Wednesday, January 15, 2014

ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የመሠረቱት ክስ


ከ7 ሳምንት በፊት ነበር ሶስት ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የቤልጄምን ጦር ኃይል በፍርድ ቤት የከሰሱት። ይህም እኢአ በ2011 መጋቢት ወር ከሊቢያ ትሪፖሊ 72 ሰዎችን አሳፍራ ወደ ላምፔዱዛ ስትጓዝ የነበረች አንዲት ጀልባ የማዕበል አደጋ ከደረሰባት በኋላ በአካባቢዉ ከነበሩ ኃይሎች ርዳታ ባለማግኘታቸዉ ነው።
defae
ወቅቱ የሊቢያ አብዮት ነበር። ሰዎች ከቤታቸው መውጣት የሚፈሩበት እና በየጎዳናው ቀን እና ሌሊት የጥይት ድምፅ የሚሰማበት። በዚህ ወቅትም በርካታ ሊቢያውያን እና በሀገሪቱ ይኖሩ የነበሩ የውጭ ሀገር ዜጎች ተሰደዋል። አቶ አቡ ከሌሎች እሳቸው እንደሚሉት 47 ኢትዮጵያውያን ፣ በርካታ ኤርትራዊያን እና ሌሎች አፍሪቃውያን ጋር ገንዘብ ከፍለው በጀልባ የሸሹት ወደ ላምፔዱዛ ኢጣሊያ ነበር። ይሁንና የፈለጉበት ሳይደርሱ ባህር ላይ የጠበቃቸው የ15 ቀን ሰቆቃ ነበር። ጉዞዋቸው ለምን እንደስተጓጓለ እና ጉዳያቸው ለምን በፍርድ ቤት እንዲታይ እንደወሰኑ በዚህ መርከብ ተሳፍረው የተረፉ እና ከከሳሶቹ አንዱ የሆኑት ኢትዮጵያዊ አቶ አቡ ገጠመኛቸውን መለስ ብለው ያስታውሱናል።
አቶ አቡ እንደሚሉት የገጠማቸው ማዕበል አደገኛ ስለነበር በስልክ የርዳታ ጥሪ ካደረጉ በኋላ አንድ ሄሊኮብተር መጥታ ውሃ እና ብስኩት ከሰጠቻቸው በኋላ ሄሊኮፕተሯ እንደሚመለስ ምልዕክት ሰጥቶዋቸው ተመልሳለች። ይሁንና ውሃ የአቀበላቻቸውም ሄሊኮፕተር ትሁን በጎናቸው የሚያልፉ መርከቦች ከዛን ሰዓት በኋላ አልደረሱላቸውም። ከዚህም በተጨማሪ የጀልባቸው ነጂ በመደናገጥ አቅጣጫ መምሪያውን ውሃ ውስጥ በመጣሉ እና አቶ አቡ እንደሚሉት ጀልባዋ ነዳጅ በመጨረሷ ቀጥለው ለመንዳት አልቻሉም። በወቅቱ ያላቸው ብቸኛ አማራጭ፤ ባሉበት መቆየት ብቻ ነበር። የዛኑ ሌሊትም 3 ስደተኞች በማዕበሉ ተወስደው ባህር ሰምጠው ቀሩ። ይህ ብቻ አይደለም፤ 63ቱ ሲሞቱ በህይወት የተረፉት 9ኙ ብቻ ናቸው።
አቶ አቡ እና ሌሎቹ 2 ከሳሾች ጉዳይን የሚከታተሉት ለስደተኞች የሚሟገተዉ አጀንሲያ ሃበሻ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ አባ ሙሴ ዘርዓይ በቤልጄም ጦር ኃይል ላይ የቀረበውን ክስ አብራርተውልናል።
አባ ሙሴ እንዳሉትም በህይወት የተረፉት ስደተኞች ካሳ እንዲያገኙ ከመጠየቅ ባሻገር፤ ዳግም እንደዚህ ዓይነት ስህተት እንዳይፈጠር እና የሰብዓዊ መብቶች እንዳይጣሱ እንዲሁም እንደዚህ ዓይነት አጋጣሚዎች ሲከሰቱ ኃላፊነት የሚወስድ ተጠያቂ አካል በአውሮፓ ህብረት ደረጃ ተደንግጎ እንዲወጣ እንደሚጥሩ ገልፀውልናል።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሀመድ
Source/www.de.dw.com

No comments:

Post a Comment