Sunday, December 22, 2013

ጉቦ በመቀበል እስረኞችን ፈተዋል የተባሉ የማረሚያ ቤት ሹሞች ታሰሩ

шаблоны RocketTheme
Форум вебмастеро-እስከ 500 ሺሕ ብር ሲቀበሉ እንደነበር ተጠቁሟል

ከአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት ከ40 ሺሕ ብር እስከ 500 ሺሕ ብር ድረስ ጉቦ በመቀበል፣ ከአምስት ዓመት በላይና በታች ተፈርዶባቸው በእስር ላይ የሚገኙ ታራሚዎችን በሐሰተኛ ሰነድ ከእስር እንዲፈቱ አድርገዋል በሚል የተጠረጠሩ ሦስት የማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎችና አምስት ግብረ አብሮቻቸው በቁጥጥር ሥር ዋሉ፡፡
የማረሚያ ቤቱ ሹሞች ኦፊሰር ገብረ መድህን አረጋ ደስታ፣ ረዳት ኦፊሰር ኢሳያስ ከበደ ገብረ ጻድቅና ዋርደር ኢብራሂም መሐመድ ሲሆኑ፣ ከውጭ ሆነው ድርጊቱን በማቀነባበር የተጠረጠሩት ደግሞ ሰለሞን ገለታ፣ ብሩክ ኃይሌ፣ ሳባ ገብረ ሚካኤል፣ ናታን ዘለዓለምና ቴዎድሮስ ግደይ የሚባሉ ናቸው፡፡ ሁሉም ተጠርጣሪዎች በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሁለተኛ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡ 
ሦስቱ የማረሚያ ቤቱ ተጠርጣሪ ሹሞች የእስረኞች አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች ሲሆኑ፣ በሐሰት የተዘጋጀና ከጠቅላይ ፍርድ ቤት የተሰጠ የእስረኛ መፍቻ የሚመስል ሐሰተኛ ሰነድ በመጠቀም፣ 11 ታራሚዎችን ከ40 ሺሕ እስከ 500 ሺሕ ብር በመቀበል ከእስር እንደፈቷቸው ዓቃቤ ሕግ ለፍርድ ቤት አስረድቷል፡፡ 
ሰለሞን ገለታ፣ ብሩክ ኃይሌና ናታን ዘለዓለም የተባሉት ተጠርጣሪዎች ቀደም ባሉት ጊዜያት ቅጣት ተወስኖባቸው በማረሚያ ቤት እንደቆዩና ጊዜያቸውን ጨርሰው የወጡ መሆናቸውን የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ለፍርድ ቤት አስረድቷል፡፡ 
ሰለሞን ገለታ፣ ብሩክ ኃይሌ፣ ናታን ዘለዓለምና ቴዎድሮስ ግደይ የእስር ጊዜያቸውን ጨርሰው ከወጡ በኋላ፣ በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተዘጋጀ የሚመስል የእስረኛ መፈቻ ቅጽ በማዘጋጀት ሳባ ገብረ ሚካኤል ለተባለችው ተጠርጣሪ በመስጠት በኮምፒዩተር ካሠሩ በኋላ፣ አመሳስለው ያስቀረፁትን ማሕተምና ፊርማ በማተም፣ ለማረሚያ ቤቱ ሹሞች እንደሚሰጡ የኮሚሽኑ መርማሪ ገልጿል፡፡ 
የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች ትዕዛዝና የእስር መፍቻው ሐሰተኛ ሰነድ የሚዘጋጀው ከአምስት ዓመት በታች ለተፈረደባቸው በ300 ሺሕ ብር፣ ከአምስት ዓመት በላይ ለተፈረደባቸው በ500 ሺሕ ብር እንደነበርና በቁጥጥር ሥር እስከዋሉበት ጊዜ ድረስ ከ11 በላይ ፍርደኞችን እንዲፈቱ ማድረጋቸውን መርማሪው ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ 
ሐሰተኛ ሰነዶቹን፣ ማሕተምና ቲተር በመያዝ ለፎረንሲክ ምርመራ መላኩን በመግለጽ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ እንዲሰጠው የ14 ቀናት ተጨማሪ ጊዜ ጠይቋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ የዋስትና መብት እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል፡፡
የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ተጠርጣሪዎቹ የጠየቁትን ዋስትና ተቃውሟል፡፡ ምክንያቱን ሲያስረዳ የሚያሰባስበው መረጃ እንዳለው በመግለጽ፣ በዋስ ቢለቀቁ ማስረጃ ያሸሻሉ የሚል ሥጋት አለኝ ብሏል፡፡ ፍርድ ቤቱ የተጠርጣሪዎቹን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ጊዜ ቀጠሮውን ፈቅዷል፡፡
ሌላው በተለይ ፍርደኞችን በሕገወጥ መንገድ ከማስለቀቅ ጋር በተያያዘ የፌዴራል ዳኞችና ፌዴራል ፖሊስ በጋራ ለመምከርና ለመወያየት ታኅሳስ 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ስብሰባ መቀመጣቸው ተጠቁሟል፡፡

source http://www.ethiopianreporter.

No comments:

Post a Comment