Wednesday, January 1, 2014

ስለ ዳግማዊ ምንሊክ የ” ኒዎርክ ታይምስ ” ጋዜጣ (ኅዳር 7/1909 ዓም እ ኤ አቆጣጠር) የዛሬ 96 አመት የፃፈው ፅሁፍ ለአሁኑ ትውልድ ታሪካዊ ማስረጃ ነው


09ኢትዮጵያ በየዘመኗ በሕልውናዋ ላይ የተቃጣባት የመበታተን አደጋን ያለፈችበት መንገድ የጦርነት መንገድ ብቻ አይደለም።ሆኖም ግን ከነበሩን የግጭት ታሪኮች በዘለለ በሕዝብ ዘንድ ተወዳጅ የነበሩ እና በሕዝብ ዘንድም የተወደዱ መሪዎች ነበሩን።ከእነኝህ ውስጥ ዳግማዊ ምንሊክ አንዱ ነበሩ። አፄ ምንሊክ ሀገር የማስተዳደር ጥበብን የተማሩት በአፄ ቴዎድሮስ እጅ ሆነው እድገታቸውን በንጉሡ ቤተመንግስት ማድረግ ከጀመሩበት ጊዜ ጀምሮ መሆኑን ብዙዎች ይስማማሉ።ንጉሡ የቀደሙ አባቶቻቸው አፄ ቴዎድሮስ እና አፄ ዮሐንስ ኢትዮጵያን አንድ የማድረግ አላማቸው እውን እንዲሆን ያደረጉ እድለኛ ንጉስም ናቸው።
አፄ ምንሊክ ኢትዮጵያን አንድ ከማድረግ አልፈው እስከ ኬንያ፣ሱዳን እና ሱማልያ ግዛት ድረስ ዘልቀው ገብተው በቅኝ ግዛት ይማቅቁ የነበሩ ህዝቦችን ነፃ ያወጣሉ የሚል ስጋት የነበረባቸው እና በወቅቱ በእነኚሁ የጎረቤት ሃገራት ላይ የጥቅም ፍላጎት የነበራቸው የአውሮፓ ሃገራት በብርቱ ተፈታትነዋቸው ነበር።
ዳግማዊ አፄ ምንሊክ ፎቶ
በመሆኑም አዲስ የድንበር ውል ከኢትዮጵያ ጋር የመፈራረም ፍላጎት ከእንግሊዝ፣ፈረንሳይ እና ኢጣልያ በኩል ጥያቄ መነጻቱን የወቅቱ የታሪክ ድርሳናት     ያወሳሉ።
ዛሬ ዛሬ በምንሊክ ላይ ታሪካዊ መሰረት የሌላቸው ቀድሞ አፄ ምንሊክ የቅኝ ግዛት ጥማታቸውን በገቱባቸው እና ቂም በያዙ ፀሐፊዎች የተፃፉ ናቸው ብለው ከሚነግሩን አስገራሚ ”የታሪክ” ፅሁፎች ውስጥ ”በምኒሊክ ዘመን እስከ አስር ሚልዮን ኦሮሞዎች አለቁ” የሚል ፅሁፍ በአንዳንድ የማህበራዊ ድህረ ገፆች ተለቀው ሲነበቡ መመልከት አስገራሚ የሰሞኑ ክስተት ነው።በፖለቲካው አለም በቂ ርዕዮተ አለምም ሆነ ፖለቲካዊ ፍልስፍና የጠፋባቸው አንዳንድ ወገኖች ”ትርፋማ” ብለው ያሰቡት የዘር ፖለቲካ በኢትዮጵያውያን መካከል መዝራት እና ከመቶ አመት በፊት የሆነውን የታሪክ ክስተት የአሁኑን ትውልድ በመውቀስ ትኩረት ለማግኘት ሲታትሩ መመልከት የዘመኑ አስቂኝ ተውኔት ነው።ዳግማዊ ምንሊክ ገና ብዙ የሚጠና ፖለቲካዊ፣ማኅበራዊ እና ወታደራዊ ክህሎት ባለቤት ለመሆናቸው በወቅቱ ከወጡት የዓለማችን ድንቅ ጋዜጦች አንዱ የ ኒውዮርክ ታይምስን እትም መመልከት ይበቃል።
ከእዚህ በታች በሚገኘው የኒውዮርክ ታይምስ ኅዳር 7/1909 ዓም እ ኤ አቆጣጠር እትም ላይ የኢትዮጵያ ጠቅላላ ሕዝብ ብዛትን 7,000,000 (ሰባት ሚልዮን) መሆኑን ያስቀምጣል። እዚህ ላይ አንዳንድ እራሳቸውን የታሪክ ምሁራን ነን በሚል ባልተጨበጠ ይልቁንም በምኒሊክ የቅኝ ግዛት ህልማቸው ከተደናቀፈባቸው ቂመኛ ፀሐፊዎች አነበብን የሚሉት እና የኦሮምኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያንን ያማለሉ መስሏቸው ”ምንሊክ 10 ሚልዮን ኦሮሞ ገደሉ” እያሉ ኢትዮጵያ ከነበራት የህዝብ ብዛት (7 ሚልዮን) በላይ ቁጥር ሲጠሩ እፍረት አልተሰማቸውም።
”ማን ያውራ የነበረ” እንዲሉ የኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ኅዳር 7/1909 ዓም እ ኤ አቆጣጠር እትም ላይ ጋዜጣው አዲስ አበባ በነበረ በልዩ ዘጋቢው አማካይነት ስለንጉሡ እና ኢትዮጵያ ፖለቲካዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ ሁኔታ ፅፎ ነበር።ጋዜጣው አፄ ምንሊክ እና አስተዳደራቸውን ከገለፀበት አረፍተ ነገር ውስጥ እነኝህ ይጠቀሳሉ -
– ኢትዮጵያን ወደ ህገመንግስታዊ የንጉሥ አስተዳደር ለመቀየር ሂደት ላይ መሆኗን፣
– የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት 7 ሚልዮን መሆኑን፣
– አፄ ምንሊክ ንጉሰ ነገስት ሲሆኑ ጦርነት የነበረው የአፄ ዮሐንስ ተተኪ እሳቸው መሆናቸውን ካልተቀበሉት ጋር ብቻ እንደ ነበር፣
– የአውሮፓውያንን ስልጣኔ ወደሀገራቸው ለማምጣት የባርያ ንግድን ከመዋጋታቸውም በላይ ነፃ ትምህርት ዕድል ዜጎች እንዲያገኙ መሰረት መጣላቸውን፣
– ምንሊክ እራሱ ልዩ ችሎታ ያላቸው ሰው መሆናቸውን። ከችሎታዎቻቸው መካከል ዲፕሎማት፣የፋይናንስ ባለሙያ እና ወታደር የሚሉት እንደሚጠቀሱ እና
– እንደ ዲፕሎማት እና ወታደር የጣልያንን ወረራ ኢትዮጵያ እንድታሸንፍ ያደረጉበት ጥበብ መሆኑን፣
የሚሉ ይገኙበታል።የጋዜጣውን ሙሉ ፅሁፍ ከእዚህ በታች ያለውን ሊንክ ከፍተው ያንብቡ።
የኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ኅዳር 7/1909 ዓም እ ኤ አቆጣጠር እትም ለማንበብ ይህንን ሊንክ ይክፈቱ።

No comments:

Post a Comment