Wednesday, December 4, 2013

አንድነት በአገር ጥቅም ላይ ከማንም ጋር እንደማይደራደር አስታወቀ


አንድነት በአገር ጥቅም ላይ  ከማንም ጋር እንደማይደራደር አስታወቀአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) መንግስትና ገዢው ፓርቲ የአገሪቷን ሁሉንም ነገር ለፖለቲካ ፍጆታ መጠቀማቸው አገርን አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ ሊቆም እንደሚገባ ገለፀ፡፡ ከትላንት በስቲያ ፓርቲው በፅ/ቤቱ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ “የኢህአዴግን ስርዓት ከቀደሙት አምባገነን ስርዓቶች ለየት የሚያደርገው ሁሉንም ነገር ለፖለቲካ ስልጣን መጠቀሚያ ማዋሉ ነው” ያለው አንድነት፤ ከዚህም ውስጥ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ አንዱ እንደሆነ ገልፃል፡፡ ግድቡ ከመጀመሩ በፊት ማለቅ የነበረባቸው ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች ነበሩ፣ ግድቡን ከፓርቲ አጀንዳ ወደ ህዝብ አጀንዳነት ማውረድ አለበት፣ የግድቡ ስራ አንድ አካል የሆነውን የወንዝ አቅጣጫ ማስቀየር በግንቦት ሀያ ዕለት ማድረጉ ፖለቲካዊ እንጂ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የለውም፣ ያለው አንድነት ፓርቲ፤ መንግስት ለግድቡ ግንባታ ከጉሮሮው እየነጠቀ የሚወስደው ከህዝብ ስለሆነ የአባይ ግድብ ጉዳይ የህዝብ አጀንዳ እንዲሆን መንግስት ከተቃዋሚዎችም ሆነ ከሌሎች ባለ ድርሻ አካላት ጋር አገራዊ ውይይና መግባባት ላይ መድረስ እንዳለበት ፓርቲው በመግለጫው አሳስቧል፡፡
“የአንድ መንግስት ግዴታዎች የሆኑት ተግባራት መንገድ ውሃ፣መብራትና መሰል ተግባራት መዳረሻቸው የፖለቲካ ስልጣን ማራዘም ነው ያለው ፣ለፖለቲካ ፍጆታ የማይውል ንፁህ መሰረተ ልማት ወሳኝ መሆኑን ፓርቲው በፅኑእንደሚያምን ገልፆ ዛሬ እንደ አዲስ ኢህአዴግ ያነሰው በአባይ ወንዝ ላይ ግድብ መስራትና ማልማት አስፈላጊነት ለዘመናት ሲነሳ የነበረ ጉዳይ እንደሆነም አስታውሷል፡፡ የአባይን ጉዳይ በተመለከተ ከአንድ አመት የተመረጡት የግብፅ ፕሬዝዳንት መሀመድ ሙርሲ ሃሳባቸው ተቀባይነት ይኑረውም አይኑረውም ከተቃዋሚዎች ጋር እንደተነጋገሩ የሱዳን መንግስት የፖለቲካ እስረኞችን በመፍታት የተሻለ ብሄራዊ መግባባት ለመፍጠር እየጣረ እንደሆነ የገለፀው አንድነት “የኢትዮጵያ መንግስት ግን በግትርነት ማሰርና መፈረጁን በመቀጠል የሀገራዊ መግባባት አደጋ እየሆነ ነው” ብሏል በመግለጫው፡፡ በመሆኑም አንድነት አምስት ነጥብ ያለው አቋም እንዳለው አስታውቋል፡፡
የግብፅና የኢትዮጵያ መንግስት ከፀብ አጫሪ ድርጊትና ፕሮፓጋንዳ እንዲታቀቡና የጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት ላይ እንዲያተኩሩ፣ አባይን መጠቀም የኢትዮጵያ የተፈጥሮ መብት እንዲሆኑ እንዲታወቅ፣ ሁለቱ ሀገራት የአባይን ጉዳይ የውስጥ ፖለቲካቸው ማብረጃ ከማድረግ እንዲቆጠቡ፣ አገራዊ መግባባት አሁኑኑ እንዲፈጠር መንግስት ሀላፊነቱን እንዲወጣና የአባይ ጉዳይ የፖለቲካ መጠቀሚያ መሆኑ እንዲያበቃ የሚሉት የፓርቲው አቋሞች ሆነው ሰፍረዋል፡፡ ከመገደቡ በፊት ማለቅ የነበረችው ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች ምንድን ናቸው? ግንቦት ሀያ ደርግ የወደቀበት የህዝብ በዓል ሆኖ ሳለ ለምን የፓርቲ በዓል ትላላችሁ? ግድቡ ሲበሰር የተቃውም አቅጣጫን ለማስቀየር ነው ስትሉ ነበር አሁንም ሁለቱ አገሮች የውስጥ ችግራቸውን ማብረጃ እንዳያደርጉት እያላችሁ ነው፣ በግብፅና በኢትዮጵያ ጉዳይ ያላችሁ ቁርጥ ያለ አቋም ምንድነው? ኢትዮጵያ በታሪኳ ለህዝብ የሚያስብ መሪ አጋጥሟት አያውቅም ብላችኋል የእነ እምዬ ምኒሊክ ውለታን ዘንግታችሁት ነው የሚሉና መሠል ጥያቄዎች ከጋዜጠኞች ተነስተው ምላሽ ተሠጥቶባቸዋል፡፡
የአንድነት ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በሠጡት ምላሽ “በእኛ በኩል ሁለቱ አገሮች ወደ ከፋ ጦርነት እንዳያመሩ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት እንዲደረግ እንፈልጋለን” ብለዋል፡፡ የሙርሲን መንግስት ተቃዋሚዎች በሠኔ ወር መጨረሻ እናስለቅቃለን በማለታቸው ሙርሲ በአባይ ጉዳይ ነገሩን፡፡ ለማረሳሳት ጥረት ማድረጋቸው የማይቀር እንደሆነ ዶ/ር ነጋሶ ጉዳዩ በአትኩሮት ታይቶ በእኛ መንግስት በኩል እልባት ሊበጅለት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ “የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎችን አስታጥቀን ችግር እንፈጥራለን የሚሉት ግብፆች ስህተት የሚጀምረው የኢትዮጵያን ተቃዋሚዎች አለማወቃቸው ላይ ነው” ያሉት የአንድነት ምክትል ሊቀመንበር አቶ ግርማ ሰይፉ፣ በበኩላቸው ይህ አይነት አባባላቸው የግብፅ ህዝብ አስተያየት ነው ብለው እንደማያምኑ ተናግረዋል፡፡ “እንዲህ አይነት ውይይት በኢትዮጵያም ቢካሄድ የአባይ ወንዝ አቅጣጫ ተቀይሮ የኢትዮጵያን ምድር ያጠጣ የሚል ኢትዮጵያዊ አይጠፋም” ያሉት አቶ ግርማ፣ ይህ ሀሣብ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ይወክላል የሚል እምነት እንደሌላቸው አስታውቀዋል፡፡
ተቃዋሚን ማስታጠቅ በሚለው ሀሳብ ላይ አንድነት በአገር ጥቅምና በኢትዮጵያዊነት ላይ ፈፅሞ እንደማይደራደርና ሊታሠብም እንደማይገባ በአፅንኦት ገልፀዋል – አቶ ግርማ፡፡ “ግንቦት 20 እኔን አይወክለኝም” ያሉት አቶ አስራት ጣሴ ደርግ መውደቁ ጥሩ ነገር ሆኖ ከግንቦት ሀያ የሚጠበቁት ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፍትሆች ባልተሟላበትና መፍትሄ ባላገኙበት ሁኔታ ግንቦት ሀያ የፓርቲ በዓል እንጂ የህዝብ ሆኖ ህዝብን ሊወክል እንደማይችል ተናግሯል፡፡ አንድም ለህዝብ የሚያስብ መሪ የላትም በሚለው ጉዳይ ላይ እኔ አፄ ቴድሮስን ብንወዳቸውም የሰብዓዊ መብት አያያዝ ላይ የተዋጣላቸው ነበሩ ለማለት አስቸጋሪ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ “መንግስት አሁንም ቢሆን የግብፅን ጉዳይ በቸልታ ሊመለከተው አይገባም” ያሉት የአንድነት ዋና ፀሃፊ አቶ አስራት ጣሴ በዚህ ጉዳይ ላይ ተቃዋሚዎች ከዲያስፖራውና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመወያየት አገራዊ መግባባት ላይ መድረስ አለበት ብለዋል፡፡ ከግድቡ ስራ በፊት ማለቅ የነበረባቸው ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች መካከል የናይል ተፋሰስ ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ማፅደቂያ አዋጅ መፅደቅ ከነበረበት ዘግይቶ የፀደቀበት ምክንያት አንዱ ነው ብለዋል አቶ ግርማ ሰይፉ፡፡

No comments:

Post a Comment