Monday, January 6, 2014

የአቶ አያሌው ጎበዜ ስልጣን መልቀቅ ከድንበር ጋር የተያያዘ ነው ብሎ የአማራ ክልል ህዝብ እንደሚያስብ መንግስት ያስጠናው ጥናት አመለከተ



ታህሳስ ፳፰( ሃያ ስምንት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የመንግስት ኮሚኒኬሺን ጉዳዮች የህዝብ አስተያየት መረጃ ክፍል በቅርቡ ከስልጣናቸው በወረዱት አቶ አያሌው ጎበዜ እና አሁን በአስቸኳይ ጉባኤ በተተኩት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ላይ ባሰባሰበው የህዝብ አስተያየት እና ለመንግስት ባቀረበው የአሉታ እና አውንታ ትንታኔ እንደገለፀው የስልጣን መተካካቱ ዋና አላማ መንግስት በትግራይ እና በአማራ ክልሎች መካከል ያለውን የድንበር ውዝግብ ለማሳካት ይረዳው ዘንድ ያደረገው ነው ብሎ ህዝቡ እንደሚያስብ ተገልጿል።

በመረጃው መሰረትም አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በክልሉ ህዝብ ዘንድ ተቀባይነት የላቸውም። የህወሀትን ጉዳይ ብቻ የሚያስፈጽሙ ናቸው ብሎ ህዝቡ እንደሚያስብ ተገልጿል።

ከፕሬዚዳንቱ ሌላ የቀድሞው ምክትል ርዕሰ መሰተዳድር አቶ አህመድ አብተው በአሁኑ ስዓት የንግድ ሚኒስትር እና አቶ አለምነው መኮንን የብአዴን ጽ/ቤት ሃላፊ የህወሀት ታማኞች ተብለው ተፈርጀዋል። ሁለቱ ባለስልጣናት በስማቸው ከተገኙባቸው ሁለት ገልባጭ ኤሮትራክ መኪኖች ጋር በተያያዘ ቢገመገሙም ለህወሀት ባላቸው ታማኝነት ከስልጣናቸው አለመነሳታቸውን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ሰዎች ለኢሳት ገልጸዋል። መሪዎቹ በካቢኔ ግምገማ ወቅት ” በአመራር ብቃታችን ከቻይና ካምፓኒዎች በድጋፍ የተሰጡን መኪኖች ናቸው” በማለት መልስ መስጠታቸው ይታወቃል።

መስሪያ ቤቱ ባሰባሰበው መረጃ በአውንታዊነት የተሰጠ አስተያየት የለም ። አስተያየቱ ለመንግስት መረጃ ክፍል እና ለካቢኔው ቀርቦ ውይይት ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

No comments:

Post a Comment