Wednesday, December 4, 2013

ሂዩማን ራይትስ ዋች ሳዑዲ ስላሉ ኢትዮጵያዊያን ሥጋቱን ገለፀ

የመላ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት - መኢአድየሳዑዲ አረቢያ መንግሥት የጀመረውን ፍልሰተኛ ሠራተኞችን በኃይል የማስወጣትን እርምጃ ተከትሎ እዚያ የቆዩ ኢትዮጵያዊያን ፍልሰተኛ ሠራተኞች የአካላዊ ጥቃት ተጋላጮች መሆናቸውንና አንዳንዶቹም መገደላቸውን፣ ወደ ሃገራቸው ለመመለስ የሚፈልጉትም በጊዜያዊ ተነቃቃይ የማሠሪያ ማዕከላት ያለበቂ ምግብና መጠለያ መያዛቸውን ኒው ዮርክ የሚገኘው ዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ቡድን ሂዩማን ራይትስ ዋች ከትናንት በስተያ (ቅዳሜ፣ ኅዳር 21/2006 ዓ.ም) ማምሻውን ባሠራጨው መግለጫ አስታወቀ፡፡

ሂዩማን ራይትስ ዋች “በሳዑዲ አረቢያ የፀጥታ ኃይሎች እና በዜጎቿ ተፈፅሟል ወይም እየደረሰ ነው” ያለውን ጥቃትም የሳዑዲ አረቢያ መንግሥት በአፋጣኝ እንዲመረምርና የዚህ “የአመፃ ወንጀል” ያለው አድራጎት ተጠያቂዎች እንዲጠየቁ አሳስቧል፡፡

በሌላ በኩል በሺሆች ለሚቆጠሩት ኢትዮጵያዊያን ተመላሾች መጠለያና ምግብ ለማቅረብ የሳዑዲ መንግሥት በየቀኑ አንድ ሚሊየን ሪያል ወይም 267 ሺህ ዶላር እያወጣ መሆኑን ባለሥልጣናቱ መናራቸውን ሂዩማን ራይትስ ዋች በሪፖርቱ ላይ ጠቁሟል፡፡

የሂዩማን ራይትስ ዋች የመካከለኛው ምሥራቅ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ጆ ስቶርክ ሲናገሩ “የሳዑዲ ባለሥልጣናት ተመላሾቹን አስረው የያዟቸው በሰብዓዊ ሁኔታ ነው ቢሉም በሺሆች የሚቆጠሩ ሰዎችን ያስቀመጡት በጊዜያዊ ማዕከላት ውስጥ ያለበቂ ምግብ፣ መጠለያ እና የሕክምና እርዳታ በማያገኙበት ወደ ሰብዓዊ አደጋነት ሊያመራ በሚችል ሁኔታ ነው” ብለዋል፡፡

የሳዑዲ ባለሥልጣናት የያዟቸዋን እሥረኞች እንዲለቅቁ ወይም በአፋጣኝ ወደሃገራቸው እንዲመልሷቸው ስቶርክ መጠየቃቸውን ሂዩማን ራይትስ ዋች አሳስቧል፡፡
   
የመላ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት - መኢአድ
ይህ በእንዲህ እንዳለ “የሳዑዲ አረቢያ መንግሥት በኢትዮጵያዊያን ላይ የፈፀመው ድርጊት በሰው ልጅ ላይ የተሠራ ወንጀል ነው፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ጉዳቱን ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ማቅረብ አለበት” የሚሉ ሃሣቦች ትናንት (ዕሁድ፣ ኅዳር 22/2006ዓ.ም) የመላ ኢትዮጵያ ህዝብ አንድነት ድርጅት ባዘጋጀው ህዝባዊ ውይይት ላይ ተንፀባርቀዋል። 
 
“አሁን ያሉት የኢትዮጵያ መንግሥት መሪዎች ከኢትዮጵያዊነት የወደቁ ናቸው” ሲሉም አንድ ምሁር ተችተዋል።

መንግሥት ግን የተፈጠረውን ችግር ተገቢና ተመጣጣኝ በሆነ እርምጃ መፍትሄ እየሰጠ እንደሆነ ይናገራል።

መለስካቸው አምሃ ዝርዝሩን ይዟል፤http://amharic.voanews.com/content/ethiopia-hrw-returnees-aeup-scholars-12-02-13/1802170.html

No comments:

Post a Comment