Thursday, December 19, 2013

የፍርሃት ባህልን እያነገሰ ያለው የኢትዮጵያ ፖለቲካ፤ አንድ እርምጃ ወደፊት ሁለት ወደ ኋላ (ክፍል ሁለታ)

December 19, 2013

ያሬድ ኃይለማርያም፣ ከብራስልስ
December 19/2013
ያሬድ ኃይለማርያም፣ ከብራስልስ
የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሂደት በኢትዮጵያዊያን ላይ እያሰፈነ ስላለው የፍርሃት ባህል ቀደም ሲል ባሰራጨሁት የዚህ ጽሑፍ የመጀመሪያ ክፍል ውስጥ ባለሙያዎች በአንድ ማኅበረሰብ ውስጥ ለፍርሃት ባህል መስፈን መንሰዔዎች ያሏቸውን ነጥቦች ዘርዝሬ ነበር። በክፍል አንድ ጽሑፌ መግቢያ ላይ እንደገለጽኩት ምንም እንኳን ፍርሃት የግለሰቦች ባህሪ መገለጫዎች መካከል አንዱ ቢሆንም የዚህ ጽሑፍ ትኩረት በወል የምንጋራቸውና በማኅበረሰብ ደረጃም በሚንጸባረቁት የፍርሃት ምልክቶች ላይ ብቻ ያተኮረ ነው። በመሆኑም በዚህ ክፍል ውስጥ የህሊና እና የአካል ቁስልን ባስከተሉ ትላንቶች ውስጥ ማለፍ የሚፈጥረውን የፍርሃት ቆፈንና የሚያስከትለውን መዘዝ በመቃኘት ፅሑፌን ልደምድም።
በአለማችን ታሪክ ከሰው ልጅ አዕምሮ ተፍቀው የማይወጡና እጅግ አሰቃቂ በመሆናቸው ሲታወሱ የሚኖሩ በርካታ ጦርነቶችና የእርስ በርስ እልቂቶች ተከስተዋል። የመጀመሪያውና የሁለተኛው የአለም ጦርነቶች፣ የኦሽዊትዝ ጭፍጨፋ፣ የአፓርታይድ የግፍ አገዛዝ፣ የሩዋንዳው የዘር ማጥፋት እልቂት፣ እንዲሁም በተለያዩ የአፍሪቃ እና የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ውስጥ የተከሰቱትና የሚሊዪኖችን ሕይወት የቀጠፉት እልቂቶች በዋነኝነት ተጠቃሾች ናቸው። እነኚህ በክፉ ክስተትነታቸው በታሪክ የሚወሱት አጋጣሚዎች ካስከተሉት እልቆ መሳፍርት የሌለው ሰብአዊ ቀውስ እና የንብረት ውድመት ባሻገር ከትውልድ ትውልድ የሚወራረስ ትምህርትንም አስተምረው አልፈዋል። በተለይም የምዕራቡ አለም በራሱም ሆነ በርቀት በሌሎች ላይም የተፈጸሙትን እነዚህን መሰል መጥፎ ክስተቶች በአግባቡ በመመርመር፣ መረጃዎችን ሰብስቦና አደራጅቶ በማስቀመጥ፣ በመጽሐፍ ከትቦና እና በፊልም ቀርጾ በማኖር ቀጣዩ ትውልድ እነኚህን መሰል አደጋዎችን ከሚያስከትሉ የፖለቲካ፣ የማኅበራዊ፣ ኃይማኖታዊና ኢኮኖሚያው ቀውሶችና ቅራኔዎች እራሱን በማራቅ ችግሮችን እጅግ በሰለጠነና ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ እንዲፈታ ማድረግ ችለዋል። ዛሬ ላይ ያለው ትውልዳቸውም እነ ናዚ እና ሌሎች አንባገነኖች በታሪካቸው ውስጥ ያደረሱትን ሰቆቃና ግፍ እያሰብ የሚሸማቀቅ ወይም በፍርሃት የሚርድ ሳይሆን ታሪክን በታሪክነቱ ትቶ ሙሉ አቅሙንና ጊዜውን ከሳይንስና ተክኖሎጂ ጋር አዋህዶ በዚህ ምድር ላይ ያሻውን ሁሉ ለማድረግ የሚያስችል አቅም በመገንባት ላይ ይገኛል።
ወደ አገራችን ስንመለስ ኢትዮጵያም ዛሬ ያለችበትን ጂዮግራፊያዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊም ሆነ ሌሎች ገጽታዎች ለመላበስ ያበቋት እጅግ በርካታ ክፉ እና በጎ ተበለው የሚጠቀሱ የታሪክ ክስተቶችን አስተናግዳለች። ምንም እንኳን ከላይ ከተጠቀሱት የአለማችን አሰቃቂ ታሪኮች ጋር ባይወዳደርም አገራችንም ከውጭ ወራሪዎች በተሰነዘረባት ጥቃትም ሆነ በልጆቿ መካከል በተከሰቱ የእርስ በእርስ ግጭቶች በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ውድ ልጆቿን አጥታለች። ድህነትን ጠራርጎ ሊያስወግድ ይችል ከነበረው አቅም በላይ በብዙ እጥፍ የሚገመት አንጡራ ሃብቷን በጦርነቶች፣ በግጭቶችና በዘራፊዎች ተነጥቃለች። ይህ እና ሌሎች በርካታ ምክንያቶችም ተደራርበው አገሪቱን ከድሃም ድሃ ተብለው ከሚጠቀሱት አገሮች ተርታ አሰልፈዋታል። እንግዲህ ትልቁ ጥያቄ እኛስ እንደ ሌላው ዓለም ሕዝብ አገራችን ካለፈችበት የረዥም ዘመን ታሪክ እና በየወቅቱ ከተከሰቱ መጥፎና በጎ የታሪክ ክስተቶች ምን ተማርን? ተምረንስ ለዛሬ እኛነታችን ምን አተረፍን? በአያቶቻችን እና በእኛ መካከል በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊ እና በፖለቲካ ተክለ አቋማችንም ሆነ አመለካከታችን ዙሪያ ለውጦች አሉ ወይ? ለውጣችን ቁልቁል ወይስ ካለፉት ወገኖቻችን የህይወት ተመክሮ ትምህርት ወስደን የደረስንበት የላቀ የአስተሳሰብና የኑሮ ደረጃ አለ? የታሪክ መዛግብቶቻችንስ ያለፉ ነገስታቶችን እና የጦር አበጋዞቻቸውን ከማወደስና ገድላቸውን ከመተረክ ባለፈ በቀጣዩ ትውልድ ሕይወት የጎላ ሚና ሊኖራቸ በሚችል መልኩ ተዘጋጅተዋል ወይ? ወይስ ‘እኔ የገሌ ዘር’ እያለ እንዲያዜምና በአያቶቹ ገድል እንዲያቅራራ ብቻ ተደርገው ነው የተዘከሩት? እንደ እኔ እምነት ከምዕራቡ አለም እኛንና ብዙዎች የአፍሪቃ አገራትን ከሚለዩን ነገሮች መካከል ጥቂቶቹ ከነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ የሚመነጩ ይመስለኛል።
የዛሬ መቶ እና ሁለት መቶ አመት በፊት የተፈጠሩ የታሪክ ክስተቶችን ፍጹም በተዛባ መልኩ እያጣቀስን ልክ የእኛ የልፋት ውጤት አስመስለን እስኪያልበን የምንፎክርና የምንጨፍር እኛ ነን። ታሪክን እና ጀግኖችን ማወደስ ተገቢ ቢሆንም የኛን ድርሻ እነሱን በማወደስ ብቻ ስንገታው አደጋ ላይ ይጥለናል። እንደ አያቶቻችን ታሪክን መስራት ሲያቅተን ታሪክ ሰሪዎችን በማውሳትና በዜማና በግጥም ማወደስ ብቻ ብንኮፈስ የዛሬውን ማንነታችንን አይሸፍነውም። ይህ በአያቶቻችን ታሪክ ውስጥ ተደብቀን ‘በኢትዮጵያዊነቴ እኮራለሁ’ እያሉ ማዜም፣ መፎከር፣ ማቅራራትና ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት ዛሬ ከተጣቡን የድህነት፣ የፖለቲካ ጭቆና እና ማኅበራዊ ቀውስ የማያስጥለን እና ነፃ የማያወጣን እሰከ ሆነ ድረስ ኩራታችን ከድንፋታ አያልፍም። አገሬን እወዳልሁ፣ በኢትዮጵያዊነቴ እኮራለሁ እያሉ ባንዲራ ለብሶ ማቅራራት በተግባር ካልታገዘ የውሸት ወይም ባዶ ኩራት (false pride) ነው የሚሆነው። እውነተኛ ኩራት የሚመነጨው ከራስ ነው፤ የራስን ማንነትን በማወቅና በመቀበል ላይ የሚመሰረት ነው። ማንነትን አምኖ መቀበል አቅማችንንም አብረን እንድፈትሽ ይረዳል። የዛሬ ባዶነታችንን በአያቶቻችን የታሪክ ገድል እንድንሞላ ወደሚያስገድድ የሞራል ክስረት ውስጥም እንዳንገባ ይረዳናል። የዛሬ ውርደታችንን በአድዋ ድል እና በሌሎች የአያቶቻችን ተጋድሎዎች በተገኙ ስኬቶችን ልንሸፍነው ከመጣር ይልቅ ታሪክ እንድንሰራ ብርታት ይሆነናል።
በሌላ በኩል የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ያሳቀፉንን የዘረኝነት መርዝ እያራባን በታሪክ ተፈጽመዋል የተባሉ አንዳንድ ክስተቶችን እየመነዘርን ‘ያንተ ቅም ቅም አያትህ የእኔን ቅም ቅም አይታቶች በድሎ ነበር፤ ስለዚህ በቅም ቅም አያቶቼ ላይ ያንተ ዘሮች ላደረሱት በደል ኃላፊነቱን አንተ ትወስዳለህ እያልን ድርጊቱን ዛሬ ላይ እንደተፈጠረ በመቁጠር የምንጋጭና ለመነጣጠል እንቅልፍ አጥተን የምናድርም አለን። እራስን እንደተበዳይ ሌላውን የኅብረተሰብ ክፍል እንደ በዳይ በመቁጥርና የተዛባን ታሪክ በመተንተን ለዛሬው በዘረኝነት መርዝ ለተለወሰው የፖለቲካ አጀንዳቸው ማሳኪያነት ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ካፈር የሚለውሱ ኢትዮጵያዊያኖችም (እነሱ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ቢሉም) ልብ ሊገዙ ይገባል። በአገሪቱ ውስጥ ያሉ የተለያዩ ጎሣዎች በገዛ አገራቸው እኩል መብትና ጥቅም እንዲረጋገጥላቸውና የሁሉም አገር እንድትሆን ከመጣር ይልቅ በዘረኝነት ስሜት ውስጥ ተወጥሮ ኢትዮጵያዊነትን መካድና ከራስ ጎሣ ውጭ ያለውን የኅብረተሰብ ክፍል እንደ ጠላት መቁጠር መዘዙ ብዙ ነው። ይህን ለመረዳት ብዙ ምርምር አያስፈልገውም። በቅርባችን ካለችው ከሩዋንዳ ትምህርት መውሰድ ይቻላል። ይህን የዘረኝነት እሳት እየተቀባበሉ የፖለቲካ መታገያቸው ያደረጉ ኃይሎችም ከዚህ እኩይ ተግባራቸው እንዲታቀቡ በስሙ የሚነግዱበት ሕዝብ ሊያወግዛቸው ይገባል።
እርቀን ሳንሄድ የቅርብ ጊዜ ታሪካችንን እንኳን ብንፈትሽ ዛሬ ለምንገኝባቸው እጅግ ውስብስብ እና ፈታኝ ችግሮች መንስዔ የሆኑትን ነገሮች በቀላሉ ልንገነዘብ እንችላለን። የችግሮቻችንን ምንጮች እና ያስከተሉብንን መዘዝ በቅጡ መረዳት ከቻልን ከተዘፈቅንበት አረንቋ ውስጥ ለመውጣት ጊዜ ላይወስድብ ይችላል። መወጣጫውም ላይርቀን ይችላል። ትልቁ ጥያቄ ችግሮቻችንን ከመዘርዘር ባለፈ ምንስዔዎቻቸውንም በቅጡ ተረድተነዋል ወይ? እንደ አንድ አገር ሕዝብ በችግሮቻችን እና በችግሮቹ ምንጭ ዙሪያ የጠራ የጋራ ግንዛቤ አለን ወይ? በፖለቲካ እና በሌሎች ማኅበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ስንደራጅስ ከነዚህ ግንዛቤዎች ተነስተን ነው ወይ? የጋራ የሆኑ ችግሮች ሰዎችን ያስባስባሉ፣ ለድርጅቶች መፈጠርም መንስዔ ይሆናሉ፣ ችግሮቹንም ለመቋቋም እና ለማስወገድ “ከአንድ ብርቱ …” እንደሚባለው ኃይልን ይፈጥራሉ። ይሁንና ስብስቡ ወይም የተደራጀው ኃይል ፊት ለፊት ከተጋረጡት ችግሮች ጋር ከመፋለም ባለፈ በድጋሚ እንዳይከሰቱ ምንጮቻቸውን ለማድረቅ የሚያስችል እይታ ከሌለው እና አቅሙንም በዚያ ደረጃ ካላሳደገ ይህ አይነቱ ማኅበረሰብ ሁሌም ለተመሳሳይ አደጋዎች የተጋለጥ ነው። የችግሩን መንሰዔ አጥንቶ ምንጩን ለማንጠፍ ከሚያወጣው ጉልበት፣ ገንዘብና ጊዜ የበለጠ አዳዲስ ችግሮች በተከሰቱ ቁጥር ከተኛበት እየባነነ ተነስቶ ችግሮቹን ለመቋቋም የሚያስችሉ ድርጅቶችን ለመፍጠርና ለማፍረስ የሚያወጣው ጊዜ፣ ገንዘብና ጉልበት እጅግ የላቀ ነው። በእንዲህ አይነት ማኅበረሰብ ውስጥ ጠንካራ የሆኑና ልምድ ያካበቱ ድርጅቶችን መፍጠር አይቻልም። ብዙዎቹ ድርጅቶች ሳይጎረምሱ፣ ሳይጎለምሱ እና ሳያረጁ በጨቅላነታቸው ይሞታሉ ወይም ደንዝዘው ስማቸውን ብቻ ይዘው ይቀራሉ። ይህ አይነቱ ማህበረሰብ አውራ የሚሆኑና በምሳሌነት ሊጠቀሱ የሚችሉም የፖለቲካ፣ የኃይማኖት እና የማኅበራዊ ህይወት መሪዎችን የመፍጠር አቅም የለውም፤ አይፈጥርምም፤ በራሳቸው ጥረት ቢፈጠሩም ጎልተው እንዲታዩ እድሉን አይሰጥም። ትላንት ያነገሳቸውን በማግስቱ አፈር ከድሜ ሲደባልቃቸው ምንም አመክንዮ አይፈልግም። ሲያከብርም፣ ሲሾምም፣ ሲያዋርድም ሆነ ሲኮንን በስሜት ነው። በተለይም እንደኛ በብዙ ውስብስብ ችግሮች ውስጥ ተተብትቦ ግራ ለተጋባ ማኅበረሰብ ልምድና በእውቀት የጎለበቱና የሕዝብ አመኔታን ያገኙ ባለ ዕራይ ድርጅቶችና ግለሰቦች መኖር እጅግ ወሳኝ ነው።
የፖለቲካም ሆነ ሌሎች ልዩነቶቻችንን የምንይዝበት መንገድ ሊፈተሽ ይገባዋል። የቀዝቃዛው የአለም ጦርነት ማብቂያን ተከትሎ የፈረሰውና ጀርመንን ለሁለት ከፍሏት የነበረው ግንብ ሲናድ ምስራቅና ምዕራቡን ወደ አንድ አገር ከመለወጥ ባለፈ መላው አውሮፓን አንድ ያደረገ ክስተትን ፈጥሯል። የሰብአዊ መብቶች እና የዲሞክራሲ ጽንሰ ሃሳቦች የልዩነት ማጦዣ ምክንያቶች ከመሆን ወጥተው ጀርመንን ብቻ ሳይሆን አውሮፓን ያዋሃዱ ተጨባጭ እውነታዎችን ፈጥረዋል። ይህን ተከትሎም ከታሪክ ለመማር ዝግጁ በሆኑ በበርካታ የአለማችን አገራት በመሬት የተገነቡም ሆነ በሰዎች አዕምሮ ውስጥ የተካቡ የልዩነት ግንቦች ሁሉ ፈርሰው ዜጎች ለጋራ ራዕይ በጋራ የመቆም ጽናትን አሳይተዋል። ሕዝባቸውንም ነጻ አውጥተዋል። ሌሎች እንደ ኢትዮጵያ ያሉ የተለያዩ አገሮች (አብላጫዎቹ የአፍሪቃ አገራት) የልዩነቶቻቸውን ግንቦች አጠንክረውና አዳዲስ ግንቦችን በአይምሯቸው ውስጥም ገንብተው የተሰበጣጠረና የሚፈራራ የኅብረተሰብ ክፍልን በመፍጠር ጉዞዋቸውን ቀጥለዋል። የጎሣ ግንቦች፣ የሥልጣን ግንቦች፣ የኃይማኖት ልዩነት ግንቦች፣ የድሃና የሃብታም ግንቦች፣ የጨቋንና የተጭቋኝ ግንቦች፣ ሌሎች ማኅበረሰቡን በአንድ ላይ እንዳይቆም እና ድህነትና አንባገነንነትን አሽቀንጥሮ እንዳይጥል አቅም የሚያሳጡ በርካታ የልዩነት ግንቦች ተገንብተዋል።
ድርጅቶችን እና መሪ የሚሆኑ ግለሰቦችን እየፈጠርንና መልሰን እየደፈጠጥን የመጣንበትን የ50 ዓመታት የፖለቲካ ጉዞ ወደ ኋላ መለስ ብለን ብንቃኝ ይህንን እውነታ ያረጋግጥልናል። ባለፉት 50 ዓመታት ውስጥ ለቁጥር የሚታክቱ የፖለቲካ፣ የሙያና በማኅበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ያተኮሩ ድርጅቶች ተፈጥረው ብዙዎች ካለሙበት ሳይደርሱ ከስመዋል። ጥቂቶችም ባልሞት ባይ ተጋዳይነት በመኖርና ባለመኖር መካከል ሆነው ቀጥለዋል። በከሰሙትም እግር ሌሎች በርካቶች ተተክተው በተመሳሳይ አዙሪት ውስጥ ወድቀው የኅብረተሰቡን ቀልብ ለመሳብ ደፋ ቀና ሲሉ ይስተዋላል። እዚህ ላይ ልብ ልንለው የሚገባው በዚህ ዘመን ውስጥ ብቅ ብለው በከሰሙትም፣ ተውተርትረው ቆይተው በተዳከሙትም፣ አዳዲስ ስም እየያዙ በተፈጠሩትም ድርጅቶች ውስጥ ዋነኛ ተዋናዮቹና የድርጅቶቹ ፈጣሪዎችም ሆኑ አጥፊዎቹ አንድ አይነት ሰዎች መሆናቸው ነው። ትላንት በአንድ ድርጅት ጥላ ስር ሆነው ሌሎችን እንደ ጠላት ይፈርጁ የነበሩ ሰዎች ዛሬ የብዙ ድርጅቶች ፈጣሪዎች ሆነዋል። ትላንት በጠላትነት የሚፈራረጁ ድርጅቶች አባል የነበሩ ሰዎች ቂማቸውን እንዳረገዙ ዛሬ በአንድ ድርጅት ጥላ ሥር የተሰባሰቡበትንም ሁኔታ እናያለን። በድርጅቶቹ መካከል እጅግ ጠባብ የሆኑ የርዕዮታለም ልዩነቶች ከመኖራቸው ውጭ አብዛኛዎቹ የመጨረሻ ግባቸው አንድ እና አንድ ነው። ዲሞክራሲ የሰፈነባት፣ የሕግ ልዕልና የተረጋገጠባት፣ ሰብአዊ መብቶች የተከበሩባት እና ድህነትን ያሸነፈች ኢትዮጵያን ማየት፣ መፍጠር ነው። በነዚህ መሰረታዊ ጉዳዮች ላይ የሚለያዩ ድርጅቶች ያሉ አይመስለኝም፤ ሊኖርም አይችልም። ልዩነቱ እነዚህ ግቦች ላይ ለመድረስ ድርጅቶቹ በሚከተሉት አቅጣጫና መንገድ ቅየሳ ላይ ነው።
በዚህ የ50 ዓመት ጉዞ ውስጥ በሽብር መንፈስና በነውጥ ተግባራት የተሞላው የኢትዮጵያ ፖለቲካ በድርጅቶች መካከል እርስ በርስ አለመተማመንንና መካካድን ፈጥሯል። ይህም አለመግባባቶቹ ከጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት አልፈው እልቂትን አስከትለዋል። በዚያም የተነሳ አገሪቷ በፍርሃት እንድትዋጥና ሕዝቧም በስጋት እንዲኖር፤ የፍርሃት ባህልም እንዲጎለብት ከፍ ያለ ሚና ተጫውቷል። ዛሬ በእያንዳንዳችን አዕምሮ ውስጥ በርካታ የልዩነት ግንቦች ተፈጥረዋል። በፖለቲካ ፓርቲዎች፣ በሲቪክ ማኅበራት፣ በኃይማኖት ተቋማት፣ በማኅበረሰብ ድርጅቶች መካከልም የበርሊን ግንብ አይነት ግዙፍ የልዩነት ግንቦች ተፈጥረዋል። የዛሬዎቹ ኃይሎች ከገዢው ፓርቲ በስተቀር በትጥቅ የተደራጁ ስላልሆኑ ነው እንጂ ለመጠፋፋት ቅርብ ናቸው። ትልቁና እያንዳንዳችን እራሳችንን ልንጠይቅ የሚገባን፤ እነዚህን ግንቦች ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዴት ንደን እና በላያቸው ላይ ተረማምደን ልብ ለልብ እንዋሃዳልን? እንዴት እንደ አንድ ሕዝብ የጋራ ዕራይ፣ የጋራ መዝሙር፣ የጋራ ህልም፣ የጋራ መፈክር፣ የጋራ መድረክና የጋራ አገር እንፈጥራለን? እንዴት ከቂም፣ ከበቀልና ከቁርሾ ሽረን ከታይታና ከቧልት ፖለቲካ ወደ እውነተኛ የፖለቲካ ሕይወት እንመለሳለን?
ለማጠቃለል ያህል በእኔ እምነት ከተተበተብንበት ውስብስብ ችግሮችና ከተጫነን የፍርሃት ድባብ ለመላቀቅ፤ አልፎም ጤናማ የሆነ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ሥርዓት ባለቤት የሆነ ማኅበረሰብ ለመፍጠር የሚከተሉት ተግዳሮቶች ቢቀድሙ ይበጃል እላለሁ::
-       ዛሬ ለፖለቲካ ንትርክና  እርስ በርስ መፈራራት እንደ ምክንያት የሚነሱት የታሪካችን ክፍሎች ከፖለቲካ፣ ከኃይማኖት እና ከሌሎች ወገንተኝነት ነጻ በሆኑ ምሁራን በአግባቡ የሚጠኑበት ማዕከል ቢኖረን። የመወዛገቢያ ነጥብ የሆኑትም ታሪካዊ ኩነቶችን በአግባቡ ቢጠኑ እና በተለያዩ መንገዶችም ተደግፈው ለማስተማሪያነት ቢውሉ በድንቁርና ላይ ከተመሰረቱት ታሪክ ጠቀስ የሆኑና በጥላቻ መንፈስ የተሞሉ ክርክሮች ወጥተን እውቀትን በዋጁ ውይይቶች ላይ እናተኩራልን።
-       የሩቁን ለታሪክ ምሁራን እንተወና ባለፉት አምሣ ዓመታት ከ1960 ዎቹ የተማሪዎች ንቅናቄ ጀምሮ በፖለቲካ ትግል ውስጥ ዋነኛ ተዋናይ የሆኑ ኃይሎች ዛሬም በአገሪቷ የለት ተዕለት የፖለቲካ ህይወት ውስጥ በግራና በቀኝ ሆነው እና በመቶ ድርጅቶች ጉያ ውስጥ መሽገው በአገሪቷና በድሃው ሕዝብ እጣፈንታ ላይ ወሳኞች ሆነው ቀጥለዋል። በተለይም ‘ያ ትውልድ’ በሚል የሚታወቀው የኅብረተሰብ ክፍል ከልጅነት እስከ አዋቂነት ክቡር ሕይወቱን፣ ጊዜውን፣ ገንዘቡን እና እውቀቱን ያለምንም ስስት የዛችን አገር እጣ ፈንታ ለማቅናት መስዋዕትነት ሲከፍል ቆይቷል፤ ዛሬም ዋነኛ ተዋናይና አድራጊ ፈጣሪ ሆኖ ቀጥሏል። ይህ ትውልድ ትላንትናም ሆነ ዛሬ በገዢና በነጻ አውጪዎቻች ቡድኖች ተፈራርጆ እርስ በርሱ ተጨራርሷል፣ ቂምና ቁርሾም ተጋብቷል፣ ተሰዷል አሰድዷል። ዛሬም በልቡ ቂም ይዞና በቀልን አርግዞ በተለያዩ ድርጅቶች ውስጥ መሽጎ የጎሪጥ ይተያያል። ባገኘው አጋጣሚም ሆሉ ይናቆራል። ‘ቂም ተይዞ ጉዞ’ እንዲሉ ትላንት በተለያዩ ድርጅቶች ውስጥ ሆነው በጠላትነት ይፈራረጁና ሊገዳደሉ ይፍላለጉ የነበሩ ሰዎች ይህን ሸክማቸውን በንስሃ እና በይቅር ባይነት ከላያቸው ላይ ሳያራግፉ ውስጥ ውስጡን እየተብሰከሰኩና እየተፈራሩ ገሚሶቹ በልጅነታቸው በቆረቡባቸው ድርጅቶች እየማሉ ቀሪዎቹም ዘመኑ በወለዳቸው አዳዲስ ድርጅቶች ውስጥ ሆነው የለበጣ ውህደት እየመሰረቱ በዋዜማው ይፈረካከሳሉ። እንደ እኔ እምነት ከዚህ የእርስ በርስ መፈራረጅ፣ መፈራራትና የቆየ ቂምና ጥላቻ ሳንሽር የምንክበው ካብ ሁሉ የእምቧ ካብ ነው የሚሆነው። እየሆነ ያለውም ይሄው ነው። ከዚህ አዙሪት ወጥተንና ከቂም ተላቀን የጋራ ራዕይ እንዲኖረን እያንዳንዱ ግለሰብ እራሱን ለይቅርታ ማዘጋጀት አለበት። ከልብ የበደላቸውን ይቅርታ ለመጠየቅና ይቅርታ ለመቀበል። ከድርጅታዊ ወገንተኝነትም እራሱን ነጻ አውጥቶ በሱና በድርጅቱ ላይ የተፈጸመውን በደል ብቻ ሳይሆን እሱም ጠላት ብሎ በፈረጃቸው ሰዎችና ድርጅቶች ላይ ያደረሰውን ግፍና በደል ለመናዘዝና ለደረሰውም ሁሉ አቀፍ ጥፋት ድርሻቸውን በድፍረት በማንሳት የተጠታቂነት ባህልን ‘ሀ’ ብለው ሊጀምር ይገባዋል።
-       ይህ ሁኔታም የደረሰውን የጉዳት መጠን በቅጡ እንድናውቅ ከማድረጉም ባሻገር እርስ በርስ የመወነጃጀሉን ታሪክ እንድንገታውና ልባችንንም በፖለቲካ ንስሃ አንጽተን የሚነገርለትን ያህል የተሳካ ባይሆንም እንኳ ልክ እንደ ደቡብ አፍሪቃው ‘በእውነት’ ላይ ወደ ተመሰረተ የእርቅ እና የሰላም መድረክ እንድቀርብ እድል ይፈጥርልናል።
-       የልጆቹን እርስ በርስ መጨራረስ እየተመለከት ፓለቲካ እንዲህ ከሆነ አርፎ መቀመጥ ይበጃል፤ እርም የፖለቲካ ነገር በሚል አይምሮውን ጥርቅም አድርጎ ዘግቶ የለት ጉርሱን ብቻ እየቃረመ የአገሩን የፖለቲካ እጣፈንታ ለእዝጌሩ ትቶ ደግ ቀንና መልካም አስተዳደርን እንደመና ከሰማይ እንዲወርድለት የሚጠባበቀውም የኅብረተሰብ ክፍል አይኑን ይገልጣል፤ ከመጠፋፋት ወደ ሰለጠነ የውይይት ባህል በሚሻገረው የፓለቲካ ኃይልም ላይ እምነት ያሳድራል፤ እራሱንም ከፍርሃት ነጻ አውጥቶ በሙሉ ልብ በአገሩ ጉዳይ ባለቤት ይሆናል።
-       ስለዚህም የገዢው ኃይል ወያኔ ካለበት ጥልቅ ፍርሃት እና የሥልጣን ጥም የተነሳ ለእንዲህ ያለው ለውጥም ሆነ የሰላምና የእርቅ ጎዳና ገና ዝግጁ ባይሆንም የተቀሩት የፖለቲካ ሃይሎች መንገዱን በመጀመር ለዘመናት በመካከላቸው የቆየውን ቁርሾና ቂም ከአዕምሯቸው በማውጣት ከልብ የመነጨ እርቅ በማድረግ የልዩነት ግንቦችን ማፈራረስ ይጠበቅባቸውል። የሰላም፣ የእርቅ እና የእውነት አፈላላፉ ጉባዔ ያስፈልገናል።
በእውነት ላይ ተመስርተው ተቃዋሚዎች በቅል ልቦና ከታረቁ አብረው ከሠሩ በኢትዮጵያዊና በኢትዮጵያዊያን ላይ ለዘመናት እንደ መዥገር ተጣብቀው ደማችንን የሚመጡትን፣ ክብራችንን ገፈው እርቃን ያስቀሩንን፤ ድኅነት፣ እርዛት፣ አንባገነናዊ ሥርዓትና ጭቆና፣ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት፣ ጦርነትና የእርስ በርስ ግጭቶች፣ ድንቁርና፣ ጨለምተኝነት፣ ፍርሃት፣ ሙስና እና ጥላቻን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ነቅለን መጣል እንችላለን። ቅን ልቦና ይኑረን! ለዘመናት የተጫነንን ሸክማችንንም እናራግፍ። ያኔ ለፍቅር በፍቅር፣ ለሰላም በሰላም፣ ለነጻነት በነጻነት፣ ለአንድነታችን በአንድነት የምንሰራበትና ታሪክ ዘካሪ ብቻ ሳንሆን ታሪክ ሰሪ የምንሆንበት ጊዜ እሩቅ አይሆንም።
ቸር እንሰንብት!
ያሬድ ኃይለማርያም
ከብራስልስ

No comments:

Post a Comment