Tuesday, January 14, 2014

በኦሮምያ ክልል ወረቀቶችን በትነዋል የተባሉ ተማሪዎች ታሰሩ



ጥር ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የአፍሪካ ቀንድ የሂውማን ራይትስ ሊግ ለኢሳት በላከው መግለጫ ከነሐሴ እስከ ታህሳስ ባለው ጊዜ ውስጥ የኦሮሞ ህዝብ ፌደራሊስት ኮንግረስ አባላት ናቸው የተባሉ 45 ሰዎች በጉጂ ዞን በነገሌ እስር ቤት ውስጥ ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ ታስረው ይገኛሉ። ከታሰሩት መካከልም የሁለተኛ ደረጃ፣ የኮሌጅና የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችና መምህራን ይገኙበታል።

በጉጂ ወረዳ በሀርኬሎ ከተማ የሚኖሩ 8 የኮሌጅ ተማሪዎች የጉጂ ኦሮሞዎች መብት እንዲከበር የሚጠይቁ በራሪ ወረቀቶችን በከተማዋ ውስጥ በመበተናቸው መታሰራቸውን የገለጸው ሊጉ፣ ጎበና ገመዳ የተባሉትን የሁለተኛ ደረጃ መምህር ጨምሮ ጋልጋሎ ጩሉኬ፣ ኮራራዩ ካንክ፣ ኢጀርሳ ሻቆ፣ ናኖ ቻማሪ እና ዙሜ ሻንቆ እስከዛሬ በእስር ላይ ይገኛሉ።
በቡሌ ሆራ ዞን በአዶላ ፖሊስ ጣቢያ ደግሞ የኦሮሞ ፌደራሊስ ኮንግረስ አባላት የሆኑት የፓርላማ አባሉ ቦረና ጃኖ፣ ፣ ሂርባየ ጋልጋሎ እና ኡቱራ አዱላ ካለፉት 3 ወራት ጀምሮ ታስረው ይገኛሉ።

የሰብአዊ መብት ሊጉ መንግስትና አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድርጅቶች ለችግሩ ትኩረት በመስጠት ግለሰቦቹ እንዲፈቱ ጥረት እንዲያደርጉ ጠይቋል።

በተመሳሳይ ዜና ደግሞ በዳውሮ ዞን በማረቃ ወረዳ የዛሬ ዓመት ገደማ ከዲሳ ህዝብ የወረዳ ማዕከል ጥያቄ ጋር በተያያዘ ‘የህዝቡ የወረዳዉ ማዕከል አያማክለኝም ጥያቄ ተገቢ እና ወቅታዊ በመሆኑ መፍትሔ ሊሰጠዉ ይገባል’ በማለት በገሳ ከተማ ላይ በተደረገዉ የሎማ ወረዳ የ መንግሥት ሠራተኞች ስብሰባ ላይ በመናገራቸው ምክንያት የ3 ዓመት ከ6 ወር እስራት የተፈረደባቸው በዳዉሮ ዞን ታርጫ ማረሚያ ተቋም የእስራት ጊዜያቸውን ሲከታተሉ የነበሩት ሳጂን ሽታዬ ወርቁ በታሰሩት ማረሚያ ቤት ሊገኙ አለመቻላቸውን ቤተሰቦቻቸው ተናግረዋል፡፡
ሳጂን ሽታየ በእስር ቤት በከፍተኛ ሁኔታ በመደብደባቸው ራሳቸውን ለሁለት ቀናት ያህል ስተው እንደነበር ቤተሰቦቻቸው ተናግረዋል።

የሳጂን ሽታዬ ወርቁ የቅርብ ዘመዶች እንደገለጹት ግለሰቡ ‘በታርጫ ማረሚያ ተቋም መታረም ስለማይችል ወደ ጋሞ ጎፋ ዞን ሳዉላ ማረሚያ ተቋም በዝዉዉር ተልኳል ቢባልም፣ ሳዉላ እስር ቤት ውስጥ ሊያገኙዋቸው ባለመቻላቸው ግለሰቡ በህይወት ይኑሩ አይኑረ ለማወቅ መቸገራቸውን በጭንቀት ገልጸዋል፡፡

የሎማ ዲሳ ህዝብ የወረዳ ማዕከል ጥያቄ እስከዛሬ ድረስ ምላሽ ያላገኘ ጉዳይ ከመሆኑም በላይ ከጥያቄዉ ጋር በተያያዘ ከ30 የሚበልጡ የአካባቢዉ ተወላጆችና ሽማግሌዎች በተርጫ ማረሚያ ቤት ታስረዉ እንደሚገኙና በብዙ መቶ የሚቆጠሩ የአካባቢዉ ነዋሪዎች ቀዬአቸዉን ለቀዉ ተሰደዋል።

No comments:

Post a Comment