Sunday, December 29, 2013

የአኖሌ ሐውልት ጉዳይ … «አሣ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል» እንዳይሆን – (ሞረሽ ወገኔ)

የአኖሌ ሐውልት ጉዳይ … «አሣ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል» እንዳይሆን – (ሞረሽ ወገኔ) በቅርቡ የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ በሚቆጣጠረው የቴሌቪዥን ጣቢያ አንድ ዝግጅት ቀርቦ ነበር የዝግጅቱ ትኩረትም «የዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሠራዊት በአርሲ እናቶች ላይ በፈፀመው የጡት መቁረጥ ግፍ» መታሠቢያ የሆነ ሐውልት ስለመቆሙ ነበር። «ነገርን ከሥሩ ፣ ውኃን ከጥሩ» ይባላልና ለመሆኑ የዚህ አዲስ ሐውልት ባለቤቶች እነማን ናቸው? በሐውልቱስ መቆም ማን ምን ፋይዳ ያገኝበታል? ብሎ መጠየቁ ተገቢ ይሆናል። ከታሪክ እንደምንገነዘበው ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ኢትዮጵያ ካፈራቻቸው ነገሥታት ውስጥ እጅግ ከፍተኛ ታሪካዊ ተግባሮችን ያከናውኑ ከሚባሉት ጥቂቶች መካከል የሚመደቡ ናቸው። የኢትዮጵያን አንድነት በማጠናከር ረገድ ከአፄ አምደጽዮን ወዲህ የተነሡት ትልቁ አገር ገንቢ ናቸው። በዚህ አኳያ የላቀ ድርሻ ያላቸው ምናልባትም ከዚያ በፊት እነ አፄ ካሌብ እና አፄ ኢዛና (አብርሃ) ናቸው። ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ወደ ኢትዮጵያ በማስገባት ደረጃ ኮትኩተው ካሣደጓቸው ከዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ የላቀ ስኬት ለማስመዝገብ ብልህነቱም ሆነ መልካም አጋጣሚው ነበራቸው። ከሁሉም በላይ በጥቁር አፍሪቃ ብቻ ሣይሆን በዓለም ደረጃ «ደካማ» የሚባሉ የዓለማችን ዜጎች «ጠንካራ» በሚባሉት ቅኝ ገዢዎች ላይ አንፀባራቂ ድል ማስመዝገብ እንደሚችሉ እርሣቸው የመሩት የዐድዋው ድል ሕያው ምሥክር ነው። ስለዚህ እኒህን ሁሉ ታላላቅ ተግባሮች ባከናወኑ ንጉሠ ነገሥት ላይ ይህ ሁሉ ውርጅብኝ እና ስም ማጉደፍ በእነማን ፣ ለምን ተብሎ እንደሚካሄድ አብጠርጥሮ ማሣወቅ ያስፈልጋል። ለመሆኑ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ማን ነበሩ? ዳግማዊ አፄ ምኒልክ የሸዋው ንጉሥ የኃይለመለኮት ሣህለሥላሤ እና የወይዘሮ እጅጋየሁ ለማ አድያቦ ልጅ ናቸው። በአባታቸው ወገን ኢትዮጵያን ከቀዳማዊ ምኒልክ ጀምሮ ያስተዳደረው የሰለሞናዊው ሥርወ-መንግሥት ደም ያላቸው ሲሆን እናታቸው ደግሞ ከጉራጌ ነገድ የሚወለዱ ናቸው። በእናታቸውም ሆነ በአባታቸው ወገን ያለው ዝርዝር የትውልድ ሐረጋቸው በደንብ ቢጠና ከሁለት በላይ ከሆኑ ነገዶች ቅይጥ ዘር እንደሚኖራቸው እሙን ነው። በዚህ ጽሑፍ ደረጃ ለማስተላለፍ የሚፈለገው ሃቅ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ቢያንስ ከሁለት የኢትዮጵያ ነገዶች የተገኙ እንጂ የዘመኑ ዘባራቂዎች በሐሰት እንደሚደልዙት «የዐማራ ንጉሠ ነገሥት» አልነበሩም። እርሣቸውም በየትኛውም አጋጣሚ ራሣቸውን በእንደዚህ ዓይነት መጠሪያ ገልፀው አያውቁም። መቼም ሥልጣኔ ማለት ለሰው ልጅ መልካም ሕይዎት መደላደል የሚያስችሉ ቁሣዊ እና ኅሊናዊ ጉዳዮችን ማሟላት እንደሆነ ይታወቃል። ይህ ማለት በቁሣዊ መልኩ ሲታይ የራቀውን ማቅረብ፣ የከበደውን ማቅለል፣ የተራራቁትን ማቀራረብ፣ ጨለማውን ብርሃን ማድረግ፣ ሙቀቱን ማቀዝቀዝ፣ ቀዝቃዛውን ማሞቅ፣ አድካሚውን ማቃለል፣ የጠበበውን ማስፋት፣ ባንድ ቃል ተፈጥሮን መግራት እና ለሰው ልጅ ሁለንተናዊ ጥቅም ማዋል መገለጫዎቹ ናቸው። በኅሊናዊ መልኩ ደግሞ ክፋትን በደግነት፣ ጠላትነትን በወንድማማችነት፣ ቂምን በይቅርታ፣ ካለፈው መጪውን፣ የኋሊት ከማየት ወደፊት ማትኮርን፣ የሕይዎት መመሪያ ማድረግ ነው። ሠሞኑን ይህችን ዓለም በሞት የተሰናበቱት የቀድሞው የደቡብ አፍሪቃ መሪ ፕሬዘዳንት ኔልሰን ማንዴላ፣ የዓለምን የዜና አውታሮችን ትኩረት የሣቡት እና የዓለማችን ኃያላን መሪዎች በቀብር ሥነ-ሥርዓታቸው ላይ በብዛት ታድመው አድናቆታቸውን ለመግለጽ የተገደዱት፣ በአፓርታይድ አገዛዝ ለ፳፯ ዓመታት በመታሠራቸው አይደለም። ይልቁንስ ለአሣሪዎቻቸው ይቅርታ በማድረግ ራሣቸውን እና አሣሪዎቻቸውንም ጭምር ከኅሊና ተወቃሽነት ነፃ በማውጣታቸው፣ አልፎ ተርፎም ያለፈውን ክፉ ድርጊት ለታሪክ ትተው፣ ለወደፊቷ ደቡብ አፍሪቃ አንድነት ምቹ መሠረት በመጣላቸው ነው። እኒህ ተግባሮቻቸው ኔልሰን ማንዴላን የዘመናችን ታላቅ ሰው አድርገዋቸዋል። በተቃራኒው ግን በኢትዮጵያ ላይ የተጫኑ እና የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጉዳይ አስፈጻሚዎች የሆኑት ዘረኛ የትግሬ-ወያኔዎች የዘመናዊቲቱን ኢትዮጵያ መሥራች ዳግማዊ አፄ ምኒልክን ነጋ ጠባ ያወግዛሉ፣ ሥራዎቻቸውንም ያራክሣሉ። ሻቢያ ፣ የትግሬ-ወያኔ እና የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ኢትዮጵያውን ለዘመናት ይዘውት እና አስጠብቀውት የኖሩትን አንድነት በመናድ ሕዝቡን አገር-አልባ አድርገውታል። ከዚህም አልፈው ኢትዮጵያዊ ሁሉ ወደፊት ሣይሆን ወደ ኋላ እንዲያይ፣ እንዲሁም እርስ በርሱ ተናክሶ «ኢትዮጵያዊነት» የተሰኘ የዜግነት መታወቂያው እና «ኢትዮጵያ» የተባለችው አገሩ እንዳትኖር የሚያደርግ የልብ ወለድ ታሪክ በሐውልት መልክ አቁመው ትውልዱ እሳት እና ጭድ እንዲሆን እያደረጉት ይገኛሉ። ሻዕቢያ እና ወያኔ በትጥቅ ትግል ዘመናቸው ኢትዮጵያን ለመበታተን ላቀዱት ዓላማ እውን መሆን፣ በአገሪቱ ካሉት ነገዶች መካከል በቁጥር ከፍተኛ መጠን ያላቸውን ዐማራን እና ኦሮሞን እስከ ወዲያኛው እንዳይገናኙ ማድረግ ተቀዳሚ ተግባራቸው ነበር፣ ዛሬም ነው። ለዚህም ተግባር አስፈፃሚነት «ተስፋዬ ገብረአብ» በመባል የሚታወቀውን በኢትዮጵያ ተወልዶ ያደገውን ግለሰብ፣ የሁለቱ ነገዶች ልጆች ወደፊት ዐይን ለዐይን ሊተያዩ የማይችሉበትን ሥራ እንዲሠራ ወያኔና ሻዕቢያ መመሪያ ሰጡት። ተስፋዬ ገብረአብም በተሰጠው መመሪያ መሠረት «የቡርቃ ዝምታ» የተሰኘ ዳግማዊ አፄ ምኒልክን እና የዐማራን ነገድ በጅምላ የሚያጥላላ ልብ ወለድ መጽሐፍ ጽፎ ከኦሮሞዎቹ በላይ ኦሮሞ ሆኖ ወጣ። «ላለቅስ ሲሻኝ ጢስ ወጋኝ» የሆነላቸው አንዳንድ የኦሮሞ ልሂቃንም «ለካ ይኸን ያህል ተበድለን ኖሯል» በሚል ስሜት ውስጥ በመግባት ዐማራውን የአባታቸው ገዳይ ደመኛ ጠላታቸው አድርገው ያዙት። ይህን ተከትሎም «የኦሮሚያ ክልል» በተሰኘው እና ጥንተ-መሠረቱ የዐማራው፣ የሐዲያው፣ የጉራጌው፣ የከምባታው፣ የሲዳማው ፣ የጋፋቱ ፣ የዳሞቱ፣ የዝዩ፣ ወዘተርፈ አጽመ-ርስት ከነበረው ቦታ ሁሉ ዐማራው በገፍ እና በግፍ እንዲባረር ተደረገ። ልብ ወለዱን መጽሐፍ የኦነግ ነባር ሰዎች ሣይቀሩ ዕውነታኛ ታሪክ ነው ብለው አመኑ። በመሆኑም የኦነግ ወታደራዊ መሪ የነበረው አብረሃም ለታ ስለቡርቃ ዝምታ አስተያየት ሲሰጥ፦ ይህ መጽሐፍ በኦሮሞ ልጅ ቢጻፍ ኖሮ የቱን ያህል ዋጋ ሊኖረው ይችል አንደነበር መቆጨቱን ይፋ አድርጓል። ከሁሉም የሚያሣዝነው ግን፣ የልብ ወለዱ መጽሐፍ የተዘጋጀው ሆን ተብሎ ኢትዮጵያን ለመበታተን በሻዕቢያ እና በወያኔ የተቀነባበረ ሤራ አካል መሆኑ በግልጽ እየታወቀ፣ ኢትዮጵያ ብትከፋፈል በመጀመሪያ ተጎጂ ከሚሆነው ከወላይታ ነገድ በሚወለደው በኃይለማርያም ደሣለኝ አመራር፣ በተስፋዬ ገብረአብ ልብ ወለድ መጽሐፍ መሪ ገጸ ባሕሪይ በ«አኖሌ» ስም በአርሲ ውስጥ ሐውልት እንዲሠራለት መደረጉ ነው። minilik ሐውልቱ «የኦሮሚያን ባህል እና ታሪክ ለትውልድ ለማስተዋወቅ» በሚል ሽፋን በሥፋት በተንጣለለ የባህል ማዕከል እና ሙዚየም መካከል የቆመ ነው። በስተቀኝ ባለው ፎቶግራፍ እንደሚታየው፣ በተዘረጋ ቀኝ እጅ መዳፍ ማህል የተቆረጠ ጡት ጉች አለበት። ይህ ሐውልት የሚወክለውም በዐፄ ምኒልክ የአገር ግንባታ ወቅት ሠራዊታቸው «በኦሮሞ ሴቶች ላይ ፈጸሞታል» የሚባለውን የ«ጡት መቁረጥ ድርጊት» እንዲወክል ታስቦ መሆኑ ተገልጿል። በእርግጥ ይህ ሐውልት ዕውነትን የሚወክል ቢሆን ኖሮ ምንኛ ጥሩ በሆነ። ነገር ግን አንዳችም የታሪክ ዕውነትነት የሌለው መሆኑን ማሣያው፦ በመጀመሪያ ደረጃ «የቡርቃ ዝምታ» የተጻፈው ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ታስቦ ነው። ሁለተኛ ተስፋዬ ገብረአብ ዕውቀቱን ከቤተሰቦቹ አገኝቷል እንዳይባል ትውልዱ ከኤርትራ ወደ ደብረዘይት በአፄ ኃይለሥላሤ የአገዛዝ ዘመን በሥራ ምክንያት ከመጡ የኤርትራ ተወላጆች እንደሆነ ይታወቃል። ሦስተኛ በትምህርት አገኘው እንዳይባል ፲፪ኛ ክፍልን እንኳን በወጉ ያጠናቀቀ አይደለም። አራተኛ በሥራ ዓለም ያካበተው ዕውቀት ነው እንዳይባል ዕድሜውም ሆነ ሌሎች ሁኔታዎች ለዚህ አያበቁትም። ስለዚህ የቡርቃ ዝምታን እንዲጽፍ ልብ ወለድ ኃሣቦችን የሰጡት የሻዕቢያ እና የወያኔ ሰዎች ስለመሆናቸው ከተስፋዬ ማንነት የምንረዳው ሃቅ ነው። የቡርቃ ዝምታ እንዲጻፍ ያደረጉ ሰዎች አብይ ግባቸው፣ ዐማራ እና ኦሮሞ ለዘለዓለም እንዳይገናኙ አድርጎ ኢትዮጵያን የማጥፋት ዓላማቸውን ማሳካት መሆኑ ግልጽ ነው። የሐውልቱ መገንባትም፣ በሐሰት የተገነባውን ኅሊናዊ ቅዠት ቁሳዊ መሠረት በመስጠት የሁለቱን ነገድ አባሎች እንዳይይገናኙ አድርጎ ማፋታት ብቻ ሳይሆን ማጠፋፋት መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ሃቅ ነው። ምክንያቱም ይህን ሐውልት የሚያይ ወጣቱ የኦሮሞ ልጅ ከማንም የዐማራ ልጅ ጎን ፈጽሞ አይቆምም። አለመቆም ብቻ ሳይሆን፣ ዐማራን አድኖ እንዲያጠፋ፣ የማይፈታ የቂም ቋጥሮ እንዲይዝ እና በቀልን እንዲወልድ የሚያደርግ እንደሆነ ለማንም የተሰወረ አይደለም። ይህም ቢሆን ሐውልቱ የሚወክለው የተስፋዬ ገብረአብን የምናብ ዓለም እንጂ፣ ዕውነቱን ባለመሆኑ ባህላቸውን እና ታሪካቸውን ጠንቅቀው የሚያውቁ የኦሮሞ ልጆች በዚህ እኩይ የትግሬ-ወያኔ ማባበያ ይደለላሉ ተብሎ አይገመትም። እንደዕውነቱ ከሆነ ጥንትም ቢሆን የወንድ ብልት መስለብ እና የሴት ጡት መቁረጥ የኦሮሞ እና የአንዳንድ የኢትዮጵያ ነገዶች ባህል እንጂ፣ የዐማራው ባህል አለመሆኑ የታወቀ ነው። ለዚህ ማስረጃ ካስፈለገ አሁንም በዘመናችን በጉጂ፣ በከረዩ፣ በአርሲ አካባቢዎች ይህ ባህል አለመተዉ ይታወቃል። ዐማራው፣ ለአገር ዕድገት እና ለብልጽግና የሚበጀው፣ ያለፈውን ትቶ ወደፊት ማዬት፣ ክፉውን በበጎ አለመመለስ መሆኑን በመገንዘብ፣ በሌሎች የተፈጸሙበትን ግፎች ለልጆቹ ግቶ ባለማሳደጉ እንጂ፣ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ እንደ ዐማራው በሌሎች ነገዶች እና ጎሣዎች ልሂቃን በደል የተፈጸመበት የለም። ሆኖም በዕምነቱ፣ በባህሉ እና በአመለካከቱ «ጠላትህን ውደድ፣ ክፉን በክፉ አትቃወም፣ ክፉ ለሠራብህ ደግ መልስለት» በሚለው ኃይማኖታዊ ትምህርት የተገራ በመሆኑ፣ በማናቸው ነገድ እና ጎሣ ላይ ቂም ቋጥሮ በቀል አለመፈጸሙ እንደአላዋቂ አስቆጥሮት፣ ለተደጋጋሚ ጥቃት ዳርጎት እያየን ነው። የተስፋዬ ገብረአብ ልብወለድ እንደ ዕውነት ተቆጥሮ ዐማራን ለማጥፋት እንደመሣሪያ እንዲያገለግል ከተደረገ፣ ኦሮሞውም ለወደፊት ልዕልናው የሚበጀውን ሣይሆን፣ ሁልጊዜ ባልተፈጸመበት የልብ ወለድ ታሪክ ላይ ተመሥርቶ አገሩን ኢትዮጵያን እና ወገኑን በጠላትነት እንዲያይ ይገፋፋል። ይህ ደግሞ ለራሣቸው ለኦሮሞው ነገድ ተወላጆችም ሆነ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ምንም አይጠቅምም። እንዲያውም በትክክለኛው አቅጣጫ ከተሄደ ዐማራውም በታሪኩ በተደጋጋሚ በደረሱበት ጭፍጨፋዎች እና ግፎች ላይ በመመርኮዝ በርካታ ሐውልቶችን ማሠራት ይችላል፣ አገሪቱም ሐውልት በሐውልት ትሆናለች። ለአብነት ያህል በዐማራው ላይ የተሠሩ ግፎችን እንይ፦ አንደኛ፦ ትውልዱን ከሶማሌ ነገድ የሚስበው አህመድ ኢብራሒም አል-ቃዚ (ግራኝ አህመድ) ከ፲፭፻፲፱ ጀምሮ በዘንተራ የጦር ግንባር እስከሞተበት ረቡዕ የካቲት ፳፯ ቀን ፲፭፻፴፭ ዓም ድረስ፣ ለ፲፯ ዓመታት ኢትዮጵያን በወረራ እሳት በለበለባት ወቅት፣ የጥቃቱ ዋነኛ ሰለባ የነበሩት ዐማራ እና የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ነበሩ። ግራኝ አህመድ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን በአሠቃቂ ሁኔታ አስጨፍጭፏል። በአምባ ግሼን ላይ ታሥረው የነበሩትን የዘመኑን የነጋሢ ዘሮች በሙሉ አርዶ ገድሏቸዋል። በሺህዎች የሚቆጠሩ አብያተ ክርቲያናትን የነበራቸውን ልዩ ልዩ ቅርስ እና ንብረት አስዘርፎ ሙሉ በሙሉ አቃጥሏቸዋልል። ይባስ ብሎም በርካታ ክርስቲያን ዐማሮችን በባርነት እየፈነገለ ወደ አረብ አገሮች፣ ቱርክ፣ ፋርስ (ኢራን)፣ ሕንድ፣ ፓኪስታን እና ኢንዶኔዥያ ሣይቀር ሸጧል። ከዚህም በተጨማሪ የፍራፍሬ ዛፎችን ሣይቀር ከሥራቸው እያስመነገለ አጥፍቷል። ሁለተኛ፦ በጦርነት የማረኩትን የዐፄ ገላውዲዎስን አንገት የቆረጡት እና ሐረር ግንብ ላይ የሰቀሉት አደሬዎች ናቸው። ሦስተኛ፦ ኦሮሞዎች ከ፲፭፻፶ዎቹ መጀመሪያ ጀምሮ ከሕንድ ውቅያኖስ ጠረፍ ተነስተው አሁን እስካሉበት የአገሪቱ ክፍሎች ድረስ የተስፋፉት ባለፉበት አገር ሁሉ ወተት እና ማር እያዘነቡ ሣይሆን፣ አልገዛም ብሎ የተዋጋቸውን ነባሩን ሕዝብ በጅምላ በመጨፍጨፍ፣ ሚስት ለማግባት የደረሰውንም በመስለብ፣ የሴቶችን ጡት እየቆረጡ፣ በአጠቃላይ የተወራሪውን ሕዝብ ማንነት በከፍተኛ ወታደራዊ ዘመቻዎች በመጨፍለቅ እንደሆነ ይታወቃል። አራተኛ፦ በ፲፯፻፸ዎቹ በአገሪቱ ከነበሩት መሥፍኖች አንዱ የትግሬው ራስ ሥሁል ሚካኤል ነበር። ይህ መሥፍን በጎንደር ተቀምጦ ነገሥታቱን በአሻንጉሊትነት በማስቀመጥ እና በታሪካችን «ዘመነ-መሣፍንት» የሚባለውን አሣፋሪ የታሪክ ምዕራፍ በመክፈት ይታወቃል። በእርሱ የምሥፍንና ዘመን በአስተዳደሩ ያልተደሰተው ፋሲል የተባለ የጎጃም የጎበዝ አለቃ በአገዛዙ ላይ አመጸ። ሥሁል ያመጸውን ፋሲልን ለማስገበር በርካታ ሠራዊት አሰልፎ ወደ ጎጃም ዘመተ። በዘመቻውም ሥሁል ሚካኤል ቀንቶት ፋሲልን ድል ነሣ። ከድል በኋላ የሥሁል ሚካኤል ሠራዊት ጨዋቃ የተባለውን የፋሲል ተከታይ አርደው፣ ቆዳውን ስልቻ በማውጣት ጭድ ሞልተው፣ ለሥሁል ሚካኤል ግዳይ ጥለውለታል። ይህ በዚያን ዘመን በትግሬዎች አማካይነት በዐማሮች ላይ የተሠራ ግፍ ነው። ወደ ኋላ ማየት ካስፈለገ ይህም ሐውልት ያሻዋል። አምሥተኛ፦ ዐፄ ዮሐንስ ፬ኛ የወሎን እስላም «ክርስትና ካልተነሳህ» ብለው ምላስ ቆርጠዋል፣ አፍንጫ ፎንነዋል፣ ከርስቱም ነቅለዋል። ስድስተኛ፦ ዐፄ ዮሐንስ «ደርቡሽን እዋጋለሁ» ብለው ከትግራይ ከተነሱ በኋላ አስቀድመው የዘመቱት ወደ በደርቡሽ ላይ ሣይሆን በሚያሣዝን ሁኔታ በደርቡሽ በተቃጠለው በጎንደር፣ ከደርቡሽ ጋር በተዋጋው በጎጃም እና «የእስልምና ኃይማኖትህን ቀይር» ብለው ባስገደዱት በወሎ ሕዝብ ላይ ነበር። በተለይም በጎጃም ሕዝብ ላይ ልጅ አዋቂ ሣይለዩ ከሕፃን እስከ ሽማግሌ ሁሉንም በግፍ አስጨፍጭፈዋል። ይህንንም ተግባራቸውን አብረዋቸው በጦርነቱ ዘምተው የነበሩት ግብፃዊው ጳጳስ አቡነ ሉቃስ «ድርቡሽን እዋጋለሁ ብለህ መጥተህ፣ አንተ ራስህ በጎጃም ሕዝብ ላይ ድርቡሽ ሆንክበት» በማለት የግፍ ግድያውን ማውገዛቸው ይታወቃል። የጎጃም አስለቃሽም የግፉን አሰቃቂነት በመመልከት እንዲህ ብላ ማስለቀሷ ይታወሳል። ጎጃም ተቃጠለ ዐባይ እስከ ዐባይ፤ ትግሬ ቅጠል ይዞ ሊያጠፋው ነዎይ፤ ሰባተኛ፦ በ፲፱፻፳፰ ዓም የጅማው ባላባት የአባ ጅፋር የልጅ ልጅ አባ ጆቢር (የኦነግ አመራር አባል የአባ ቢያ አባት)፣ ከፋሽስቱ ወራሪ ጣሊያን ጋር በማበር፣ የዐማራ አንገት እየቆረጠ ለሚያመጣለት ኦሮሞ ሁሉ ፴ ጠገራ ብር እንደሚከፍል አዋጅ አስነግሮ፣ አያሌ ዐማሮችን ማስጨፍጨፉ ይታወቃል። ከአባ ጆቢር ይልቅ ፋሽስቱ ግራዚያኒ ሰብአዊነት ተሰምቶት ግድያውን ማስቆሙ ታሪካችን ያረጋግጣል። ስምንተኛ፦ በ፲፱፻፹፪ ዓም በአሶሳ ይኖሩ በነበሩት ዐማሮች ላይ የሻዕቢያ እና የኦነግ ታጣቂዎች በጣምራ በመዝመት ከ500 በላይ የሚሆኑትን ሰብስበው ቤት ውስጥ በመዝጋት በእሳት አቃጥለው እንደጨረሱዋቸው ይታወቃል። ዘጠነኛ፦ ከ፲፱፻፹፬ እስከ ፲፱፻፹፮ ዓም በነበሩት ፫ ዓመታት ውስጥ ብቻ በበደኖ፣ በወተር፣ በአርባ ጉጉ፣ በአሰቦት ገዳም በሌሎችም የምሥራቅ ኢትዮጵያ ክፍሎች ዐማሮች ዐማራ በመሆናቸው ብቻ በዘራቸው እየተለቀሙ ከነሕይዎታቸው ወደ ገደል ተወርውረዋል፤ ታርደዋል፣ ነፍሰጡር እናቶች ሆዳቸው በሳንጃ ተሰንጥቆ ሽል ተሰልቧል፤ ሰዎች ቆዳቸው እንደ ፍየል ሙክት ተገፍፎ ስልቻ ወጥቷል። አሥረኛ፦ በ፲፱፻፺፫ ዓም ምሥራቅ ወለጋ ውስጥ ለዘመናት ይኖሩ የነበሩ ከ፳ ሺ በላይ ዐማሮች «አገራችሁ አይደለም፣ ውጡ» ተብለው፣ ቤት ንብረታቸውን ተነጥቀው ተባርረዋል። በዚህ ዐማራን የማፈናቀል ሂደት ውስጥ ይታየው መሥፍን የተባለውን ኅዳር ፳፰ ቀን ፲፱፻፺፫ ዓም ከነከብቶቹ በእሳት አቃጥለው ገድለውታል። መልካሙ ውባለም የተባለውን ገድለው ምላሱን ቆርጠው ወስደዋል። አስረግደው ውቡ የተባለውን በጥይት ገድለው በሬሣው ላይ በአንገቱ፣ በወገቡና እና በእግሩ ላይ አንካሤ ቸክለውበታል። አባ በላይ የተባሉትን ማዬት የተሳናቸው አዛውንት ከገደሉ በኋላ «ዐማራ ዐማራ ነው» በማለት ሰልበዋቸዋል። የሁለት ዓመቱን ሕፃን ልጅ እናቱን ስለገደሉበት አባቱ አቶ አዲሱ እናት አልባ የሆነውን ልጁን ያለእናት ማደጉን ለመግለጽ ስሙን «ቀረብህ» ብሎታል። ። (ዝርዝር ታሪኩን ጦቢያ መጽሔት ቅጽ ፰ ቁጥር ፰ ፲፱፻፺፫ ዓም ዕትም ይመልከቱ)። አሥራ አንደኛ፦ የወልቃይት፣ የጠገዴ፣ የጠለምት፣ የሰቲት እና የአርማጨሆ ዐማራ በጅምላ ተገድሎ ታስሮ እና ተፈናቅሎ፣ በአጽመ ርስቱ ላይ ትግሬ እንዲሠፍርበት ተደርጓል። አሥራ ሁለተኛ፦ በምሥራቅ ኢትዮጵያ በጅጅጋ ከተማ ለዘመናት ይኖሩ የነበሩትን ዐማሮች «አገራችሁ አይደለም» ተብለው ኃብት ንብረታቸውን ተነጥቀው ተባርረዋል። አሥራ ሦስተኛ፦ ከ፪ሺህ፬ ዓም ጀምሮ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በጉራ ፈርዳ ወረዳ ይኖሩ የነበሩትን ከ፸፰ ሺህ በላይ ዐማሮች «አገራችሁ አይደለም» ተብለው በግፍ ኃብት ንብረታቸውን ተነጥቀው ተባርረዋል፤ በአሰቃቂ ሁኔታም ብዙዎች ተገድለዋል። አሥራ አራተኛ፦ ባለፈው ዓመት በ፪ሺህ፭ ዓም በአሶሳ እና በመተከል (ጎጃም) ይኖሩ የነበሩትን ከ፶ ሺህ በላይ ዐማሮችን «አገራችሁ አይደለም፣ ውጡ» ተብለው ቤት ንብረታቸውን ተነጥቀው ተባርረዋል። በማባረሩ ሂደት ውስጥም አቶ አሥራደ መቅጫ የተባለውን ዐማራ አርደው፣ ሰልበው እና የፊቱን ቆዳ ገፍፈው አስከሬኑን ጫካ ውስጥ ጥለውታል። አቶ ተሰማ ስዩምን በጥይት ደብድበው ገድለዋል። ሌሎች ፲፪ ሰዎችን ሠርተው እንዳይኖሩ አድርገው፣ ከሞት መልስ ቀጥቅጠው ደብድበዋቸዋል። ወላድ ሴቶች በመንገድ ላይ እንዲወልዱ በመገደዳቸው የእንግዴ ልጃቸውን ውሻ እንዲበላው ተደርጓል። እትብት መቁረጫ አጥተው በባልጩት እንዲቆርጡ ተገድደዋል። አሥራ አምሥተኛ፦ ዘረኛው የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ዐማራውን ከምድረ ኢትዮጵያ ለማጥፋት በኤች አይ ቪ ቫይረስ የተበከለ ደም በመርፌ እየወጋ በሽታውን እያሰራጨ እንደሆነ የአደባባይ ሚስጢር ነው። በዚህም አጥፊ ጉዞው ከ፲፱፻፹፱ እስከ ፲፱፻፺፱ ዓም ድረስ በነበሩት በ፲ ዓመታት ጊዜ ውስጥ ብቻ የዐማራው ቁጥር ከሌሎች ነገዶች በተለየ ሁኔታ በሁለት ሚሊዮን አምስት መቶ ሺህ እንዲቀንስ አድርጓል። አሥራ ስድስተኛ፦ በተላላፊ በሽታ እና በወሊድ ቁጥጥር ሰበብ የዐማራውን ተወላጅ፣ ወንዱን የሚያኮላሽ፣ ሴቱን የሚያመክን መድኃኒት በመስጠት ከፍተኛ የሆነ የዘር ማጥፋት ወንጀል ይፈጸምበታል። ከላይ ከተዘረዘሩት መካከል እኛ ባለንበት በ፳፩ኛው ክፍለ-ዘመን የተፈፀሙት እና የሚፈፀሙት በፍርድ ሂደት ዕምነት-ክህደት የሚጠየቅባቸው እንኳን አይደሉም። በጥቅሉ ሲታይ በዐማራው ነገድ ላይ በተከታታይ የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል ተፈጽሞበታል። እነዚህ ሁሉ፣ «ወደ ኋላ እንይ፣ ትውልዱን በቂም በቀል ስሜት ውስጥ ከትተን እስከ ዝንተ-ዓለሙ እንዳይገናኝ አድርገን ኢትዮጵያን እናፍርሳት» ብለን ካሰብንና ካመንን፣ ታላላቅ ሐውልቶች ማቆም ብቻ ሣይሆን ብዙ የደም መፋሰስ የሚያስከትሉ እንደሆነ ማንም ኅሊና ያለው ሰው ይገነዘበዋል። ከዚህ አንፃር የጥፋት መልዕክተኛውን የተስፋዬ ገብረአብን የልብ ወለድ መጽሐፍ የቅዠት ተረት ተረት፣ በገሃዱ ዓለም የተፈጸመ አስመስሎ «የአኖሌ እጅ» ላይ የተቆረጠ ጡት አስቀምጦ ሐውልት ማቆም፣ አተራማሾቹ የፈለጉትን ኢትዮጵያን የመናድ ተልዕኮአቸውን እንዲወጡ ከማድረግ ያለፈ ለኦሮሞ ሕዝብ የሚሰጠው አንዳችም ቁሳዊም ሆነ ኅሊናዊ ፋይዳ የለም። በትርምሱ ተጠቃሚ የሚሆኑትም የአናሳዎቹ የሻዕቢያ እና የትግሬ-ወያኔ ቡድኖች እና ተከታዮቻቸው ብቻ ናቸው። ለ፳፫ ዓመታት በሥልጣን ኮርቻ ተፈናጥጠው ለመቆየት የቻሉትም፣ በእነዚህ ሁለት ታላላቅ ነገዶች መካከል ባሠራጩት የጠላትነት ፕሮፓጋንዳ፣ ሆድና ጀርባ ሆነው እንዲተያዩ በማድረጋቸው እንደሆነ ግልፅ ነው። ኢትዮጵያዊነትን፣ ብሔራዊ አንድነትን እና የአገራችንን ኅልውና ማስጠበቅ የሚቻለው ለሥልጣን እና ማዕከላዊ አስተዳድርን ለመመሥረት ሲባል የተደረጉትን ግብግቦች እና ግጭቶች፣ አልፎ አልፎም ጦርነቶች ያስከተሉትን ጥፋት፣ የተወሰኑ ነገድ አባሎች ብቻ እንዳደረጉት በመቁጠር፣ አልፎ ተርፎም የዚያን ነገድ አባሎች በጅምላ ለመበቀል በመነሣት አይደለም። ውሾች በአጥንት ይጣላሉ፤ ጅብ ሲመጣባቸው ግን ጠባቸውን ትተው በጅቡ ላይ ያብራሉ። የእስከዛሬዎቹ ኢትዮጵያውያን አባቶቻችን እና እናቶቻችንም ሲያደርጉ የኖሩት ይህንኑ ነበር። ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ የአፍሪቃ መመኪያ እስከመሆን የዘለቀችውም አባቶቻችን «የዘመድ ጥል፣ የሥጋ ትል» ብለው በየግል የደረሰባቸውን በደል በሠፊዋ ኢትዮጵያ ኅልውና ለድርድር የማያቀርቡ በመሆናቸው ነበር። በአገራችን ብሔራዊ አንድነት ግንባታ ወቅት «ተከሰተው ነበር» የሚባሉ ችግሮች ሁሉ፣ በአድራጊ ግለሰቦች እና በአደራረግ ሁኔታ እንዲሁም በቦታ እና በጊዜ ከመለያየት ውጪ፣ በየትኛውም አገር የተከሰቱና ሁሉም አገሮች ያለፉባቸው የኅብረተሰብ ዕድገት ውጤቶች ናቸው። በዚያን ጊዜ ሠፊ መሬትና የፈላጭ ቆራጭነት ሥልጣን ከመፈለግ አኳያ አንዱ ነገድ ሌላውን ፈጽሞ ለማጥፋት የቃጣበት ወቅት የለም። እንዲያውም የጦርነቶቹ ባህርይ፣ «የተገዛ፣ አልገዛም» ግብግብ መገለጫ ስለነበር፣ በተመሣሣይ የነገድ አባሎች መካከል የነበረው የእርስ በእርስ ግጭት የበዛ ነበር። በዚህ ረገድ በእኛ አገር ዋነኞቹ ተፋላሚዎች «ከዘውድ እንወለዳለን» በሚሉት የመሣፍንት ወገኖች መካከል ስለነበር፣ ጦርነቱ ከነገድ ወርዶ በወንድማማቾች መካከል የተካሄደ ነበር። ይህም በመሆኑ በአገራችን የግራው አመለካከት በትውልዱ መሐል እስከተዘራበት እስከ ፲፱፻፷ዎቹ ድረስ አንድም ነገድ ሌላውን ነገድ በጠላትነት ፈርጆት አያውቅም ነበር። የ«አኖሌ የጡት ቆረጣ» ታሪክም የዚሁ የግራ-ዘመሙ ትውልድ የፈጠራ ታሪክ ውጤት ነው። የግራው አመለካከት ለእኛ አገር ቀርቶ ለበቀለበትም አገር የማይጠቅም ሆኖ፣ ተወግዞ ከተወገደ ከ፳ ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል። ስለሆነም፣ ኢትዮጵያን የሚያጠፋ፣ ሕዝቡን ለመተሣሠብ እና ለአንድነት ሳይሆን ለቂምና ለቁርሾ የሚያነሣሣ ልብ ወለድ ድርሰትን በታሪክ ስም ማስቀመጥ፣ አልፎ ተርፎም ሐውልት መገንባት፣ ከጥቅሙ ይልቅ ዘለቄታዊ ጉዳቱ እንደሚያመዝን በስማቸው ለሚነገድባቸው የኦሮሞ ተወላጆች ግልፅ ሊሆንላቸው ይገባል። የኦሮሞ አባቶችም በስማቸው የሌላቸውን ጠላት የሚገዛላቸውን ይህን ሐውልት እንዲያወግዙ ይለመናሉ። ይህ ካልሆነ ግን የዐማራ ተወላጅ ሁሉ እንዳለፉት ዘመናት «ለጋራ ጥቅም» እያለ «ሆድ ይፍጀው» ብሎ በዝምታ አይቀመጥም። እስከዛሬ ድረስ የዐማራው ወላጆች በኢትዮጵያዊነት ጥላ ሥር አብሮ ለመኖር ሲባል ለልጆቻቸው ሲያስጠኑ የኖሩት፣ የታሪካችንን ደግ ደጉን ክፍል እንጂ፣ ክፉ ክፉውን አይደለም። ሆኖም ዐማራውን የሚያጥላሉ «የቡርቃ ዝምታ» ዓይነት ጽሑፎች እና የአኖሌ ሐውልትን ዓይነት ቋሚ ሥራዎችን ማስፋፋት፣ ለዘመናት ሣይገለፅ የኖረውን ዕውነተኛ የኦሮሞዎችን ማንነት ግልጥልጥ አድርጎ እንዲያስተምር ይገፋፋሉ። ስለዚህ የአኖሌ ሐውልት መቆም እንደ ሶባስቶፖል መድፍ ወደ ኋላ ተተኩሶ ተኳሹን የሚያጠፋ ከመሆን ያለፈ ፋይዳ አይኖረውም፦ «ደባ ራሱን፣ ስለት ድጉሡን» ወይም በሌላ አገላለፅ «አሣ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል፣ የሰው ፈላጊ የራሱን ያጣል» ነውና! ዐማራን ከፈፅሞ ጥፋት እንታደግ! ፈለገ አሥራት የትውልዳችን ቃል ኪዳን ነው! ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!

No comments:

Post a Comment