Sunday, December 15, 2013

በኢትዮጵያ ላይ ስለ ተፈጸመው የፋሺሽት የጦር ወንጀል ዓለም-አቀፍ ተቃውሞ


December 15, 2013
Italian Fascists posing in Ethiopia
መግለጫ
ፋሺሽት ኢጣልያ፤ በቫቲካን ድጋፍ፤ በ1928-33 ዓ/ም በኢትዮጵያ ላይ በፈጸመችው የጦር ወንጀል፤ አንድ ሚሊዮን ሕዝብ በመጨፍጨፉ እንዲሁም 2000 ቤተ ክርስቲያኖችና 525000 ቤቶች፤ ከነንብረቶቻቸውና ቅርሶቻቸው በተጨማሪም፤ ሕዝቡ የሚጠቀምባቸው ውሀና የአካባቢ ብክለት በመከሰቱና 14 ሚሊዮን እንስ ሶች በመውደማቸው ሕዝባችን የደረሰበትን ረሀብና ሥቃይ መገመት አያዳግትም። ስለዚህ በየዓመቱ እንደሚደረገው፤ ዘንድሮም የካቲት 12 ቀን 2006 ዓ/ም ወይም ሰሞኑን ሰማእታቱን ለማስታወስ በሰላማዊ ሰልፍና በመሳሰሉት ተቃውሟችንን በኢትዮጵያና በዓለም አቀፍ በሚገኙ 50 ልዩ ልዩ ከተሞች ለመግለጽ አቅደናል።
ፋሺሽቶች፤ በሶስት ቀኖች ውስጥ፤ የካቲት 12-14 ቀኖች 1929 ዓ/ም፤ 30፣000 ኢትዮጵያውያንን አዲስ አበባ ጨፍጭፈዋል።
ፋሺሽቶች በኢትዮጵያ ላይ ለፈጸሙት ግፍ የኢጣልያን መንግሥት ለኢትዮጵያ ተገቢውን ካሣ አልከፈለችም። ከኢትዮጵያ ተዘርፎ በኢጣልያና በቫቲካን መንግሥቶች እጅ የሚገኘው መጠነ ሰፊ ንብረትም አልተመለሰም። አይሑዶችን በመደጋገም ይቅርታ የጠየቀችው ቫቲካንም እስካሁን ድረስ የኢትዮጵያን ሕዝብ ተመሳሳይ ይቅርታ አልጠየቀችም። ኢጣልያ በሊቢያ ላይ ለፈጸመችው ወንጀል $5 ቢሊዮን ዶላር የከፈለች መሆኑ የታወቀ ነው። በተጨማሪም ኬንያውያን በእንግሊዝ መንግሥት ለደረሰባቸው ግፍ ተገቢውን ይቅርታ ተጠይቀው ካሣ እንዲከፈላቸው አድርገዋል። የኢንዶኔዝያ ሕዝብም ከኔዘርላንድስ መንግሥት ተመሳሳይ ይቅርታ መጠየቅና ካሣ እንዲከፈል አድርጓል። የኢትዮጵያ ሕዝብስ መቼ ነው ከቫቲካንና ከኢጣልያ መንግሥቶች የሚገባውን ፍትሕ የሚያገኘው? ለክብራችንና ለመብታችን ካልታገልን ፍትሕ አይገኝም። “ባለቤት ካልጮኸ ጎረቤት አይረዳም” ነውና።
በፖፕ ፓየስ 11ኛ ትመራ የነበረችው ቫቲካን ሙሶሊኒንና የፋሺሽቶችን መንግሥት ትደግፍ
እንደ ነበር በብዙ ማስረጃ የተረጋገጠ ነው። ዝርዝሩን ለማየት www.globalallianceforethiopia.org መመልከት ይቻላል። የቫቲካን አባቶች የፋሺሽቱን ጦር መባረካቸውን፤ ለቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴም አንድ ሚሊዮን ስተርሊንግ ፓውንድ ጉቦ በመስጠት ሥልጣናቸውን እንዲለቁ መሞከሯን፤ ፖፕ ፓየስ 11ኛ የኢጣልያን ንጉሥ ሲባርኩ፤ “King of Italy and Emperor of Ethiopia” (ትርጉም፤ የኢጣልያ ንጉሥና የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት) ማለታቸውን፤ እንዲሁም ቫቲካንና ፋሺሽቶቹ “ላተራን” የተሰኘ ውል በመፈራረም እጅና ጓንት ሆነው ጥቃታቸውን ያከናወኑ መሆኑ፤ ወዘተ. በታሪክ የተረጋገጠ ሐቅ ነው። ይህ ሁሉ አልበቃ ብሎ፤ በቅርቡ፤ ነሐሴ 1 ቀን 2005 ዓ/ም አፊሌ (Affile) በምትሰኝ የኢጣልያ ከተማ፤ የቫቲካን ተወካይ በተገኙበት፤ ለጨፍጫፊው፤ ለግራዚያኒ የመታሰቢያ ኃውልት ተመርቆለታል።
A Vatican Clergy blessing the Italian Fascist Army on its way to commit war crime
የፋሺሽቱ ጦር በቫቲካን ካሕን ሲባረክ
የዓለም-አቀፍ ሕብረት ለፍትሕ – የኢትዮጵያ ጉዳይ (Global Alliance for Justice – The Ethiopian Cause) ዓላማዎች
የሕብረቱ ዓላማዎች፤ 1ኛ/ ቫቲካን የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ እንድትጠይቅ፤ 2ኛ/ ቫቲካንና ኢጣልያ የተዘረፉትን ንብረቶች እንዲመልሱ፤ 3ኛ/ ኢጣልያ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ተገቢውን ካሣ እንድትከፍል፤ 4ኛ/ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በኢትዮጵያ ላይ የተፈጸመውን ግፍ በመዝገቡ እንዲያውልና፤ 5ኛ/ ለግራዚያኒ የተቋቋመው ኃውልት እንዲወገድ ነው።
ለሐገር ክብርና ፍትሕ፤ ለሰብአዊ መብት መከበር የምንቆም ሁሉ፤ የመንፈሳዊ፤ የመገናኛ ብዙኃን፤ የሴቶች፤ የወጣቶችና ለሰብአዊ መብት የሚታገሉ ድርጅቶች፤ ወዘተ. ጭምር፤ የየካቲት 12 ቀን 2006 ዓ/ምን የሰማእታት ቀን፤ ከላይ ለተጠቀሱት ዓላማዎች በመታገል በደመቀ ሁኔታ እንድናከብረው እናሳስባለን። የመታሰቢያው ቀን፤ በሰላማዊ ሰልፍ፤ በጉባኤ እና/ወይም በጸሎት ሊከናወን ይችላል።
“ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” መዝሙረ ዳዊት 67/31
ቸሩ የኢትዮጵያ አምላክ ያበርታን።
Global Alliance for Justice – The Ethiopian Cause; 4002 Blacksmith Drive, Garland, TX 75044
www.globalallianceforethiopia.org; info@globalallianceforethiopia.com

No comments:

Post a Comment