Friday, December 13, 2013

ጄነራል ሳሞራ የኑስ በውጭ ተቃዋሚዎች የመለስን የበላይነት መስክረዋል አሉ

(ዘ-ሐበሻ) ኢሕአዴግ ለይስሙላ ያከብረዋል እየተባለ በሚተቸውና ለ8ኛ ጊዜ የተከበረውን የኢትዮጵያ ብሄሮች ብሄረሰቦችና ህዝቦች የሕገ መንግሥት ቀን በዓል ምክንያት በማድረግ መንግስት ባሳተመው ‘ሕብረ ብሔር’ መጽሔት ላይ ቃለ ምልልስ የሰጡት የጦር ኃይሎች ኤታማዦር ሹም ጀነራል ሳሞራ የኑስ መለስ ከሞተ በኋላ በውጭ ያሉ ተቃዋሚዎች የሟቹን አቶ መለስ ዜናዊን የበላይነት መስክረዋልና እናመሰግናቸዋለን አሉ። በሰራዊቱ ውስጥ እኩልነት እንዳለ መናገራቸውም ብዙዎችን አስገርሟል።
በከፍተኛ ህመም እየተሰቃዩ ነው በሚል በተደጋጋሚ ተጽፎላቸው የነበሩትና አሁንም ህክምና ሁልጊዜ እንደሚከታተሉ የሚነገርላቸው ጄነራል ሳሞራ ከመንግስታዊው መጽሔት “የቀድሞው የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ህልፈተ ሕይወታቸው በድንገት ከተሰማ በኋላ በውጭ የሚገኙ አንዳንድ ፀረሰላም ኃይሎች እና አንዳንድ ተቃዋሚዎች ኢትዮጵያ ለሽብርና ለሌሎች ፀረ-ሰላም ተግባር መጋለጧ አይቀርም ሠራዊቷም መዳከሙ አይቀርም በማለት ሲገልጹ ነበር። ይህ ሊሆን ያልቻለው ለምንድ ንነው ይላሉ? እነዚህ ወገኖች ይህን ተመኝተዋል ነገር ግን ያልሞከሩት ከምን አንፃር ነው?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ “ከመለስ በኋላ ሠራዊቱ ይዳከማል ብለው ማሰባቸው የመለስ አስተዋፅኦ ጠንካራ ሠራዊት እንዲኖር፣ ጠንካራ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ መከላከያ ኃይል እንዲኖር ያስቻለ ስለመሆኑ እውቅና መስጠት ስለሆነ እናመሰግናለን።” ካሉ በኋላ ቀጥለውም “ምክንያቱም መለስ ይህቺ አገር ጠንካራ የመከላከያ ኃይል እንዲኖራት ወሳኝ ድርሻ ነበረው ብለው ስላመኑ ነው ይህንን ማንሳት የጀመሩት፡፡ ይህን ማሰብ በመጀመራቸው ደግሞ መመስገን ይኖርባቸዋል፡፡” ብለዋል።
ሳሞራ በመንግስታዊው ጋዜጠኛ ለቀረበላቸው ለዚሁ ተመሳሳይ ጥያቄ በሌላ በኩል የአንድ ሰራዊት ጥንካሬ የሚለካው በሰራው አንድ ሥራ ብቻ አይደለም። ሠራዊቱ ይህቺ አገር እስካለች ድረስ አብሮ ይኖራል። ምክንያቱም ተቋሙ ቀጣይ ነው። ተቋሙ ለሁለት ነገር ብቁ መሆን አለበት። አንደኛ ለወቅታዊ ግዳጁ፣ ሁለተኛ ደግሞ ለወደፊት ለሚሰጥ ግዳጅ ብቁና ዝግጁ መሆን አለበት። የእያንዳንዱ አመራር ተልዕኮም ይሄ ነው። በተለይ የከፍተኛ አመራሩ ተልዕኮ ይህንን ማረጋገጥ ነው። ይሄን እንዴት እንፈፅመዋለን ለሚለው ደግሞ ሶስት መሰረታዊ ሥራዎችን በመሥራት ነው።
ዋናውና ወሳኙ የሰው ኃይሉን ማዕከል ያደረገ ሥራ መሥራት ነው። የሰው ኃይሉን ማብቃት። ቴክኒካዊና ሙያዊ እንዲሁም አካዳሚያዊ ብቃቱን ማሳደግ፣ ሳይንሳዊ ዕውቀቱን ማዳበር፡፡ እንግዲህ ሶስት የአቅም ግንባታ ሥራ መሥራት ዋነኛው ሆኖ የሰው ኃይል ማዕከል ያደረገ የአቅም ግንባታ ሥራ መስራት ያስፈልጋል። ሁለተኛው ሥራ በአደረጃጀቱና አሰራሩ ሕዝባዊ ባህሪውን እንደጠበቀ ከተልዕኮውና ከባህሪው የሚስማማ አደረጃጀትና አሰራር ያለው እንዲሆን ማድረግ ነው። አደረጃጀት አቅም ፈጣሪ ነው። አደረጃጀት ለዘለዓለም የሚኖር አይደለም። ከሁኔታው ጋር እየዳበረ አቅም እየፈጠረ የሚሄድ መሆን አለበት። አሰራሩም በተመሳሳይ ከሕዝባዊ ባህሪውና ከተልዕኮው የተጣጣመ አሰራር ዴሞክራሲ ያዊና ደስተኛ ሕይወቱን በአስተማማኝ የሚጠብቅ፣ የግዳጅ አስተሳሰቡንና ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰቦችን የሚያዳብሩ አሰራሮችን ማረጋገጥ ማለት ነው። አደረጃጀቱም፣ አሰራሩም፣ የሰው ኃይሉም ሦስቱን ሥራዎች በመሥራት ነው ለተጨባጭ ግዳጅም ሆነ ለወደፊት ለሚሰጠው ግዳጅም ዝግጁ የሚሆነው፡፡
“ስለዚህ ሠራዊቱ በዚህ እየተገነባ ስለቆየ ነው ውጤትም እየተገኘ የመጣው፡፡ ካብ አይደለም ሲሠራ የነበረው። ጠንካራ የመከላከያ ተቋም፣ ጠንካራ የመከላከያ ኃይል፣ ሕዝባዊ ባህሪውን የጠበቀ የመከላከያ ኃይል ነው ሲገነባ የነበረው። እና በዚህ ምክንያት ሊፈርስ አልቻለም፡፡ አይፈርስምም ይጠነክራል።
እነዚያ ወገኖች የተመኙትን አልሞከሩትም ማለት ግን አይደለም፡፡ የብተናና የተለያዩ ሥራዎችን አልሞከሩም ማለትም አይደለም። መከላከያ ሠራዊታችንን የሚያፈርሱት ሦስት ምክንያቶች ካጋጠሙ ብቻ ነው የሚል እምነት አለን። በንግግር አይፈርስም። በሦስት ነገር ግን ሊፈርስ ይችላል። አንደኛውና ዋናው ተልዕኮው ከተቀየረ ነው፡፡ እንግዲህ አሁን ተልዕኮው ሕዝባዊ ነው። የወረራ ተልዕኮ የለውም። የሠላም ተልዕኮ ነው ያለው፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ህዝብ ተስፋው ከሰላም እንጂ ከጦርነት አይደለም፡፡ ስለዚህ ከዋናው ተልዕኮ አንደኛው ሠላም ማረጋገጥ ነው። ይህ ደግሞ በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠለት ነው። ሁለተኛው ደግሞ የጦርነት አደጋ ካጋጠመ በአጭር ጊዜ እና በአስተማማኝ በመጨረስ ተመልሰን ወደ ልማታችን መግባት ነው።ሌላው ተልዕኮ ደግሞ የአፍሪካ ወንድሞቻችን ከእኛ ለሚፈልጉት ሁሉ አስፈላጊውን ድጋፍ ማበርከት ነው።
የእነርሱ ሰላም የእኛም ሰላም ስለሆነ በአቅማችን በሰላም ማስከበር ሥራ መሳተፍ ነው። አራተኛው ደግሞ በአገር ውስጥ ከፀጥታ ኃይሎች አቅም በላይ የሆነ ጉዳይ ካለ መሳተፍ። በህብረተሰቡ ላይ ሰብአዊና ተፈጥሮአዊ አደጋዎች ከአጋጠሙ የድርሻችንን መወጣት ነው። እነዚህ ተልዕኮዎች ሕዝባዊ ተልዕኮዎች ናቸው። ከሕገ መንግሥቱ የወጡ፣ የተቀዱ ተልዕኮዎች ናቸው።
“ሁለተኛው የሠራዊቱን ጥንካሬ ሊበረብር የሚችል ደግሞ የራሱ የሰራዊቱ የውስጥ ችግር ነው። ኢ-ዴሞክራሲያዊነት ከሰፈነ ሠራዊቱን ሊያፈርሰው ይችላል። ኢ-ዴሞክራሲያዊነት ከተፈጠረ በርካታ መዘዞች ይመጣሉ። ፀረ-ዴሞክራቲክ መሆን ከተጀመረ የህግ የበላይነት ይጣሳል ማለት ነው፡፡ በአንድ በኩል በህግና በአሰራር መሄድ ይቀራል። ሁለተኛ የሠራዊቱ ደስተኛና ዴሞክራሲያዊ ሕይወት ይበላሻል። ስለሆነም ጠንካራ አንድነት፣ አስተማማኝ አንድነት፣ የማይናወጥ አንድነት ያለውን ሠራዊት አንድነቱ እንዲናጋ ያደርገዋል። የጌታና የአሽከር አካሄድ ነው የሚኖረው፡፡ ይሄ ደግሞ ለአገሪቱም ለሁሉም አይጠቅምም።
“ሌላው ደግሞ ሙስና ነው። ሙስና ሠራዊቱን ሊያበላሸው ይችላል፡፡ ሙስና ፀረ ልማት ነው። ሠራዊቱን ሊበትነው እና ሕዝባዊ ባህሪውን እንዲያጠፋ ሊያደርገው ይችላል። አንድ ሠራዊት ሠራዊት ነው የሚባለው እንደ ወታደር እንደ አንድ አካል ሲያስብ እንጂ ለግሉ ሲያስብ አይደለም።
ለምሳሌ አንድ ወታደር በአንድ ሻለቃ ወይም በአንድ ቡድን ሊድን ከሆነ ሻለቃዋ መዳን አለባት፡፡ በሌላ በኩል አስሩ ከዳኑ ነው እርሱ መዳን የሚችለው። ቡድኑ ብቻውን ሊድን አይችልም። ስለዚህ ይሄ ሻለቃ አስሩን ማዳን አለበት።ወታደሩ መዳኑ የሚረጋገጠው አስሩ ከዳኑ ይሆናል። ብቻውን ሊድን ከፈለገ አይችልም። በተመሳሳይ አንድ የመቶ ካለችም ሶስት ቲም አሏት፡፡ የመቶዋ ልትድን ከሆነ ቲሟ መስዋዕትነት መክፈል አለባት፡፡ እንደዛ እያለ ነው የሚሄደው፡፡ ስለዚህ እንደ አንድ አካል የሚያስብ መሆን አለበት፡፡ ፀረ ዲሞክራሲ አካሄድ ካለ በውስጡ አንድነቱ ይላላል፤አስተሳሰቡም ይሸረሸራል ማለት ነው፡፡ ሙስናም በተመሳሳይ ለግል ማሰብን ይመጣል፤ ይህም ያፈርሰዋል። በአጠቃላይ በዚህ ነው የሚፈርሰው እንጂ በንግግርና በአሉባልታ አይደለም።” ብለዋል።
የአንድ ብሔር ተወላጆች በሰራዊቱ ውስጥ ቁልፍ ቦታ መያዛቸው፣ በትውልድ ብሔራቸው የተነሳም በሙስና ነቅዘው ሃብታም መሆናቸውን፣ መከላከያ ሰራዊቱም የሃገር ዘራፊዎች መሳሪያ መሆኑን በስፋት በሕዝብ ዘንድ የታወቀ ሆኖ ሳለ ኤታማዦር ሹሙ ይህንን ሽምጥጥ አድርገው በመካድ ለዚሁ መጽሄት “ወታደር ሲሆን ሕገመንግሥታዊ ሥርዓቱን የመጠበቅ ተልዕኮ ነው ያለው። ሌላ ምንም ነገር የለውም። ከሌላው ዓለም የእኛ ደግሞ ትንሽ ይለያል። ሕገመንግሥታዊ ሥርዓቱ የሚጠበቀው በሕዝቡ፣ በሠራዊቱም በሁሉም እኩል ነው፡፡ የሁሉንም ሕዝቦች ተጠቃሚነት ስለሚያረጋግጥ በተወሰኑ ምሁራን ብቻ የሚጠበቅ አይደለም፡፡ስለዚህ የሁሉንም ህዝቦች ተጠቃሚነት የሚያረጋግጠውን ህገመንግስት ሁሉም ህዝብ ማወቅ አለበት፡፡ ሁሉም ህዝብ ማወቅ አለበት ብቻ ሳይሆን እንዲያምንበትም መደረግ መቻል አለበት፡፡ካመነበት በኋላ ደግሞ እንደወታደር ለመጠበቅም ለመስዋዕት ራሱን ዝግጁ እንዲያደርግ ይገነባበታል።” ማለታቸው ትዝብት ውስጥ እንደጣላቸው ታዛቢዎች ይናገራሉ።
zehabesha

No comments:

Post a Comment