Saturday, December 7, 2013

አቃቤ ህግ በእነ አቶ ያረጋል አይሸሹም ላይ ቅጣቱ እንዲከብድ ጠየቀ


December 7/2013
የፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህግ በከባድ ሙስና ወንጀል ጥፋተኝነታቸው የተረጋገጠውን የቀድሞው የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሠ መስተዳደር አቶ ያረጋል አይሸሹምን ጨምሮ በሁሉም ተከሣሾች ላይ የሚወሠነው ቅጣት እንዲከብድ ጠየቀ፡፡ አቃቢ ህግ ጉዳዩን ሲከታተል ለቆየው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 15ኛው ወንጀል ችሎት በፅሁፍ ባቀረበው የቅጣት አስተያየት፤ በአንድ ክስ ጥፋተኛ የተባሉት አቶ ያረጋል እና በሶስት ክሶች ጥፋተኛ የተባሉትን የቀድሞው የክልሉ ም/ቤት አፈ ጉባኤ እና የትምህርት ቢሮ ሃላፊ አቶ ሃብታሙ ሂካ እንዲሁም በመጀመሪያው ክስ 3ኛ እና 4ኛ ተከሣሽ ሆነው ጥፋተኝነታቸው የተረጋገጠው፡፡ አቶ ጌድዮን ደመቀ እና አቶ አሠፋ ገበየሁ ላይ ቅጣቱ ይክበድልኝ ሲል አመልክቷል፡፡ የቅጣት ማክበጃ ምክንያቶቹም 1ኛ እና 2ኛ ተከሣሽ ከፍተኛ ስልጣን የነበራቸው በመሆኑ፣ 3ኛ እና 4ኛ ስልጣን ባይኖራቸውም በልዩ ወንጀል ተካፋይ በመሆናቸውና የቅጣት እርከኑም ከፍተኛ ስልጣን ባላቸው ስር የሚታይ በመሆኑ እንዲሁም ሁሉም ተከሣሾች በመንግስት ላይ ከባድ አላማ በመያዝ በጣም ከፍተኛ ጉዳት ያደረሡ በመሆናቸው የሚሉት ናቸው፡፡ በተመሣሣይ አቃቤ ህግ ከ2ኛ እስከ 3ኛ ባሉት ክሶች ጥፋተኛ የተባሉት ሁሉም ተከሣሾች በከፍተኛ ስልጣን፣ በጣም ከፍተኛ ጉዳት እና ከባድ አላማ በሚሉ የወንጀል ደረጃ መግለጫዎች እንዲያዝለት በቅጣት አስተያየቱ አመልክቷል፡፡ ቅጣቱ በሁሉም ተከሣሾች ላይ እንዲከብድለት የጠየቀው አቃቤ ህግ አቶ ሃብታሙ ሂካ፣ አቶ ጌዲዮን ደመቀ፣ አቶ አሠፋ ገበየሁ በ3 ግዙፍ ክሶች ጥፋተኝነታቸው የተረጋገጠ በመሆኑ የእያንዳንዱ ክስ የቅጣት ውሣኔ ከተላለፈ በኋላ የእስራትና የገንዘብ መቀጮው ተደምሮ እንዲወሠን አመልክቷል፡፡ በአንድ ክስ ብቻ ጥፋተኛ የተባሉት አቶ ያረጋል አይሸሹም፣ የጋድ ኮንስትራክሽን ድርጅት ስራ አስኪያጅ አቶ ገዛኸኝ አድገህ፣ የየኮለን ኮንስትራክሽን ስራ አስኪያጅ አቶ መክብብ ሞገስ ላይም ቅጣቱ ከብዶ እንዲወሠን አቃቤ ህግ ጠይቋል፡፡ ፍ/ቤቱም የተከሣሾችን የቅጣት ማቅለያ አስተያየት ለመቀበል መዝገቡን ለታህሣስ 15 ቀጥሯል፡፡

No comments:

Post a Comment