Saturday, December 28, 2013

ኢጋድ የደቡብ ሱዳን ግጭት ተዋናዮች የፊት ለፊት ድርድር እንዲጀምሩ የአራት ቀን ማስጠንቀቂያ ሰጠ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 18፣ 2006 (ኤፍ ቢ ሲ) በደቡብ ሱዳን ለተከሰተው የፖለቲካ ቀውስ መፍትሔ ለማፈላለግ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት(ኢጋድ) መሪዎች በናይሮቢ ተወያይተዋል።
መሪዎቹ ከስብሰባቸው በኋላ ባወጡት መግለጫ፥ በአገሪቱ ግጭት ውስጥ ተዋናይ ለሆኑት ለፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪርና ለቀድሞ ምክትላቸው ሪክ ማቻር የፊት ለፊት ድርድር እንዲጀምሩ የአራት ቀናት ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል። ቢቢሲ በጉባኤው ላይ እየተሳተፉ የሚገኙ የአገራት መሪዎችን ዋቢ አድርጎ እንደዘገበውም፥ የደቡብ ሱዳን መንግስት የተኩስ አቁም ለማድረግ ተስማምቷል። መሪዎቹ የደቡብ ሱዳን መንግስት ግጭቱን ለማቆም የወሰደውን ፈጣን እርምጃ ማድነቃቸው ተመልክቷል። ተቀናቃኛቸው እና የቀድሞ የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚዳንት ሪክ ማቻርም ተመሳሳይ እርምጃ እንዲወስዱም ነው ያሳሰቡት። ሁለቱም ወገኖች እስከ ማክሰኞ ድረስ ለሰላማዊ መፈትሄ ፊት ለፊት ተገናኝተው መነጋገር ካልጀመሩ ኢጋድ ተጨማሪ እርምጃዎችን ለመውሰድ ይገደዳል ብለዋል በመግለጫቸው። በደቡብ ሱዳን የሚገኙ ወሳኝ መሰረተ ልማቶችን ለመጠበቅ ኡጋንዳ የወሰደችውን እርምጃ ያደነቁት መሪዎቹ፥ ይህንን ተግባር ኢጋድ ይደግፋል ብለዋል። በአገሪቱ ተሞክሯል በተባለው መፈንቅለ መንግስት ተወንጅለው በእስር ላይ የሚገኙ ፖለቲከኞችም ሰብዓዊ መብታቸው ተጠብቆ በደቡብ ሱዳን ህግ መሰረት እንዲዳኙ አሳስበዋል። በናይሮቢው የኢጋድ ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ የአስተናጋጇ አገር ኬኒያ፣ የኡጋንዳ፣ የጂቡቲና ሶማሊያ መሪዎች ተገኝተዋል። ደቡብ ሱዳንም በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ተወክላለች።

No comments:

Post a Comment