Saturday, December 14, 2013

አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ስለምኒሊክና ስለኢትዮጵያ

bulcha d
የአጼ ምኒሊክን መቶኛ የሙት አመት መከበር ምክንያት በማድረግ በ DW ሬድዮ በተደረገው ጥያቄና መልስ አቶ ቡልቻ ደመቅሳ፣ ዶ/ር ሓይሌ ላሬቦና ዶ/ር ሹመት ሲሳይ (የታሪክ ተመራማሪዎች) ቃለ መጠይቅ ተደርጎ በሚሰጠው መልስ ላይ ስለ አቶ ቡልቻ ደመቅሳ በተናገሩት ላይ አስተያየቴን አቀርባለሁ።
አንባቢያንን ቃለመጠይቁን ቢያዳምጡ ጥሩ ነው ባይ ነኝ፤ ሁለቱ የታሪክ ምሁራን ትምህርታዊ ትንተና ይሰጣሉና፡፡
ውሸት ሲደጋገም እውነት ሊመስል ይችላል፤ በተለይም የአገራችንን የኢትዮጵያን ታሪክ ለማያውቁ እውነታው ምን እንደሚመስል መረጃ ለማቅረብ እሞክራለሁ።
አቶ ቡልቻ ኦሮሞ ከባሌ እየተስፋፋ ሲመጣ ልብነ ድንግል እንዳይስፋፋ አቆሙት ይላሉ፡፡ ለምን ይህን ምሳሌ እንዳቀረቡም ግልጽ አይደለም ለሳቸው ትንታኔ የማይመች በመሆኑ፤ ለዛውም በአጼ ልብነ ድንግልና በኦሮሞች መሀከል ስለነበረው ግኑኝነት በከፊል ዶ/ር ሃይሌ ላሬቦ ሊያስረድዋቸው ሞክረዋል፤ ስለመስፋፋቱና እንዲያውም አማራውን እንደገፋው ለአቶ ቡልቻ መረጃ ላቅርብ፡፡
ጥንት ሌላ ስም የነበራቸው በኦሮሞ ከተያዙ ማግስት ስማቸው የተቀየረ፤ ደዋሮ-ጨርጨር፣ ጋፋት-ሆሮ፣ ገራሪያ-ሰላሌ፣ ዳሞት-ወለጋ፣ አበቤ-በቾ፣ ሽምብራ ኩሬ-ሞጆ … (የሃያኛው ክፍለዘመን ኢትዮጵያ ገጽ 50 በጥላሁን ገ/ስላሴ) በቅኝ ተገዛ የሚሉት ኦሮሞ ተጨማሪ ቦታ እንደያዘ እንጂ እንደተወሰደበት አይደለም ታሪኩ የሚመሰክረው፡፡
BULCHADEMEKSAአቶ ባልቻ የኦሮሞን ታሪክ ከደቡብ አፍሪካ ጋር ሊያዛምዱት ይሞክራሉ፤ ኦሮሞም እንደ ደቡብ አፍሪካ ጥቁሮች ኢትዮጵያ ውስጥ ሲረገጥ የኖረ ሕዝብ አድርገው ያቀርቡታል። መፍትሄውንም ሲጠይቁ reconciliation እርቅ ኦሮሞ ይቅርታ ተጠያቂ የተቀረው ይቅርታ ጠያቂ በተለይም የፈረደበት አማራ ለዚህ ወንጀል ትልቁን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ባለፉት አስተዳደሮች ስህተቶች አልተሰሩም ብሎ የሚከራከር የለም፤ ጥያቄው እንዴት አብረን ወደፊት መሄድ እንችላለን ነው?
እንደቅኝ ተገዛን የሚሉት ቡልቻ ደመቅሳ አገሪቱን በእርሻ ሚኒስቴርነትና በምክትል ገንዘብ ሚኒስቴርነት አስተዳድረዋል – ቸር ቅኝ ገዢ ነበር የነበራቸው፤ እኛ ቅኝ እየተገዛን ስለሆንን በሚኒስቴርነት ቅኝ ገዢዬን አላገለግልም ብለው አላንገራገሩም፡፡
ኦሮሞ በሲቪሉም ሆነ በወታደራዊው ክንፉ ታላቅ የሚባሉትን ስልጣኖች ይዞ የኖረና ያለ የህብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ አገሪቱ ውስጥ ለነበሩትና ላሉትም ደግ ነገሮችም ሆነ ክፉ ነገሮች ተጠያቂነቱ እኩል ነው፡፡ አቶ ቡልቻ ቅኝ ገዢ የሚሉትን የአማራውን ክፍለሀገር ደጃዝማች ክፍሌ ዳዲ ያስተዳድሩት ነበር፡፡ (ምሳሌ የሚያቀርቡበት ደቡብ አፍሪካ የማስተዳደር ቅንጦት ይቅርና ነጭ በሚዝናናበት ቦታ ጥቁር መግባት አይፈቀድለትም ነበር)፡፡
ስለኦሮሞ ባለስልጣናት እስቲ እንመልከት
ምኒሊክ በሸዋ ሲነግሱ የረዷቸው አብሮ አደግ ባልንጀራቸው ጎበና ዳጬ ናቸው፡፡ የወለጋውም አስተዳዳሪ ኩምሳ ምኒሊክን በደጃዝማችነት አግልግለዋል፤ እነ ባልቻ አባ ነፍሶም የማይረሱ ታላቅ ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡
የአጼ ሃይለስላሴ አባት ራስ መኮንን ወልደሚካኤል (ጉዲሳ) አባታቸው ኦሮሞ ነበሩ፤ እናታቸውም ወ/ሮ እመቤት እናታቸው ኦሮሞ ነበሩ፡፡
ራስ ዳርጌ የሸዋው ንጉስ ሳህለስላሴ ከወለዷቸው አራት ወንዶች መሃከል አንዱ ሲሆኑ ጥናታቸው አርሲ ውስጥ የአንድ አካባቢ ኦሮሞ ባላባት ልጅ ነበሩ (አባ ቦራ በታቦር ዋሚ፤ ገጽ 9)
ራስ አበበ አረጋይ  መከላከያ ሚኒስትር
አቶ ይልማ ዴሬሳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፤ የገንዘብ ሚኒስትር
ደጃዝማች ክፍሌ ዳዲ የጎንደር አስተዳደር
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ የእርሻ ሚኒስትርን ምክትል የገንዘብ ሚኒስትር
ሜጀር ጀኔራል ሙሉጌታ ቡሊ የክብር ዘበኛ አዛዥና የባህል ሚኒስትር
ደጀዝማች ገረሱ ዱኪ የኢሊባቡርና የጎሙገፋ አስተዳዳሪ
ሜጀር ጀኔራል ደምሴ ቡልቲ የሁለተኛው ክፍለ ጦር አዛዥ
ሌተና ጀኔራል ጃጌማ ኬሎ የአራተኛው ክፍለጦር አዛዥና የባሌ አስተዳደር
ፊታውራሪ ለማ ወልደጻድቅ የሲዳሞ ምክትል አስተዳደር
ሜ/ጀኔራል አበራ ወልደማርያም የአየር ኃይል ምክትል አዛዥ
ደጃዝማች በቀለ ወያ የጨቦና ጉራጌ አስተዳደር ከዚያም የጨርጨር አስተዳደር
ደጃዝማች ካሳ ወልደማርያም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንትና የእርሻ ሚኒስትር
አንባቢያን መረዳት ያለብን ሁላችንም በመጀመሪያ ደረጃ ኢትዮጵያውያን መሆናችን ነው፡፡ ሕዝባችን በጋብቻ፣ በእምነት፣ በባሕል፣… የተሳሰረ በመሆኑ መሰረት የሌለው ታሪክ እያነበነቡ ሊበታትኑን የሚያስቡትን ታሪካዊ መረጃ እያቀረብን ወግዱ ልንላቸው ይገባል፡፡ ድር ቢያብር አንበሳ ያስር ነው፤ ምኒሊክም ያስተማሩን መቻቻልን አንድነትንና ፍቅርን ነው፡፡
ዶ/ር ካሳሁን በጋሻው
www.goolgule.com.

No comments:

Post a Comment