Wednesday, December 4, 2013

ማኅበረ ቅዱሳን ከስደት ተመላሾችን ለመደገፍ እንደሚሠራ አስታወቀ አትም ኢሜይል ኅዳር 24 ቀን 2006 ዓ.ም.



በእንዳለ ደምስስ

ማኅበረ ቅዱሳን ከሳውዲ አረቢያ ተመላሽ ወገኖቻችንን ለመደገፍ ቀጣይ ሥራዎችን እንደሚሠራ አስታወቀ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ከሳውዲ አረቢያ በመመለስ ላይ ለሚገኙ ከ2ሺሕ በላይ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ኅዳር 23 ቀን 2006 ዓ.ም. ቦሌ በሚገኘው የስደተኞች ጊዜያዊ መቀበያ ጣቢያ በመገኘት የምሳ ግብዣ ባደረገበት ወቅት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ ማኅበሩ በዚህ በጎ አድራጎት ተግባር ላይ ለመሳተፍ የተነሣበትን ምክንያት ሲገልጹ “ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ክርስትናም፤ እንደ ዜግነት የወገኖቻችን በዚህ ሁኔታ ላይ መገኘት ያስጨንቀዋል፡፡ ችግሩንም ለመፍታትና ወገኖቻችንን ለመደገፍ ማኅበራችን የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንዳለበት በማመን በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ ይህ የምሳ ግብዣ የመጀመሪያ ምዕራፍ ሲሆን ወንድሞቻችንና እኅቶቻችንን ለመደገፍ ምእመናንንና አባላትን በማስተባበር ቀጣይ ሥራዎችን እንሠራለን፡፡” ብለዋል፡፡
አቶ ተስፋዬ አያይዘውም እነዚህ ወገኖቻችን ሠርተው በሚልኩት ገንዘብ በርካታ ቤተሰብ የሚተዳደር በመሆኑ ቤተሰብ እንዳይበተን፤ ተማሪዎች ከትምህርታቸው እንዳይደናቀፉ ከፍተኛ ሥራ መሠራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጀምሮ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ በዚህ ሀገራዊ በሆነ ችግር ላይ መፍትሔ ለመሻት እየተንቀሳቀሰች መሆኗንና፤ ማኅበረ ቅዱሳንም በጋራ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር እንደሚሠራ በመግለጽ ምእመናንና አባላትም ማኅበሩ የሚያከናውነውን ተግባር እንዲደግፉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አቶ ምሕረተአብ ሙሉጌታ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፕሮቶኮል ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራልና የጊዜያዊ ጣቢያው ከስደት ተመላሾች ጉዳይ አስተባባሪ ከስደት ተመላሾችን አቀባበል በተመለከተ ሲገልጹ “ከመንግሥት ጥረት ጎን ለጎን የተለያዩ የንግድ ማኅበረሰብ አባላት፤ ማኅበራትና በጎ አድራጊ ግለሰቦች ከስደት ተመላሽ ወገኖቻችንን ለመርዳት ድጋፍ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ 79ሺህ ኢትዮጵያዊያን ወደ ሀገራቸው የተመለሱ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 49 ሺሕ ወንዶች፤ 26ሺሕ ሴቶች እንዲሁም ከ3ሺሕ በላይ ሕፃናት ናቸው፡፡”በማለት ገልጸዋል፡፡ አስፈላጊውንም ምዝገባና መስተንግዶ እየተደረገላቸው ወደየትውልድ ቀዬአቸው የመመለስ ሥራዎች እየተሠሩ እንደሚገኙ የገለጹት አቶ ምሕረተአብ ማኅበረ ቅዱሳንና ሌሎችም ማኅበራት እያደረጉ ላሉት ወገኖቻችንን የመርዳትና የመደገፍ ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

አቶ መስፍን መንግሥቱ “ኢትዮጵያዊያን ለኢትዮጵያዊያን” በሚል ከነጋዴው ኅብረተሰብ የተቋቋመ ማኅበር አስተባበሪ ሲሆኑ ቦሌ በሚገኘው ጊዜያዊ የስደተኞች መቀበያ ጣቢያ ሲያስተባብሩ አግኝተናቸው ላቀረብንላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ “የተፈጠረው ድንገተኛ ችግር እጅግ አስደንጋጭ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን በዚህ ወቅት ተባብረን ፈጣን ምላሽ መስጠት ይጠበቅብናል፡፡ በዚህም መሠረት ወገኖቻችንን ለመርዳት ተሰባስበን ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለዶክተር ቴዎድሮስ አድኀኖም ደብዳቤ በማስገባት ድጋፍ መስጠት እንደሚገባን ተወያተናል፡፡ የተቀደሰ ዓላማ በመሆኑም ወደ ተግባር መግባት ትችላላችሁ በማለት ፈቃድ ሰጥተውናል፡፡ ስደተኞቹ መግባት ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ በአጭር ሰዓት ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ በማሰባሰብ ከመስተንግዶ ጀምሮ እየሠራን እንገኛለን” ብለዋል፡፡

ከስደት ከተመለሱት መካከል ስሟን መግለጽ ያልፈለገች አንዲት እኅት በሳውዲ አረቢያ ስለነበረው የሥራዋ ሁኔታ ስትገልጽ “ከሀገሬ ከወጣሁ ሁለት ዓመት ሆኖኛል፡፡ ሁለት ሕፃናት ልጆቼን ትቼ ያልፍልኛል ብዬ ነበር አወጣጤ፡፡ ነገር ግን እዚያ የገጠመኝ እጅግ አስከፊ ሁኔታ ነበር፡፡ ከአሰሪዬ ቤት ውጪ ለሦስት ቤቶች በነጻ እንድሠራ አድርጋኛለች፡፡ ለምን ብዬ በጠየቅሁበት ወቅት ደብድባኝ ጎኔን ኦፕራሲዮን እሰከመሆን ደርሻለሁ፡፡ ሃያ አራት ሰዓት ያለማቋረጥ እንድሠራ ስታደርገኝ ቆይታለች፡፡ ከዚህ ሥቃይ በሀገሬ ልሙት ብዬ ነው የመጣሁት” በማለት ተናግራለች፡፡

No comments:

Post a Comment