Tuesday, December 24, 2013

በቀብሪ ቤያህ እስር ቤት ውስጥ የሞቱ ሰዎች የሉም ሲል የክልሉ ፖሊስ አዛዥ አስተባበሉ



ታህሳስ ፲፫( አስራ ሦስት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የክልሉ ጽህፈት ቤት ፖሊስ አዛዥ ከጅጅጋ 25 ኪሜ ገደማ በምትገኘዋ ቀብሪበያህ እስር ቤት ውስጥ የሞቱ ሰዎች ስለመኖራቸው ሪፖርት እንዳልደረሰቻው ገልጸዋል።
አዛዡ እንዳሉት በክልሉ የሚንቀሳቀሱ ሽብረተኞችን በተመለከተ ከፌደራል መንገስቱ የጸረ ሽብር ግብረሀይል ጋር በጋራ የሚሰሩ በመሆኑ፣ በዚሁ ወንጀል ተጠርጥረው የሚያዙ ካሉ በጋራ የሚታይ ጉዳይ ይሆናል ሲሉ አክለዋል

በጅጅጋ የተከበረውን የብሄር ብሄረሰቦች በአል ምክንያት በማድረግ “መታወቂያ የላቸውም፣ የከተማዋን ገጽታ ያበላሻሉ፣ ከተማዋን ያቆሽሻሉ፣ የጸጥታ ስጋት ደቅነዋል በሚል ከ770 በላይ ሰዎች ቀብሪበያህ በሚባለው ወረዳ ውስጥ በአንድ ክፍል ውስጥ እንዲታሰሩ ከተደረጉት መካከል ከ40 በላይ የሚሆኑት መሞታቸውን ማንነታቸው እንዳይታገለጽ ከጠየቁ የክልሉ ባለስልጣናት ያገኘውን መረጃ በመንተራስ ዘገባ መስራታችን ይታወሳል።

እስረኞቹ የሞቱት በምግብ እጥረትና በእስር ቤቱ ውስጥ በተነሳ የታይፎይድ ( ተስቦ) በሽታ መሆኑን የዜናው ምንጮች ገልጸዋል። 
ዘመዶች የሞቱባቸውንና ለቅሶ የተቀመጡ ሰዎችን ኢሳት ለማነጋገር ቢሞክርም፣ ሰዎቹ ለደህንነታቸው በመስጋት ለመናገር ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።

ሰዎችን ከከተሞች በመውሰድ ያሰሩዋቸው በክልሉ ውስጥ የሚንቀሳቀሱት ልዩ ሚሊሺያ እየተባሉ የሚጠሩት ታጣቂዎች መሆናቸውን ምንጮች አክለው ገልጸዋል። ማንኛውም የሰብአዊ መብት ድርጅት በአካባቢው በመሄድ በቀላሉ ማረጋገጥ የሚችለው ሀቅ ነው በማለት የክልሉ ፖሊስ አዛዥ የሰጡትን ማስተባበያ ውድቅ አድርገዋል። ለሁለት ወራት ያክል ታስረው የነበሩት በተለያዩ ምክንያቶች የታሰሩ የከተማዋ ነዋሪዎች ባለፈው ሳምንት መለቀቃቸውን መዘገባችን ይታወሳል።

No comments:

Post a Comment