Wednesday, December 25, 2013

ለሕግ የበላይነት መከበር ትኩረት ይሰጥ!



አሁንም ለሕግ የበላይነት መከበር ትኩረት ይሰጥ!
የሕግ የበላይነት ባለበት ሰላም አለ፡፡ ዲሞክራሲ አለ፡፡ የሰብዓዊ መብት ጥበቃ አለ፡፡ ልማት አለ፡፡ ብልፅግና አለ፡፡

የሕግ የበላይነት በሌለበት ሰላም ፈጽሞ አይታሰብም፡፡ መረጋጋት አይኖርም፡፡ የሰው ልጅ መብት አይጠበቅም፡፡ ዲሞክራሲን ማሰብ አይቻልም፡፡ ልማትና ብልፅግና ሊኖሩ ይቅርና በሰላም ወጥቶ መግባት ከባድ ይሆናል፡፡ ዜጐች በሕግ የበላይነት ተማምነው እንዲኖሩ ሕግ ሊከበር ይገበዋል፡፡

በተደጋጋሚ እንደምንለው የሕግ የበላይነት ሲከበር ዜጐች በትክክል በሕግ ፊት እኩል መሆናቸውን ይረዳሉ፡፡ የሕግ የበላይነት በሌለበት ግን ዜጐች በሕግ ላይ ሊኖራቸው የሚገባው እምነት ይሸረሸራል፡፡ ሕገወጦች እየፈነጩ የሰውን መብት ሲጥሱና ዜጐችን ሲያሸማቅቁ የሕግ የበላይነት ጥያቄ ውስጥ ይወድቃል፡፡ በተለይ ዜጐች በሕግ የበላይነት መከበር የማይተማመኑ ከሆነ ችግሩ የከፋ ይሆናል፡፡

ብዙ ጊዜ የመልካም አስተዳደር ችግሮች ይነሳሉ፡፡ ለችግሮቹ መፍትሔ እንደሚፈለግም በተደጋጋሚ ይነገራል፡፡ የመልካም አስተዳደር ዋነኛ እንቅፋት የሕግ የበላይነት ያለመከበር መሆኑ ግን አይወሳም፡፡ ዜጐችን ያላግባብ የሚያንገላቱ፣ ተገቢውን አገልግሎት የማይሰጡ፣ የመብት ጥያቄ ሲቀርብ በአግባቡ የማያስተናግዱ፣ የሥልጣን የመጨረሻው አካል ሕዝብ መሆኑን የማይረዱ፣ በሙስና የተዘፈቁና ለአገርና ለወገን ደንታ የሌላቸው ለሕግ የበላይነትም ደንታ የላቸውም፡፡ ለሕዝብ ቆሜያለሁ፣ ተጠሪነቴም አገልግሎቴም ለሕዝብ ነው ብሎ የሚያስብ ግን ከምንም ነገር በላይ የሕግ የበላይነት እንዲከበር ሽንጡን ገትሮ ይሟገታል፡፡ ለተግባራዊነቱም አስፈላጊውን መስዋዕትነት ይከፍላል፡፡ የሕግ የበላይነት የዜጐች መተማመኛ ዋስትና እንዲሆንም ሌት ተቀን ይደክማል፡፡

የሕግ የበላይነት እንዲከበር እኛ ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ ኃላፊነት ያለብን ቢሆንም፣ በተለይ ደግሞ ሦስቱ መዋቅሮች ማለትም ሕግ አውጪው፣ ሕግ ተርጓሚውና አስፈጻሚው ታላቅ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ሕግ አውጪው ፓርላማ የሚያወጣቸው ሕጎች ሳይሸራረፉ ሥራ ላይ መዋላቸውን የመከታተል ትልቅ ኃላፊነት አለበት፡፡ ጥራት የጐደላቸው ለአገርና ለሕዝብ የማይጠቅሙ አንቀጾችን ያዘሉ ረቂቅ ሕጐች ሲቀርቡለት፣ ከሕዝብና ከአገር ጥቅም አንፃር እየመዘነ ጥራት ያላቸው ሕጐች እንዲወጡ ተገቢውን ሚና መጫወት ይኖርበታል፡፡ አገሪቱ ሕግ የሚከበርባት መሆኑን በተጨባጭ ማረጋገጥ አለበት፡፡

ሕግ ተርጓሚው አካል ሕሊናው በመራውና ሕግን መሠረት አድርጐ ለዜጐች ፍትሕ መስጠት አለበት፡፡ በተፅዕኖና ነፃነትን በሚጋፋ መንገድ የሚቀርቡ ክሶችን ውድቅ በማድረግ ዜጐች በፍትሕ ሥርዓቱ ላይ እንዲተማመኑ ሙያዊ ኃላፊነቱን ሊወጣ የግድ ይለዋል፡፡ የፍትሕ ሥርዓቱን ነፃነት የሚፈታተኑ ሕገወጥ ድርጊቶች የሕግ የበላይነትን የሚያዳክሙ በመሆናቸው የዳኝነቱ አካል ለፍትሕና ለርትዕ ሲል መሟገት ይኖርበታል፡፡ የፍትሕ ሥርዓቱ ነፀብራቅ የሆኑ ዳኞች ክብር ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ደኅንነታቸው መጠበቅ አለበት፡፡ እነሱ በተሻለ ሁኔታ በተራመዱ ቁጥር ውጤታቸው ጥሩ ይሆናል፡፡

ከአስፈጻሚ አካል ተፅዕኖ ሳይደርስባቸው ሙያቸውን በሚገባ ሊሠሩበት ይገባል፡፡ ከአድልኦና ከሙስና በራቁ ቁጥር የፍትሕ ተደራሽነት ይጨምራል፡፡ የፍትሕ ሥርዓቱ አካላት የሆኑት ፖሊስና ዓቃቤ ሕግ ሕዝብን የሚያገለግሉት በሕገ መንግሥቱ መሠረት እስከሆነ ድረስ ለሕግ የበላይነት ሊቆሙ ይገባቸዋል፡፡ የፍትሕ ሥርዓቱን የሚገዘግዙ ሕገወጦች በኃይል፣ በማስፈራራትና በገንዘብ ፍትሕን ሊያደናግሩ ሲሞክሩ የማስቆም ወይም ሕግ ፊት የማቅረብ ኃላፊነት አለባቸው፡፡

አስፈጻሚው አካል መንግሥትን እንደመምራቱ መጠን ለሕግ የበላይነት መከበር ትልቅ ድርሻ አለው፡፡ መንግሥት ሕገ መንግሥታዊው ሥርዓት በሰላማዊ መንገድ እየተመራ ዲሞክራሲ እንዲሰፍን፣ ሰብዓዊ መብት እንዲከበር፣ አገር እንዲለማ፣ ወዘተ   ለሕግ የበላይነት መከበር ዋነኛው ተዋናይ መሆን አለበት፡፡ በመንግሥት ውስጥ የተሸሸጉ ሕገወጦችና ግብረ አበሮቻቸው ሕዝቡን እያስለቀሱ የሕግ ልዕልናን ሲጋፉ እንዳላየ የሚያልፍ ከሆነ ወይም ካድበሰበሰ ተጠያቂነት ይኖርበታል፡፡ በፍትሕ ሥርዓቱ ላይ አመኔታ የሚያሳጡ ሕገወጥ ድርጊቶች በተደጋጋሚ ጊዜያት ሲፈጸሙ ዳተኝነት ይታያል፡፡ ይህ ዳተኝነት ደግሞ የአስፈጻሚውን አካል ደንታ ቢስነት ብቻ ሳይሆን ሥርዓቱ ለሕግ የበላይነት ያለውን ክብርና ደረጃ ቁልጭ አድርጐ ያሳያል፡፡ ዜጐች በሕግ ፊት እኩል ናቸው ሲባል ባለሥልጣናትንም ጭምር የሚያካትት በመሆኑ ለሕግ የበላይነት ትኩረት ሊሰጥ ይገባዋል፡፡ ሕግና ሥርዓት በሌለበት ድባብ ውስጥ የሚፈነጩት ሕገወጦችና ሙሰኞች ብቻ ናቸው፡፡ ስለልማት ሲታሰብ ቅድሚያ ለሕግ የበላይነት ይሰጥ፡፡ ሕዝብ በሕግ የበላይነት ጥላ ሥር መተዳደር እንዳለበት ግንዛቤ ይያዝ፡፡ የፍትሕ ሥርዓቱ ያለምንም ጣልቃ ገብነት እየተመራ ነው ሲባል ተግባራዊነቱ ሊረጋገጥ ይገባል፡፡ በንድፈ ሐሳብ ከሚባለው ይልቅ ተግባር ይበልጣልና፡፡

ሦስቱ አካላት እየተናበቡ በሕጋዊ መንገድ ተግባራቸውን ማከናቸወናቸውን የሚቆጣጠር አካል መኖር አለበት፡፡ በሠለጠነው ዓለም ይህ ተግባር የሚዲያው ቢሆንም፣ እንደ አለመታደል ሆኖ በአገራችን የሚዲያው ሚና ተፈላጊ አይደለም፡፡ ለሕግ የበላይነት መስፈን መሥራት የሚገባቸው ሚዲያዎች የሦስቱን መንግሥታዊ መዋቅሮች መናበብና የሕግ የበላይነት መከበሩን ለማረጋገጥ የሚያደርጉት ጥረት ሲመክን ይታያል፡፡ ይህ ችግር ጐልቶ የሚታየው ከአስፈጻሚው አካል በኩል ቢሆንም፣ ሚዲያው በውስጡ ባሉ የተለያዩ ችግሮች ምክንያት የተቆጣጣሪነት ሚናው ያነሰ ነው፡፡ የሲቪል ማኅበረሰቡ አቅም የጫጫ በመሆኑ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ እነዚህ እስኪጠናከሩ ድረስ የሦስቱን መዋቅሮች ተናቦ መሥራት ማረጋገጥ የግድ ይላል፡፡

አለን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ የሕግ የበላይነት ጉዳይ ይመለከተናል የሚሉ አካላት  በሙሉ ለተግባራዊነቱ መረባረብ አለባቸው፡፡ የሕግ የበላይነትን የሚያኮስሱ ድርጊቶች በየቦታው ስለሚታዩ ሕግ እንዲከበር ዜጐች በሙሉ ድምፃቸውን ማሰማት አለባቸው፡፡ በሕጋዊነት ሽፋን ሕገወጥ ተግባራት እየተፈጸሙ የሕግ የበላይነት ሲሸረሸር በአገር ላይ እንደተቃጣ አደጋ ሊሰማን ይገባል፡፡ የሕግ የበላይነት በሌለበት ሰላም፣ ዴሞክራሲ፣ ሰብዓዊ መብትና ብልፅግና አይኖሩም፡፡ የሕግ የበላይነት በሌለበት ስለመልካም አስተዳደርና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መነጋገር አይቻልም፡፡  የሕግ የበላይነት በሌለበት ስለአገር ፍቅር፣ መከባበር፣ መቻቻልና በሰላም አብሮ መኖር ማሰብ ከቶውኑም አይቻልም፡፡ የሕግ የበላይነት ሲኖር ግን ሁሉም ነገር ይኖራል፡፡ 

ስለዚህ ለሕግ የበላይነት መከበር ትኩረት ይሰጥ!

ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment