Monday, December 16, 2013

ይሄ ተንኮል ግን የህወሓት ዕድሜ ያራዝማል የሚል ግምት የለኝም።


ባለፈው ቅዳሜ ዓረና መድረክ በጠራው ህዝባዊ ስብሰባ ለመሳተፍ ወደ ማይጨው ከተማ ተጉዤ ነበር። ከመቀሌ -ማይጨው በመኪና የሦስት ሰዓት ጉዞ ነው። ከሰባት ዓመት በፊት የማውቃት ማይጨው ምንም አልተቀየረችም። ብዙ የህወሓት ባለስልጣናት እዛው ማይጨው ነበሩ። ስብሰባዎችና ስልጠናዎች ነበሯቸው።
ቅዳሜ ከማይጨው ወጣቶች ጋር ተገናኝቼ ነበር። ወጣቶቹ ለውጥ ይፈልጋሉ። ግን ይፈራሉ። የሰለማዊ ትግል ዉጤታማነት ይጠራጠራሉ። ህወሓት በምርጫ ስልጣን ሊያስረክብ ይችላል ብለው አያምኑም። በሰለማዊ መንገድ ከሚቃወሙ በትጥቅ ትግል ቢሳተፉ ይመርጣሉ። ምክንያቱም በትጥቅ ትግል ህወሓት ከስልጣን የሚባረርበት ዕድል ሊኖር ይችላል ብለው ያስባሉ።
Abraha Destaበማይጨው የሚገኙ የመንግስት ሰራተኞችም (በተለይ መምህራንና የግብርና ሰራተኞች) በስርዓቱ ቅሬታ አላቸው። የራያ አከባቢ ተወላጆች የሆኑ የህወሓት ካድሬዎችም በስርዓቱ ደስተኞች አይደሉም። ሁሉም ለውጥ ይፈልጋሉ። ግን ዓረና ህወሓትን ታግሎ ሊያሽንፈው ይችላል የሚል እምነት የላቸውም። በራያ ቦታ የሚገኙ የህወሓት አባላት (የራያ ተወላጆች) ህወሓትን ማሸነፍ የሚችል ተቃዋሚ ፓርቲ ካገኙ ህወሓትን እንደሚቃወሙ ይገልፃሉ።
የህወሓት መሪዎችም ይህንን ያውቃሉ። እንደዉጤቱም ህወሓት ከሌላ አከባቢ ታማኝ ካድሬዎች እየላከ የራሱ አባላት ይሰልላል፣ ይቀጣል፣ ያባርራል። በዚህ መንገድ የራያ ህዝብ በራሱ ሰዎች እንዲበደል ይደረጋል። የራያ ተወላጆች የሆኑ የመንግስት ሰራተኞች ለእንጀራቸው ሲሉ ህዝብ ይበድላሉ። ህዝብ ካልበደሉ ይቀጣሉ፣ ይባረራሉ፣ ሌላ የሚተዳደሩብት የስራ መስክ የላቸውም።
የራያ ቦታ በህወሓት ከተረሱ አከባቢዎች አንዱ ነው። የራያ ህዝብ የክረምት ምግብ የነበረ ‘በለስ’ ለምርምር ተብሎ በገባ የሀር ትል ምክንያት ከጥቅም ዉጭ ሁነዋል። መንግስት የበለስ ጉዳቱ ለማካካስ የወሰደው እርምጃ የለም። በብዙ የራያ ቦታዎች የዉኃ ችግር አለ። የዉኃ ችግሩ ለመቅረፍ ብዙ ጉድጓዶች የተቆፈሩ ቢሆንም የዉኃ ቦይ ማስገባት ባለመቻሉ እስካሁን የዉኃ አገልግሎት የማያገኙ የራያ ቦታዎች አሉ።
ከዓመታት በፊት ለመስኖ እርሻ እንዲዉል በጥናት መሰረት የተመረጠ ‘የጎልጎል ራያ’ ሜዳም እስካሁን አልተተገበረም። የህወሓት መሪዎች ጎልጎል ራያን በመስኖ የማልማት ዕቅድ ሰርዘውታል። ፕሮጀክቱ ለመሰረዝ የሰጡት ምክንያት በራያ የሚገኝ ዉኃ ‘ጨዋማ’ ስለሆነ ለመስኖ ጥቅም አይውልም የሚል ነበር። የሚገርመው ነገር ደግሞ አሁን ጎልጎል ራያ በኢንቨስትመንት ስም ለባለ ሃብቶች እየተሸጠ ነው የሚገኘው። ስለዚህ የህወሓት ሰዎች የጎልጎል ራያን በመስኖ የማልማት ፕሮጀክት የሰረዙበት ምክንያት ሰፊ ለም መሬቱ ለባለሃብቶች ለመሸጥ ስለፈለጉ ሊሆን ይችላል።
የራያ ህዝብ ጀግናው ጥላሁን ይግዛውን ለመዘከር ሐውልት ለመገንባት ተብሎ ከራያ ተወላጆች ወደ 700,000 ብር የሚጠጋ ገንዘብ ከሰባት ዓመት በፊት የተሰበሰበ ሲሆን እስካሁን ድረስ ምንም ነገር አልተሰራም። የራያ ህዝብ ለጥላሁን ይግዛው ሐውልት ለመስራት የተሰበሰበ ገንዘብ የት እንዳለ ማወቅ ይፈልጋል፣ ይጠይቃል። አስተዳዳሪዎቹ የሰጡት መልስ ገንዘቡ ለኮብልስቶን አውለነዋል የሚል ነበር። ህዝቡም ኮብልስቶን የራሱ በጀት እንዳለው ሲከራከር ደግሞ አስተዳዳሪዎቹ ገንዘቡ የት እንዳለ እንደማያውቁ ይናገራሉ።
በማይጨው አከባቢ በሚገኙ ተቋማትም የሙስና አሰራሮች መኖራቸው ኗሪዎች ይናገራሉ። በዚሁ ምክንያት የችፑድ ፋብሪካ፣ ማይጨው ግብርና ኮሌጅና ማይጨው ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በተመሳሳይ ሁኔታና ወቅት የዳታ ኮምፒተሮች እንዲጠፉ ተደርገዋል። የዳታ ኮምፒተሮች እንዲጠፉ ሲደረግ ተቋማቱ ኦዲት እንዳይደረጉ ይረዳል። ኦዲት ካልተደረጉ ሙስና መሰራቱና አለመሰራቱ ለማወቅ ይከብዳል። የሙስና ጉዳይ ይፈተሽ።
ቅዳሜ ማይጨው በነበርኩበት ሰዓት በከተማው የኢንተርኔት አገልግሎት አልነበረም። ለዚህም ነበር ስለ ማይጨው ሁኔታ በወቅቱ መፃፍ ያልቻልኩ (ኢንተርኔት መጠቀም የሚቻለው በሞባይል ብቻ ነበር)። በወቅቱ የዓረና የማይጨው ከተማ አባላት የማይጨው ህዝብ ዓረና ፓርቲ በጠራው የእሁድ ህዝባዊ ስብሰባ እንዲሳተፍ ይቀሰቅሱ ነበር። ህዝቡም ለዓረና ጥሩ አመለካከት ነበረው። የዓረና አባላት ‘ዓረና’ የሚል ፅሑፍ ያለው ነጭ ቲ-ሸርት ለብሰው ነበር የሚቀሰቅሱ።
የህወሓት ሰዎችም ህዝብ በዓረና ስብሰባ እንዳይሳተፍ ለማድረግ የራሳቸው ቅስቀሳ ጀመሩ። ህወሓቶች ትልቅ ስፒከር ተጠቅመው በዕለተ እሁድ (በዓረና ስብሰባ) በማይጨው ከተማ የእግር ኳስ ውድድር ስላለ መላው ወጣት ተጫዋቾችን እንዲደግፍና እንዲያበራታታ ያውጁ ነበር።
የራያ ተወላጆች ያልሆኑ ካድሬዎች ለራያዎቹ በእሁድ ቀን በሚደረገው የዓረና ስብሰባ ሰው እንዳይሳተፍ እንዲመክሩና እንዲያስፈራሩ ተነገራቸው (ይህ መረጃ የተገኘው ከካድሬዎቹ ከራሳቸው ነው)። በስብሰባው የተሳተፈም እንዲመዘግቡ ትእዛዝ ተሰጣቸው። በተጨማሪም ሰው ለመያዝ ሲባል የተለያዩ ያልታሰቡ የህዝብ ስብሰባዎች ተጠሩ። አብዛኛው የማይጨው ወጣት በራሳቸው ስብሰባ እንዲገኝ አዘዙት። የችኮማዮና የመኾኒ ‘ስራ አጥ’ ወጣቶች ‘ስራ እንዲሰጣቸው’ ለእሁድ ስብሰባ ተጠሩ። እሁድ በስብሰባው የተገኘ ስራ እንደሚሰጠው፣ ያልተገኘ ግን ስራ እንደማያገኝ ተነገረው።
የማይጨው ህዝብም ለህወሓት ታሪክ ለመጀመርያ ግዜ የሙዚቃ ባንድ እንደሚመጣለት ሲነገረው ነበር። ህወሓት በማይጨው ከተማ የሙዚቃ ኮንሰርት ሲያዘጋጅ (ወይ አዘጋጃለሁ ሲል) ለመጀመርያ ግዜ ነው። ይህም ዓረና ህዝባዊ ስብሰባ በጠራበት ቀን ነው። እሁድ ቀን በስብሰባው ተሳታፊ ስለነበርን ህወሓቶች የራሳቸው ስብሰባ ስለማካሄዳቸው ሙሉ መረጃ አልነበረኝም። የሙዚቃ ኮንሰርቱ ስለ መሳካቱም እርግጠኛ አይደለሁም። የሙዚቃ ኮንሰርቱ ያልታቀደና ያልታሰበበት ስለነበረ ያልተሳካ ሙከራ ሊሆን ይችላል (ከተጋበዙት ሙዚቀኞች ቅሬታ ያሰሙ ነበሩ፤ በቂ ግዜ ስላልተሰጣቸው)።
እሁድ ጠዋት ሰው ዓረና ወደ ጠራው ስብሰባ መግባት ከመጀመሩ በፊት የተወሰኑ የፀጥታና የፕሮፓጋንዳ ሐላፊዎች አደራሹ አከባቢ ተሰብስበው ነበር። ወደነሱ አከባቢ ስንሄድ ተበትነው ጠፉ። አብዛኞቹ የማይጨው ካድሬዎችና ፖሊሶች ግን ተባብረውናል። ተሳታፊ እንዲሰልሉና እንዲያስፈራሩ የተላኩ ካድሬዎች ከጎናችን ነበሩ። ‘እንደምንም ብላቹ ህወሓትን ማባረር የምትችሉ ከሆነ ከጎናቹ ነን’ ይሉን ነበር። ላደረጉልን ትብብር እናመሰግናለን። ህወሓትን ከስልጣን ማባረር የምንችል ግን ሁላችን ስንተባበር ነው።
ህዝብ ወደ አደራሹ ገባ። ስብሰባውም ተጀመረ። እኛ ስለ ህወሓት መጥፎነትና የለውጥ አስፈላጊነት አወራን። ህዝቡም አስተያየት ሰጠ። ከህዝቡ የተረዳነው ነገር ቢኖር የራያ ህዝብ የህወሓትን መጥፎነት ከኛ በላይ ያውቃል። የህዝቡ ጥያቄ ህወሓትን እንዴት ከስልጣን ማውረድ ይቻላል? ዓረናስ አንዴ እየመጣ፣ ብዙ ግዜ እየጠፋ ህወሓትን ማሸነፍ ይችላል ወይ? ዓረናን ብንደግፍና ህወሓትን ከስልጣን ማባረር ባንችል ዋስትናችን ምንድነው? ህወሓት ሽፍታ ነው፤ ሊያጠፋን ይችላል ወዘተ የሚሉ ሐሳቦች ተነስተዋል።
ህዝቡ በሰጠው አስተያየትና ትንተና ተገርምያለሁ። ህዝቡ ለውጥ ይፈልጋል። በህወሓት መሪነት እምነት የለውም። ህዝቡ ያጣው ነገር ህወሓትን ሊያባርር የሚችል ዓቅም ያለው የተቃዋሚ ፓርቲን ነው። ህዝቡ የሚመራው ፓርቲ ካገኘ ለመታገል ዝግጁ ነው። ዓረና ቆራጥነት ካለው ህዝቡ ከዓረና ጎን ተሰልፎ እንደሚታገል ቃል ገብተዋል።
የማይጨው ስብሰባ ለየት የሚያደርገው ተሰብሳቢው በሙሉ የህወሓት ተቃዋሚ መሆኑ ነው። የህወሓት ካድሬዎች አልነበሩም። ሁላችን በአንድነት ለመታገል ቃል ስንገባ በአደራሹ የነበረ ሁሉ ቃሉ ሰጠ። አብረን ለመታገል ቃል ገባን። (ኩልና ብሓባር ንምቅላስ ንዓሪ ኢልና ዓረና)። ሦስት ሰዓት ተኩል የጀመረ ስብሰባችን ዘጠኝ ሰዓት ተኩል ተጠናቀቀ።
እኔ የተረዳሁት ነገር አለ። የህወሓት ስጋት ዓረና አይደለም። የህወሓት ስጋት የህዝብ ማወቅ ነው። ህወሓት የትግራይ ህዝብ የፖለቲካ እውቀት እንዲኖረው አይፈልግም። ምክንያቱም የትግራይ ህዝብ የፖለቲካ ንቃተ ህሊናው ከፍ ካደረገ ለህወሓት ካድሬዎች አሜን ብሎ አይገዛም። ካልተገዛ ደግሞ የህወሓቶች ህልውና ያበቃል። የህወሓቶች ጥረት ህዝብ በስብሰባው እንዳይሳተፍና አማራጭ ሐሳብ እንዳይሰማ መከልከል ነበር። ህወሓት የሚሰጋው ዓረና እንዳይቃወመው ሳይሆን ህዝቡ ፖለቲካ አውቆ እንዳይቃወመው ነው።
ይሄ ተንኮል ግን የህወሓት ዕድሜ ያራዝማል የሚል ግምት የለኝም።
It is so!!!

No comments:

Post a Comment