Monday, December 9, 2013

የመንግስት ወሮበላ ሚልዮነሮች ወይ ቢልዮነሮች እነማን ናቸው?

የኢትዮጵያ ‘ሚልዮነሮች’!አብረሃ ደስታ

ከአንድ መቶ ዘጠኝ ሺ በላይ ዜጎች ወደ አንድ ሀገር የሚሰደዱባት ሀገረ ኢትዮጵያ ባለ ብዙ ሚልዮነሮች ሆነች አሉን። ወጣት ዜጎቻችን ስደት የሚመርጡበት ምክንያት ምንድነው? እውን መንግስት እንደሚለን ‘ቸግሯቸው ሳይሆን ባቋራጭ ለመበልፀግ ፈልገው ነው’? ወይስ የወላጆቻቸው የማዳበርያ ዕዳ ተሰደው ሰርተው ለመክፈል ነው?

ተመላሽ ስደተኞቹ ይዘዉት የመጡ ንብረት የኢትዮጵያ መንግስት እየነጠቃቸው መሆኑም ሰምቻለሁ። የኢትዮጵያ መንግስት ስደተኞቹ የሚቋቋሙበት ገንዘብ ይሰጣቸዋል ብለን ስንጠብቅ የያዙትን ንብረት መንጠቅ ምን ይባላል? ‘ዘረፋ’ ይባላል።
ብዙ ሚልዮነሮች እንዳሉን መነገሩ ሰምቻለሁ። እኔ ግን ቅሬታ አለኝ። ‘ሚሊዮነሮች’ የሚለውን ‘ቢልዮነሮች’ በሚል መቀየር አለበት። ምክንያቱም በኛ ሀገር ብዙ ሚልዮነሮች ብቻ ሳይሆኑ ብዙ ቢልዮነሮችም አሉ።
ነጥቡ ሚልዮነሮቹ ወይ ቢልዮነሮቹ እነማን ናቸው? ሃብቱ እንዴት አካበቱት? በትክክል የቢዝነስ ሰዎች ናቸው ወይ? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎች መመለስ ተገቢ ነው። ሚልዮነሮች ወይ ቢልዮነሮች እነማን መሆናቸው ቢታወቁ ባለስልጣናቱ ወይ የባለስልጣናት ቤተሰቦች መሆናቸው አይቀርም።
እንዴት ሚሊዮነሮች ሆኑ? ሰርተው ነው? ተወዳድረው ነው? አምርተው ነው? ኢንተርፕሪነሮች ስለሆኑ ነው? አይደሉም። የሃብታቸው ምንጭ ሙስናና ኮንትሮባንድ እንደሚሆን ነው የምገምተው። የቢልዮነሮቹ የሃብት ምንጭ በግብር መልክ ከድሃው ህዝብ የተሰበሰበ የመንግስት ገንዘብ ነው። በሙስና የአንድ መስራቤት ግዢ ጨረታ ያሸንፋሉ። ከዛ ሃብታም ይባላሉ። ከባለስልጣናቱ ጋር በመመካከር በኮንትሮባንድ ንግድ ይሰማራሉ። ሕጋዊ ነጋዴዎችን አዳክመው ሃብት ይሰበስባሉ። ከዛ ሃብታም ይባላሉ።
አብዛኞቹ ቢልዮነሮች በዓለም ዓቀፍ ገበያ ተወዳድረው አሸንፈው ያሰባሰቡት ሃብት አይደለም። ፍትሐዊ ባልሆነ መንገድ ከድሃው ሕብረተሰብ ያሰባሰቡት ነው። ስለዚህ ኢትዮጵያ ሚልዮነሮች ያሏት ሀገር ብትሆንም ለብዙ ዜጎች መዳረስ የነበረበት ሃብት በግለሰቦች እጅ ገብቷል ማለት ነው። ይህም ፍትሐዊ ያልሆነ የሃብት ክፍፍል አለ ማለት ነው። አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ድሃ እያለ የተወሰኑ ሚልዮነሮች ቢኖሩ ብዙ ትርጉም የሚሰጠው ጉዳይ አይደለም። ሁሉም ሚልዮነሮች ተመሳሳይ ናቸው ማለት ግን አይቻልም። ሰርተው የበለፀጉም ይኖራሉ።
ፍትሐዊ የሆነ የዉድ ድር ገብያ መሰረት ያደረገ የኢኮኖሚ ስርዓት በሌላት ሀገር ብዙ ሚልዮነሮች አሉን ብንባል ሚልዮነሮቹ ትክክለኛ የቢዝነስ ሰዎች ስለመሆናቸው እርግጠኛ መሆን ይከብዳል።

No comments:

Post a Comment