላል በሚል ስጋት አካባቢው በፖሊስ እንዲታጠር ከተደረገ በኋላ ሥራውም እንዲቋረጥ ተደርጓል።
በፓለቲካ መስመር ልዩነት ምክንያት ደርግ ያለ ርህራሄ የጨፈጨፋቸውን ከመቃብር እያወጣ ዘመድ አዝማድ በማላቀስ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ሲዳክር የኖረ አገዛዝ በእንዲህ አይነት አሳዛኝ ሁኔታና አጋጣሚ የተገኘውን የጅምላ አስከሬን አይቶ አንዳላየ ለማለፍ መሞከሩ ለምን ይሆን?Mass grave found in Military camp in Addis Ababa
አብዛኛው የአዲስ አበባ ነዋሪ እንደሚያስታውሰው የክብር ዘበኛ ጦር ካምፕ በመባል የሚታወቀው የጃን ሜዳ 3ኛ ክፍለ ጦር ግቢ ድህረ ምርጫ 97 ወያኔ ለጅምላ እስር ቤትነት ከተጠቀመባቸው የማጎሪያ ቦታዎች አንዱ ነበር። ከዚያን ጊዜ በፊትና በኋላም ቢሆን ካምፑ በወያኔ ጠላትነት ተፈረጀ በጸጥታ ሠራተኞች ከታገቱ በኋላ አድራሻቸው እስከዛሬ ተሰውሮ ላሉ በርካቶች በምስጢር እስርቤትነት በማገልገል ላይ ከሚገኙ ወታደራዊ ካምፖች አንዱ እንደሆ ይታወቃል።
ዘመድ አዝማዶቻቸው ይመለሳሉ ብለው ሲጠብቋቸው ሳይመለሱ እንደወጡ የሚቀሩ በርካታ ዜጎች አሉ። በእንዲህ ሁኔታ ወጥተው ከቀሩ መካከል ከሰሞኑ የስድስቱ መቃብር በአጋጣሚ ተገኝቷል። የተገነዙበት ብርድ ልብስ ይነትብና ምንም ዓይነት ብልሽት ሳይደርስበት መገኝቱ ግዲያው በህወሃት ዘመነ መንግስት ስለመፈፀሙ ጥሩ ማስረጃ ነው። ለህወሃት ሰው መግደል ሥራ እንጂ ወንጀል አይደለም። በህወሃት ነፍሰ ገዳይ ይሞገሳል ይሾማል እንጂ አይወቀሰም አይጠየቅም። የስድስቱ ስዎች አስከሬን ሲገኝ መንግስትነኝ የሚለው ህወሃት አይቶ እንዳላየ መሆን ብቻ ሳይሆን ሌሎች አካላትም የሥፍራውን ሚስጢር እንዳያዩ ከልክሏል።በቁጥጥሩ ሥር ያሉ መገናኛ ብዙሃንም ዜናውን እንዳይናገሩ ታግደዋል። ህወሃት ከሚሰራቸው አስገራሚ ወንጀሎች መካከል አንዱይሄው ነው። ይሄ ግድያ በሌላ አካል ተፈፅሞ ቢሆን ኑሮ በረከት ስምዖንና እና ሺመልስ ከማል እየተፈራረቁ ያደነቁሩን ነበር።ይሄ የራሳቸው የእጅ ሥራነውና አይነገርም። የሄንንም የሚናገር እንደ ኢሳት ያለ ነፃ ሚዲያ ካለም ይታፈናል። አሸባሪም እየተባለ ይፈረጃል።
ግንቦት ሰባት የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ እነዚህ ዜጎች በህወሃት ተግድለው እንደተጣሉ ያምናል። ውሎ አድሮ እውነቱ እስከሚወጣ ድረስ ግን ዜጎች በሙሉ ይሄን ግድ በተመለከተ መረጃ የመሰብሰብና የማሰረጫት ሥራችውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ እናሳስባለን። ይሄን ወንጀል የፈፀሙ አካላት መጠየቅ አለባቸው። የዜጎች ደም እንዲሁ በከንቱ ፈሶ መቅረት የለበትም።
ለኢትዮጵያ ህዝብ መብትና ጥቅም እንታገላለን የሚሉ የፖለቲካና የስቪክ ድርጅቶች እንዲሁም ለሰው ልጆች የሰብአዊ መብት የሚሟገቱ ሁሉ የተገኘው አስከሬን በአስቸኳይ ተመርምሮ ማንነታቸው ለቤተሰቦቻቸውና ለወዳጅ ዘመዶቻቸው እንዲገለጽ፤ ተጨማሪ አስከሬን ሊገኝ ይችላል በሚልስጋት የመንገድ ቁፋሮውን ከሰዎች እይታውጪ ለማካሄድ እንዲቋረጥ የተደረገው ሥራ ለህዝብ እይታ ግልጽ በሆነመንገድ በአስቸኳይ እንዲጀመር የመጠየቅ ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ ግንቦት 7 ያሳስባል::
በዚህአጋጣሚ ወያኔ ሥልጣን ከተቆጣጠረበት ጊዜጀምሮ በሱማሌ፣ በጋምቤላ፣ በአዋሳ፣ በጎንደር፣ በአዲስ አበባና ሌሎች የአገራችን ክፍሎች በጠራራ ጸሃይ ካስጨፈጨፋቸው በተጨማሪ በፖለቲካ እምነታቸው ምክንያት ታግተው በየእሥርቤቱ የተወረወሩትንና ከታገቱበት ዕለት ጀምሮ እስከ ዛሬ የደረሱበት ያልታወቁ ወገኖቻችንን ዝርዝር በአስቸኳይ ያሳውቅ ብለን አንመክረውም።እኛ ግን ህወሃት የደበቀውን ወንጀል ሁሉ ህዝብ እንዲያውቀው ለማድረግ ያለምንም ማቅማማት ጠንክረን እየሰራን ነው። መንግስት ነኝ ብሎ በሥልጣን ላይ የሚወጣ ማንኛውም አካል የህዝብ አገልጋይ እንጂ ነፍሰገዳይ እንዳይሆን የጀመርነው ትግል ተጠናክሮ ይቀጥላል።
እንግዲህ ህወሃት በህዝባችንና በአገራችን ላይ የሚፈጽመውን ሰቆቃ ለማስቆም ግንቦት 7 የጀመረውን የነጻነት ትግል አጠናክሮ እንደሚቀጥል እያስታወቅን እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ እንዲህ በየቦታው ተገድሎ ከመጣል ራሱን ለመታደግ ሲል የነፃነቱ ትግል አካል እንዲሆን ጥሪያችንን አሁንም ደግመን እናቀርባለን::

http://ecadforum.com/
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !!

No comments:

Post a Comment