Wednesday, January 8, 2014

የኢትዮጵያ ሰራተኞች ተወካዮች ብሶታቸውን ለመንግስት ባለስልጣናት ቢያቀርቡም መልስ እንዳላገኙ ተዘገበ



ታህሳስ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ሰንደቅ ጋዜጣ አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ የመሩትን ስብሰባ በዝርዝር ያቀረበ ሲሆን፣ ከጋዜጣው ለመረዳት እንደተቻለው ሰራተኛው በሚያነሳቸው ቅሬታዎችና መንግስት በሰጣቸው መልሶች መካከል ከፍተና ክፍተት አለ።
የሰራተኞቹ ተወካዮች የሰራተኛው የመደራጀት መብት እንዳልተከበረና ሕገ-መንግስታዊ መብታቸው እንደሚጣስ ገልጸዋል። የሰራተኛው የመደራጀት መብት ሲጣስም በመንግስት በኩል አርኪ ምላሽ አይሰጥም ብለዋል።

ተወካዮቹ የኑሮ ውድነቱን መቋቋም ባለመቻላቸው መንግስት ድጎማ ያድርግልን ብለዋል። በሰራተኛው ላይ ተደራራቢ ታክስ በመበራከቱም የሰራተኛው ኑሮ ከድጡ ወደ ማጡ እየገባ በመሆኑ መንግስት የገቢ ግብርና የቫት ታክስ ማሻሻያ ያድርግልን ሲሉ ጠይቀዋል።

አንዳንድ የግል አሰሪዎችና የመንግስት ኃላፊዎች የሀገሪቱን ሕገ-መንግስት ሲጥሱ ሀይ የሚላቸው የለም የሚሉት የሰራተኞች ተወካዮች፣ “በነፃ መደራጀት አቅቶናል” ሲሉ በምሬት ተናግረዋል። “ሕገ-መንግስቱን የሚያስከብረው ማነው?” ሲሉ መጠየቃቸውንም ጋዜጣው ዘግቧል።

በኮንስትራክሽን አካባቢ በኬሚካል መመረዝን ጨምሮ በርካታ ጉዳቶች እንደሚደርሱ፣ ለሰው ልጅ ጤንነት አደገኛ የሆኑ መራዥ ኬሚካሎች የሰራተኛውን ዓይን እንዲያጣ፣ በቆዳው እና በመራቢያ አካላቱ ላይ ችግር እንዲፈጥር ማድረጉንም የማህበራቱ ተወካዮች ገልጸዋል።
አንዳንድ አሰሪዎች ሰራተኛውን የሚያስሩበት የራሳቸው እስር ቤት አላቸው ያሉት ወኪሎቹ፤ ከስራና ሰራተኛ አገናኝ ጋር በተያያዘ ከአረብ አገር በባሰ መልኩ በኢትዮጵያ በሰራተኞች እየተነገደ መሆኑንም አስረድተዋል። ከአሰሪና ሰራተኛ አገናኝ ጋር በተያያዘ ከአረብ አገር የባሰ የጉልበት ብዝበዛ ኢትዮጵያ ውስጥ እየተካሄደ እንደሆነም ገልጸዋል።

“ሰራተኛው አንድ ጫማ ከቀየረ ይበቃዋል። በዚያው መጠን ግን አምስትና ስድስት መኪኖችን የሚቀያይሩ ቀጫጭን ባለሀብቶች ተፈጥረዋል” የሚሉት የሰራተኞቹ ተወካዮች፤ “ድሮ የምናውቀው ወፍራም ባለሀብት ነበር፤ የዛሬ ባለሀብቶች ግን ቀጫጭን ናቸው።” በማለት ስለ አዲሶቹ ባለሀብቶች ገልጸዋል።

የታክስና የኑሮ ውድነትን በተመለከተም የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ ሶፊያን አህመድ ለታክስ መሻሻሉም ሆነ ለደመወዝ ጭማሪ የሀገሪቱ ኢንዱስትሪ ማደግ ይገባዋል በማለት መልስ ሰጥተዋል።

የኑሮ ወድነትን ለማርገብ መንግሰት ደመወዝ ከመጨመር አንስቶ ስንዴ፣ ስኳር፣ ዘይትና ዳቦ በከፍተኛ ድጎማ እያከፋፈለ እንደሚገኝ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ የአገሪቱ ምርት ካላደገ ጥሩ ደሞዝ መክፈል እንደማይቻል አስረድተዋል።

No comments:

Post a Comment