Saturday, January 4, 2014

ከቃሊቲ ዉጭ ሌላ ቃሊቲ


2665272d78511e341383257989January 4, 2014
ወያኔ የጫካ ዉስጥ ኑሮ በቃኝ ብሎ አዲስ አበባን ከረገጠ በኋላ ኢትዮጵያ ዉስጥ ብዙ አዳዲስ ቃላት ተፈጥረዋል፤ አንዳንድ አብረናቸዉ ያደግናቸዉ ቃላትና የቦታ ስሞች ደግሞ እየፋፉ መጥተዉ የሌሎች ሰፋ ያሉ ሀሳቦች መግለጫ ሆነዋል። ለምሳሌ የዛሬ ሃያ አምስት አመት ኮሌጅ የጨረሰ ልጅ አባቱን ቃሊቲ መግባቴ ነዉ ብሎ ቢነግረዉ አባቱ . . . . ምንዉ ስራ አገኘህ እንዴ ብሎ ከመጠየቅ ዉጭ በልጁ አባባል በፍጹም አይደነግጥም። ዛሬ ግን “ዕድሜ ለወያኔ” ቃሊቲ ሲባል የማይደነግጥ ኢትዮጵያዊ የለም። በፋብሪካ ማዕከልነቷ ትታወቅ የነበረችዉ ቃሊቲ ዛሬ አጥሩ ዉስጥ ወያኔ አፍኖ የከተታቸዉ ሰላማዊ ዜጎች ከአጥሩ ዉጭ ደግሞ የእነዚሁ ሰላማዊ ዜጎች ቤተሰቦች የሚተራመሱበት የጭንቅና የመከራ አምባ ሆናለች። አዎ ቃሊቲ እንደ አልባኒያዋ ቡሪልና እንደ ሩሲያዋ ሳይቤሪያ ዜጎችን ለማፈንና በዜጎች ላይ ሰቆቃ ለመፈጸም ሆን ተብላ እንደገና የተፈጠረችና አለፍላጎቷ አስቀያሚ ገጽታ የተከናነበች ከተማ ሆናለች። ቃሊቲ ታሪክ ከክፋታቸዉና ከጭካኔያቸዉ ዉጭ በፍጹም የማያስታዉሳቸዉን የሩሲያዉን ጆሴፍ ስታሊንና የአልባኒያዉን ኤንቨር ሆዣን እኛ ኢትዮጵያዉያን አለዝምድናችን በግድ እንድናስታዉሳቸዉ የተገደድንባት የአምባገነንነት ተምሳሌት ናት። የሚገረመዉ ቃሊቲ ወያኔ ተሸክሞ ካመጠልን የጆሴፍ ስታሊንና ኢንቨር ሆዣ መንታ ትዝታዎች አንዷ ናት። ጆሴፍ ስታሊንና ኢንቨር ሆዣ የሩሲያንና የአልባኒያን ህዝብ እስር ቤት ዉስጥ ብቻ አልነበረም ያሰሩት፤ አንድ ለአምስት በሚሉት ማለቂያ በሌለዉ ሰንሰለታቸዉ በመኖሪያ ቤቱ ዉስጥ፤ በሚሰራበት ፋብሪካ ዉስጥ፤ በሚማርበት ት/ቤቶች ዉስጥና በተደራጀበት ገበሬ ማህበር ዉስጥ ጭምር ጭምድድ አድርገዉ አስረዉታል።
የኢትዮጵያን ህዝብ የሚረገጡትንና እንደ እንስሳ እየታሰሩ የሚገረፉበትን መንገድ ለማወቅና ልምድ ለመቅሰም አልባኒያ ድረስ የሄዱት ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች ከአልባኒያ ይዘዉብን የመጡት ቃሊቲን ብቻ አይደለም፤ ከቃሊቲ ዉጭ ህዝብን በሰንሰለት ማስር የሚያስችላቸዉን “አንድ ለአምስት” አደረጃትም ይዘዉ መጥተዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ተግባራዊ አድርገዋል። አንድ ለአምስት ወያኔ ምንም ይበለዉ ምን በግንብና በሽቦ አጥር ያልታጠረ ሰፊ እስር ቤት ነዉ፤ ወይም አንድ ለአምስት – ከቃሊቲ ዉጭ የሚገኝ ሌላ ቃሊቲ ነዉ። ወያኔ የኢትዮጵያን ህዝብ በአንድ ለአምስት ሰንሰለት ማሰር ከጀመረ ቆይቷል። ዛሬ ወያኔ ይህንን የእነ ስታሊንን የመከራ ማራዘሚያ ገመድ ከገመደብን ከአመታት በኋላ “እንድ ለአምስትን” እንደገና ማንሳት የፈለግነዉ ጉዳዩ አዲስ ሆኖብን ሳይሆን ሁለት ነገሮች አሳስበዉን ነዉ፤ አንደኛዉ ወያኔ የ“እንድ ለአምስት” አደረጃጀትን የህብረተሰባችን መሰረት ወደ ሆነዉ ወደ ቤተሰብ ደራጃ ሲያወርደዉ በማየታችን ሲሆን፤ ሁለተኛዉ ደግሞ “እሾክን በእሾክ” እንዲሉ የኢትዮጵያ ህዝብ ከወያኔ ዘርኝነት፤ሰቆቃና ጭቆና ለመላቀቅ ወያኔ የፈጠረዉን አንድ ለአምስት አደረጃት በመሰላልነት ተጠቅሞ እራሱን እንዲያደራጅና ለወሳኙ ፍልሚያ እራሱን እንዲያዘጋጅ ለማሳሰብ ነዉ።
ወያኔ ነገረ ስራዉ ሁሉ ከጉልበትና ከሀይል ጋር የተያያዘ ነዉ፤ ስልጣን የያዘዉ በጠመንጃ ሀይል ነዉ፤ ስልጣን ላይ የቆየዉ በጠመንጃ ሀይል ነዉ። የኢትዮጵያን ህዝብ አንድ ለአምስት እያለ የሚያደራጀዉም በሀይል እያስገደደ ነዉ እንጂ የኢትዮጵያ ህዝብማ በወያኔ ስር መደራጀት ቀርቶ ወያኔ ድርጅቱ ብቻ ሳይሆን ወያኔ የሚባል ቃሉ እራሱ ከምድረ ኢትዮጵያ ቢጠፋ ደስታዉን አይችለዉም። የሚገርመዉ ወያኔ በዚያ ጠመንጃ በጨበጠበት እጁ የጻፈዉ ህገ መንግስት አንቀጽ 31 ማንኛዉም ሰዉ ለማንኛዉም አላማ በማህበር የመደራጀት መብት አለዉ ይላል፤ ሆኖም ይህ ህገመንግስታዊ መብት ለይስሙላ የተቀመጠ የባዶ ቃላት ክምር ነዉ እንጂ ኢትዮጵያ ዉስጥ ህዝብ በራሱ ፈቃድ መደራጀትም አለመደራጀትም አይችልም። ለመሆኑ ወያኔ በፍጹም በማይመለከተዉ በቤተሰብ ጉዳይ ጣልቃ የሚገባዉ ለምንድነዉ? እኛስ ኢትዮጵያዉያን ይህንን የወያኔ ጣልቃ ገብነት እንዴት አድርገን ነዉ እራሳችንን ነጻ ለማዉጣት የምንጠቀምበት?
በቅርቡ የቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ለወረዳ ሁለት የላከዉን የቤተሰብ ማቋቋሚያ ቅጽ አስመልክቶ በሰጠዉ ተጨማሪ ማብራሪያ የቤተሰብ ፖሊስ መመስረት አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሶ በቤተሰብ መካካል ለሚፈጠሩ አለመግባባቶችና ማህበራዊ ችግሮች መፍትሄዉ ቤተሰብን አንድ ለአምስት ማደራጀት እንደሆነ ተናግሯል። ባለፈዉ ሳምንት አጋማሽ ላይ የወያኔ ባለስልጣኖች በዳግማዊ ሚኒልክ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ዉስጥ ከየትምህርት ቤቱ ለተሰባሰቡ ርዕሰ መምህራንና ሱፐርቫይዘሮች አዲሱን አደረጃጀት አስመልክተዉ በሰጡት መግለጫ በቅርቡ ወደ ሁሉም ትምህርት ቤቶች ይወርዳል ብለዉ ካሉት የኮማንድ ፖስት አደረጃጀት በተጨማሪ “ትራንስፎርሜሺን ፎረም” እና “የልማት ቡድን” የሚባሉ አደረጃጀቶችም እንዳሉ ለማወቅ ተችሏል። የወያኔ ዘረኞች ስም እየቀያየሩ ኮማንድ ፖስት አሉት፤ “ትራንስፎርሜሺን ፎረም” ወይም “የልማት ቡድን” የሁሉም አደረጃጀት ተቀዳሚ ተግባር “አንድ ለአምስት” ተብሎ የተጀመረዉን አደረጃጀት ለማጠናከርና ለማስቀጠል ነዉ።
የኢትዮጵያ ህዝብ ይህንን ወይኔ ለራሱ እኩይ አላማ ሲል የጀመረዉንና ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል በማጠቃለል ላይ የሚገኘዉን የአንድ ለአምስት አደረጃጀት ወደ “ሚሊዮኖች ለሚሊዮኖች” አደረጀጃት በመቀየር ወያኔን እሱ እራሱ በፈጠረዉ ሰንሰለት ለማሰር ከአሁን የተሻለ ግዜ የሚያገኝ አይመስለንም። “አንድ ለአምስት” ከዛሬ በኋላ ወያኔ ኢትዮጵያዉያንን የሚሰልልበት ሳይሆን ኢትዮጵዉያን የወያኔን የስለላ መረብ የሚበጣጥሱበት፤ የማይተዋወቁ የትግል ጓደኞች የሚተዋወቁበት፤ ድርጅት የናፈቃቸዉ ኢትዮጵያዉያን እራሳቸዉን ከወያኔ አፈና ነጻ ለማዉጣት የሚደራጁበት የዝግጅት ቦታ መሆን አለበት። ወያኔ አንድ ለአምስት ያደራጀዉ የመንግሰት ሰራተኞችን፤ ተማሪዎችን፤ አርሶ አደሮችንና የከተማ ነዋሪዎችን እየነጣጠለ ለየብቻቸዉ ቢሆንም የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ይህንን ወያኔ የፈጠረለትን መድረክ በመጠቀምና የወያኔን የልዩነት ግድግዳ በመሰባበር አንድ ለአምስትን የመገናኛዉና የመደራጃዉ መድረክ ማድረግ አለበት።
ወያኔ ስፍር ቁጥር የሌለዉ የአደረጃጀት አይነቶች እያመጣ የኢትዮጵያን ህዝብ እንደ ቋጠሮ የሚቋጥረዉ እሱ ሊነግረን እንደሚፈልገዉ ለኢትዮጵያ ህዝብ ደህንነት ተጨንቆ ወይም ለአገርና ለህዝብ ሰላምና ዕድገት አስቦ አይደለም። ወያኔ ለህዘብ ሰላምና ደህንነት የሚያስብ ቢሆን ኖሮ ማድረግ ያለበት የኢትዮጵያን ህዝብ መብትና ነጻነት ማክበር እንጂ ኮማንድ ፖስትና አንድ ለአምስት እያለ ህዝብን በማይታይ ሰንሰለት ማሰር አይደለም። ኮሚኒስቶች ከግማሽ ምዕተ አመት በላይ ዜጎቻቸዉን ያሰቃዩበት “አንድ ለአምስት” አደራጃጀት አራት ሰዎች አንዱ በሌላዉ ላይ ስለላ እያካሄድ ለአምስተኛዉ ሰዉ መረጃ የሚያቀብሉበት ጓደኛን ከጓደኛ፤ ተማሪን ከአስተማሪ፤ አንዱን ሰራተኛ ከሌላዉ ሰራተኛ ጋር የሚያጋጭና በህብረተሰብ መካከከል መተማመን እንዳይኖር የሚያደርግ የስቃይ ሰንሰለት ነዉ። ወያኔ ይህንን የስቃይ ሰንሰለት በየቦታዉ ሲዘረጋ ከርሞ ዘንድሮ ካልጠፋ ቦታ ወደ ቤተሰብ ደረጃ እያወረደዉ ይገኛል። ፓርላማዉን ጨምሮ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ስልጣን፤ መከላከያዉን፤ ደህንነቱንና የአገሪቱን የኤኮኖሚ መዋቅር ሙሉ በሙሉ የሚቆጣጠረዉ ወያኔ ይህ ሁሉ አልበቃ ብሎት ፈጣሪ ለአባትና ለእናት የሰጠዉን ብቸኛ ሀላፊነት የራሱ ለማድረግ አንድ ለአምስትን በየቤተሰቡ ለመዘርጋት እየሞከረ ነዉ።
“ፈጣሪ ሊያጠፋዉ የፈለገዉን ያሳብደዋል” ተረት ወያኔን በትክክል የሚገልጸዉ የአባቶቻችን ተረት ነዉ። በእብደት ቢባል፤ በጭቆና፤በዘረኝነት፤ በትዕቢት፤ ወይም ህዝብን በመበደልና አገር በመበተን አገራችን ኢትዮጵያ ከወያኔ የባሰ እብድ በፍጹም ሊመጣባት አይችልም። ይህ ለይቶለት ያበደ ስርዐት የአንድ ለአምስት አደረጃጀትን ብቻ ሳይሆን ካሁን በኋላ የሚወስዳቸዉን ማንኛዉም አይነት እርምጃዎች የኢትዮጵያ ህዝብ እራሱን ከባርነት ነጻ ለማዉጣት መጠቀም መቻል አለበት። ወያኔ በጠመንጃ ሀይል ከቀማን መብቶች አንዱ የመደራጀት መብት ነዉ፤ ሆኖም ለራሱ በሚያመች መንገድ አንድ ለአምስት እያለ እያደራጀን ነዉ። የኢትዮጵያ ህዝብ ይህንን የወያኔን አንድ ለአምስት አደረጃጀት ተጠቅሞ እራሱን ለማደራጀትና ከወያኔ የአፈና ሰንሰለት ለመላቀቅ አመቺ አጋጣሚ ተፈጥሮለታል። ወጣቱ፤ገበሬዉ፤ሠራተኛዉ፤ አስተማሪዉና የከተማ ነዋሪዉ ማህበረሰብ የየራሱን የጎበዝ አለቆች እየመረጠ ወያኔን እራሱ በገመደዉ ገመድ ማሰር ካለበት ግዜዉ አሁን ነዉ።
ከፋሺስት ጣሊያን ወረረ አገራችንን ያዳኗት ጀግኖች አባቶቻችን መሪ የለንም ብለዉ ጠላትን ዝም ብለዉ አልተመለከቱም። እነ በላይ ዘለቀ፤ አብዲሳ አጋና ጃገማ ኬሎ የጎበዝ አለቃ መርጠዉ እራሳቸዉን አደራጅተዉ ነዉ አገራችንን ከአደጋ ያዳኗት። በአምስቱ የትግልና የአርበኝነት ዘመን በትጥቅ፤ በቁሳቁስና በዘመናዊነት የሚበልጣቸዉን የፋሺስት ጣሊያን ጦር አሳፍረዉ ወደመጣበት የመለሱት አባቶቻችን ለድል የበቁት ፋሺስት ጣሊያን በፈጠረዉ የድርጅት መዋቅር ዉስጥ እራሳቸዉን አደራጅተዉ ነዉ። አብዲሳ አጋ ጣሊያንን ያርበደበደዉ በጣሊያን ተራሮችና በረሃዎች ዉስጥ ነዉ። ዘርዓይ ደረስ የጣሊያኖችን አንገት የቀላዉ በሮም አደባባዮች ዉሰጥ ነዉ። ዛሬ በወያኔ ጥቁር ፋሺስቶች እየተገዛ ቁም ስቅሉን የሚያየዉ ኢትዮጵያዊ የእነዚህ ጀግኖች የልጅ ልጅ ነዉና የአባቶቹን ታሪክ በመድገም ወያኔ በፈጠራቸዉ ድርጅቶች ዉስጥ እየተደራጀ እራሱን፤ አገሩንና ወገኑን ነፃ ማዉጣት አለበት።
ወያኔን በህዝባዊ አመጽም ሆነ በህዝባዊ እምቢተኝነት ወይም በሁለቱም የትግል ስልቶች ታግሎ አገራችንን ነጻ ለማዉጣት ከዉጭ የሚመጣ ሀይል የለም፤ ነጻ አዉጪዉም በሚገኘዉ ነጻነት ተጠቃሚዉም ያለዉ እዚያዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ነዉ። ነፃነት ያለትግል ትግል ደግሞ ያለ ድርጅት በፍጹም የሚታሰቡ ነገሮች አይደሉም። ከአላማ ጽናት ቀጥሎ አንድ ህዝብ ነፃኑቱን እንዲጎናጸፍ የሚያስችለዉ ድርጅታዊ ብቃቱ ነዉ፤ ወያኔ የኢትዮጵያ ህዝብ ከሱ ፈቃድና ፍላጎት ዉጭ እንዳይደራጅ አጥብቆ የሚታገለዉ ይህንን ሀቅ በሚገባ ስለሚረዳ ነዉ። ሆኖም የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነቱን ለመቀዳጀት መታገል ለመታገል ደግሞ ወያኔ ፈቀደም አልፈቀደ ህዝብ በመረጠዉና ይበጀኛል ብሎ ባሰበዉ መንገድ ሁሉ መደራጀት አለበት። የኢትዮጵያ ህዝብ በወያኔ ሰላዮችና ካድሬዎች ተከብቦ እንደሚኖር የታወቀ ነዉ፤ ሆኖም ይህንን ከበባ ጥሶ ለመዉጣት ወያኔ እራሱ ያመቻቸዉ መንገድ አለ፤ እሱም ከሰራተኛና ከገበሬዉ ተነስቶ ቤተሰብ ድረስ የወረደዉ የወያኔ “አንድ ለአምስት” አደረጃጀት መዋቅር ነዉ።
የኢትዮጵያ ህዝብ ባለፉት 35 አመታት በሁለት አምባገነን ስርዐቶች ዉስጥ አልፏልና ስለአምባገነኖችና ስለ አምባገነንነት ብዙ ልምድ አለዉ። ወያኔ የኢትዮጵያን ህዝብ አንድ ወጥ በሆነ ድርጅታዊ መዋቅር ዉስጥ የሚያደራጀዉ የህዝብን ስነ ልቦና ለመስበርና ህዝብ በፍርሀት ደመና ተዉጦ እየሰገደ እንዲኖር ለማድርግ ነዉ። የኢትዮጵያ ህዝብ ግን የወያኔን ማንነት በሚገባ የተረዳዉ ስለሆነ የተገነባ ሞራል ያለዉና በራሱ የሚተማመን ህዝብ ነዉ፤ ስለሆነም ወያኔ የፈጠረዉን የድርጅት ጋጋታ እራሱን ነፃ ለማዉጣት ይጠቀምበታል የሚል ሙሉ እምነት አለን። ያለፈቃዳቸዉና ያለ እምነታቸዉ በግዴታ በአንድ ለአምስት ከተደራጁ ሰዎች ከአስር ዘጠኙ ወያኔን የሚቃወሙና የወያኔን ስርዐት ለማፍረስ የሚታገሉ ሰዎች ናቸዉ። እነዚህ ሰዎች ወያኔ ለስለላና ለጭቆና ያዋቀረውን የ“አንድ ለአምስት” አደረጃጀት ወያኔን እራሱን ለመታገልና ብሎም ለማዳከም እንደ መሣሪያ ተጠቅመዉ ይህንን አስከፊ ስርዐት ከጀርባቸዉ ላይ አንከባልለዉ መጣል አለባቸዉ።

No comments:

Post a Comment