Saturday, December 7, 2013

መድረክ የጠራው ሰልፍ ተከለከለ


 December 5, 2013
የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ህዳር 29 ቀን 2006 ዓ.ም ለማድረግ ያሳወቀው ሰልፍ ተከለከለ፡፡ መድረክ ሰልፉን ለመጥራት በሀገራችን መሰረታዊና ወቅታዊ የሆኑ ችግሮችን እንዲሁም በሰውዲና በአለም ዙሪያ በኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ ያለው ሰቆቃ መሰረቱ የስደት መንስኤው ላይ በመሆኑ መንግስትን በሰላማዊ ሰልፍ ለመጠየቅ እንደነበር ለማወቅ ችለናል፡፡
ሰልፉን ለማድረግ የታቀደው ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ አምስተኛ በር ፊት ለፊት ከሚገኘው የመድረክ ቢሮ በመነሳት በአምስት ኪሎና ስድስት ኪሎ አድርጎ ወደ ጠቅላይ ሚኒስትር ፅ/ቤት ድረስ ለመጓዝ ነበር፡፡ ነገር ግን የአድስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከንትባ ፅ/ቤት “ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ እውቅና የጠየቃችሁበት ስፍራ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስብሰባና የሰላማዊ ሰልፍ አሰራር ስነ-ስርዓት አንቀፅ አምስት ሀ እና መ የሰላማዊ ሰልፍ የማይካሄድባቸው ቦታዎች ተብለው የተጠቀሱ በመሆናቸው የተጠየቀው የሰላማዊ ሰልፍ እውቅና መስጠት የማንችል መሆናችንን እንገልፃለን” ሲል መልስ ሰጥቷል፡፡
በጉዳዩ ላይ አስተያት እንዲሰጡ የጠየቅናቸው የመድረክ ስራ አስፈፃሚና የአንድነት ፓርቲ ዋና ፀሀፊ አቶ አስራት ጣሴ “መልሱ የመድብለ ፓርቲ ቅልበሳ ከመሆን አይዘልም” ይላሉ፡፡ አስተዳደሩ ጠቅሶ እውቅና ለመንፈግ የተጠቀመበት ደንብ ማንም የሚያውቀው መሆኑን የተናገሩት አቶ አስራት በማያውቁት ህግ እንደማይደኙ ገልፀውልናል፡፡ በተጨማሪ በዚህ ጉዳይ ላይ የወጣው አዋጅ መወቅ ቢችሉ እንኳ በተባለው ደንብ እንደማሻር አክለዋል፡፡
በ1983 ዓ.ም የወጣው የሰላማዊ ሰልፍና ህዝባዊ ስብሰባ አዋጅ (አዋጅ ቁጥር 3 1983) የተከለከሉ ብሎ የሚጠቅሳቸው ቦታዎች እንደሌሉና ከኤምባሲዎች፣ ት/ቤቶች፣ ሆስፒታሎች፣ የሀይማኖት አምልኮ ስፍራዎች፣ በገበያ ቀን (ከገበያ ስፍራ) መቶ ሜትር መራቅ እንዳለበት ማዘዙን አቶ አስራት ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ከጦር ካምፕና የደህንነት ተቋማት 500 ሜትር መራቅ እንዳለበት አዋጁ ማስገደዱን ያስረዱት አቶ አስራት ከዚህ ቀደም አንድነት መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም በጠራው ሰልፍ ይህንን አዋጅ በመሻር በጦር ካምፕና በደህንነት መስሪያቤቶብ በተከበበው ጀንሜዳ እንድንወጣ ነግረውናል ብለዋል፡፡
በተሰጠው መልስ ላይ አቋም ለመያዝ የመድረክ አመራር እንደሚሰበሰብ ከአቶ አስራት ጣሴ ለማወቅ ችለናል፡፡

መድረክ ህዳር 5 ቀን 2006 ዓ.ም መድረክ ለጠራው ሰልፍ አስተዳደሩ ከተደራራብ የስብሰባ ጫና የተነሳ የፖሊስ ሀይል ስለሌለኝ ጥበቃ ለደደርግለት አልችልም በሚል እውቅና መንፈጉ ይታወቃል፡፡

No comments:

Post a Comment