Wednesday, January 15, 2014

“የህዝባዊ አንድነትና ኃይል የወያኔ ሕወሐት ማጥፊያ መድሃኒት” January15/2014


ከሮባ ጳዉሎስ

ካለመታደል ሀገራችን ዛሬም ሰላም ፍትህና ዲሞክራሲ የሰፈነባት በልማትና በእድገት ጎዳና የምትራመድ ሀገር አልሆነችም። ለዚህም በርካታ ምክንያቶች ቢኖሩም እንደ ዓቢይ ምክንያት ተደርጎ የሚቀርበው የህዝብን ይሁንታን ያገኘ፡ ህዝብን በእኩልነት የሚዳኝ፡ ህዝባዊና ዲሞክራሲያዊ የሆነ መንግሥት አለመመስረቱ፡ አገርና ህዝብ የሚተዳደሩበት ዲሞክራሲያዊ ህገ መንግሥት አለመኖሩ ነው። እስከዛሬ በተጨባጭ እንደታየው በ ኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ የተፈራረቁበት ገዥዎቹ በየበኩላቸው አንዱ ከሌላው የሚለዩባቸው ባህርያት ቢኖራቸውም ሁሉንም ግን አንድ የሚያስመስሏቸው ባህርያትም አሏቸው። እነሱም ሁሉም በኃይል ሥልጣን መያዛቸው፡ አምባገነንነታቸው፡ የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲ ማራመዳቸው፡ በህዝብ መካከል የጋራ መተማመንና ከበሬታን ለመፍጠር፡ ሁሉም ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን በሀገሪቱ ለማስፈን አለመቻላቸው ደግሞ ዛሬ ለሁሉም በግልጥ እየታየ ያለ ነው። በዚህም የተነሳ በሀገራችን ለብሔራዊ ክብርና ነፃነት፡ ለዲሞክራሲ፡ ለማህበራዊ ፍትህ፡ ለሰላምና ለእኩልነት የሚታገሉ ኃይሎች የሰላማዊ ለውጥ በሮች ስለተዘጉባቸው የአ መፅን ጎዳና እንዲከተሉ የሚጋብዝ በር ተቀዶ ይገኛል።


በሌላ በኩል ደግሞ በሀገሪቱ ውስጥ የፖለቲካ መረጋጋት ንእዲፈጠር፡ ሕዝቡም አስተማማኝ ሰላምና ፀጥታ አግኝቶ ያለስጋት ለመኖር እንዲችል፡ የዳኝነት ተቋሞች ነፃ ሆነው የሚሠሩበት፡ የህግ የበላይነት የተረጋገጠበት ሁኔታ እንዲፈጠርና፡ ህዝቡም በህግና ሥርዓት መኖር ላይ እምነት እንዲያድርበት ለማድረግ እንዲቻል፡ ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚታገሉ ኢትዮጵያዊ ተቃዋሚ ኃይሎች በተናጠልም ሆነ በኅብረት በርካታ ጥረቶች ተደርገዋል። ሆኖም እስከዛሬ የተደረጉት ጥረቶችን ሁሉ በማምከን ወያኔ የሰላምና የእርቅ መሰናከል ከመሆኑም ባሻገር በንፁሃን ዜጎች ደም ሰላምን አጠልሽቶታል። ወያኔ ስለ ሰላምና እርቅ ሊሰማም ሊነጋገርም እማይችልበት የደም ስካር ላይ ደርሷል።

ብአዴን ቢመጣ ኦህዴድ ቢመጣ ደህዴን ቢመጣ የሚለወጥ ነገር አይኖርም። ጠንከር ያለ ለለውጥ የተዘጋጀ – አስከ ሞት የቆረጠ -ጠቅላይ ሚኒስተር ስልጣን አገኘ ማለት የህወሃት የበላይነት እና ፈላጭ ቆራጭነት ፍላጎት ፈተና ይገጥመዋል ማለት ስለሆነ! ህወህት የበላይነቱን ለማሰጠበቅ የፈጠራቸው የመንግስት ስልጣን አደረጃጀት አና ተቋማት ዛሬም በሙሉ ሃይላቸው አሉ። የህወሃት ፈላጭ ቆራጭነት ሳይዳከም ለውጥ አይመጣም። የህወሃት ፈላጭ ቆራጭነት መሰረቱ ደሞ ከምንም በላይ ወታደራዊ ሃይሉ ላይ የተመሰረተ አንደሆነ የአደባባይ ሚስጥር ነው። በደህነንት ቢሮ ያሉትን የህወሃት አመራሮች ከታች ያሉት ማዳክም የሚችሉበትን አጋጣሚ አና ሁኔታ ተጠቅመው አስካላዳከሙት ደረስ የህወሃት የስልጣን የበላይነት ትርጉም ባለው ሁኔታ እክል ሊገጥመው አይችልም።

ሌላ ሌላውን ትተን መሰረታዊ የሆነ ህገ-መንግስታዊ ማሻሻያ ያስፈልጋል፣ የፍትህ ስርዕቱ የፍትህ ስርእት መመስልም መሆንም አለበት፣ የነጻው ፕሬስና ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ህዳሴ አንመራለን አየተባለ በመካከለኛው ዘመን አና ከዛ በፊት ከነበረው አንደነበረው በሰይፍ አና በሰደፍ መያዝ የለበትም። አነኚህ ወሳኝ ርምጃዎች በአዝጋሚ ለውጥ ይመጣሉ ብየ አላስብም። የአዝጋሚ ለውጥ ዲስኩር (ፍላጎት ካለ ፍላጎትም) ጭራሽ ወደማይቀልበስ የባርነት ዓለም አና ዘመን የመውሰጃ ከፓለቲካ ዘዴ ሊሆን ይችላል። ጋዜጠኞችና የተቃዋሚ ፓለቲካ መሪዎች ዘብጥያ ሲጣሉ ሙስሊም ኢትዮጵያውያን የፈጠሩትን ዓይነት ጫና መፍጠር ስላልተቻለ አንኳን መሰረታዊ የፕሬስ ነጻነት አና በነጻነት ያለገደብ የመደራጀት መብት የሚከበርበት ፍንጭ ሊገኝ ቀርቶ የታሰሩትን ጋዜጠኞች አና የፓለቲካ መሪዎች ማስፈታት አንኳን አልተቻለም። ጭራሽ መብታቸው ተረግጦ ያላግባብ አስር ቤት የተጣሉ ኢትዮጵያውያን ዛሬ ድረስ “አሸባሪ” አየተባሉ አየተፌዘባቸው ነው ያለው። አቶ ኃይለማርያምም ፌዙን በጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ አያስተጋቡት ነው።

ከበቀለበት የተጋጋበት አንዲሉ የ”በሳሉ መሪ ራዕይ” ዜማ ከህወሃት አባላት በእህት ድርጂቶች የፓለቲካ አላዋቂዎች አና መሪዎች ይበልጥ ተዜመ! በአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝም ተሰማ። ችግሩ የለውጥ ጥያቄ ማድበስበሻ ሆኖ ለረዢም ጊዜ ሊቆይ አይችልም። በውሽት ላይ የተመሰረተ ፐሮፓጋንዳ ስር ሊይዝ አይችልም።አንዴት ይሄን ማየት አቃታቸው?!የሕዝባችን መከራና ሰቆቃ እየከፋ ሄደ። የተጨቆነዉ ሕዝብ ተነሳስቶ ለመብቱ ሲታገል ጨቋኝ መንግሥታት ለዉጥ እንዲያደርጉ ይገደዳሉ፤ ካለዚያ በተባበረዉ የሕዝብ ኃይል ተንኮታኩተዉ ይወድቃሉ። የታገለዉ ለዉጥ ያመጣል፤ ያልታገለዉ ቁጭ ብሎ በባርነት ሲገዛ ይኖራል፤ ቁጭም ባለበት ይሞታል ማለት ነው። የለዉጥ ባለቤት ሁሌ ሕዝብ መሆን አለበት። ህዝቡ ትግሉን በሚገባ እንዲያቀናጅ የትግል መሪ ይፈልጋል። ስለዚህ የተቃዋሚ የፖሊቲካ መሪዎች ታላቅ ኃላፊነት ይጠበቅባቸዋል። ያገራችንን ጭብጥ ሁኔታ ስንመረምር ግን በሁለቱም በኩል ታላላቅና ተደጋጋሚ ድክመቶች ታይተዋል። አምባገነን መንግሥታት ለዘለዓለም ካልገዛን ሲሉ የተቃዋሚ ድርጅቶች ኅብረታቸዉን ማጠናከር ስላልቻሉ የጨቋኝ መንግሥታትን ዘመናት ሲያራዝሙ ቆይተዋል።ወያኔ/ኢሕአደግ ለዘለዓለም ሊገዛ አይችልም፤ ለሁሉም ጊዜ አለዉና።ትግሉ ይበልጥ መፋፋም፡ ይበልጥ መጨስ፡ መጋጋም፡ መንደድ ይጠበቅበታል። ትግሉን ለማፈንና አቅጣጫውን ለማሳት የወያኔ መንጋ እየተሯሯጠ ነው።

 በውጭ ያለውንም የሕዝብና የድርጅቶችን ተቃውሞ ቢቻለው ለማዳፈን፡ ካልሆነለት ደግሞ ለማዳከም፡ በአሁኑ ወቅት የወያኔ ከፋፋይ ቡድን በየቦታው በመንቀሳቀስ ላይ እንደሚገኝ እያየን ነው። ይህ ቡድንም፡ ምሁር ነን፡ አስታራቂ ነን፡ ሽማግሌ ነን ወይም ታጋይ ነን በሚሉ መሰሪዎችም እየተደገፈ ነው። የሕዝብ ክንድ ይላላ፡ ይደክም ዘንድ፡ በከፋፋይ ሴራ የተሰማሩትን ነቅቶ መጠበቅ፡ ትግሉን መከላከል ብቻ ሳይሆን ወያኔ ለባሾችን፡ ሰላዮችን ሳንፈራ እየመነጠርን ማጋለጥ ይኖርብናል። ዘረኛው ቡድንና ጭፍሮቹ የሕዝቡን ትግል ለመከፋፈል ከመቼውም ጊዜ በበለጠ እየጣሩ ናቸውና። ሕዝብ አንድነቱን ጠብቆ፡ የወያኔን ቡድን ለአንዴም ለሁሌም ለማስወገድ አስፈላጊውን መስዋእ ትነት እየከፈለ ባለበት ወቅት የፖለቲካ ድርጅቶችን እገዛና አመራር ይጠይቃል። የሕዝብ አሸናፊነት አጠራጣሪ ባይሆንም፡ አሸናፊ ለመሆን ግን መታገል መቅደም እንዳለበት ምን ጊዜም መረሳት የለበትም። ለዚህ መሠረቱ ግን ከራስ ጋር እየታረቁ፡ ከወገን ጋር እየተስማሙ በጋራ ዓላማና ብሔራዊ እጅንዳ ዙሪያ ተሰባስቦ በጋራ መታገል ብቻ ነው። በዓለም ታላቅ ዝና ያተረፉት የግ/ቀ/ኃ/ሥና በአፍሪቃ አህጉር መሬትን ያንቀጠቀጠዉ የደርግ መንግሥት ቀናቸዉ ሲደርስ እንዴት እንደመነመኑና እንደከሰሙ መዘርዘር አይኖርብኝም፤ በታሪክ ፊት ተቀምጧልና። በሩቁም በእነ አሜሪካ ለረዥም ዓመታት ሲረዱና ሲደገፉ በነበሩት በእነ ሞቡቱ፤ የሻህ ንጉሥ፤ ሆስኒ ሙባረክ፤ ወዘተ ላይ በመጨረሻ የደረሰዉን ዉርደት መገንዘብ ያስፈልጋል። ተቃዋሚ የፖሊቲካ ድርጅቶች ነን የሚሉትና በተግባር ግን የጭቆናን ዘመን የሚያራዝሙ በሙሉ ካለፉት ስህተቶች ገና ሊማሩ አልቻሉም፤ ・ድር ቢያብር እንበሳ ያስር・ የተባለዉን ቅዱስ አሳብ ደጋግመዉ መናቃቸዉ ያስተዛዝባል። ቁርጥ ያለ አቋም ያስፈልጋል፤ ከዛፍ ዛፍ መዝለል ዬትም አያደርስም። ለጊዜያዊ ጥቅማ ጥቅሞች በርካሽ መገዛትና አገርን መሸጥ በሰማይም በምድርም ያስጠይቃል። ቀኑ ሲደርስ ራቆታችንን ወደምድር እነደመጣን ሁሉ ራቆታችንን ወደዚያዉ እነደምንመለስ አንርሳ!!!

ነገርግን በህብረት ለሀገር ታሪክ ሰርቶ ማለፍ ዘላለማዊ የትዉልድና የሀገር ክብር ነዉ!!!

ዘ-ሐበሻ

No comments:

Post a Comment