Sunday, November 3, 2013

አርቲስት ደበበ እሸቱ ባለው የፖለቲካ ተሳትፎ ምክንየት ብሔራዊ ትያትር እንዳይገኝ እና ስሙ እንዳይጠራ ተወሰነበት


አርቲስት ማለት በተፈጥሮ ያገኘውን ጸጋ ተጠቅሞ መልእቱን ማስተላለፍ የሚችል በስዕል፣ በሙዚቃ፣ በስነጽሁፍ፣ በቲያትር… ሊሆን ይችላል፡፡ አርቲስቶችም ይህን ጸጋ ተጠቅመው ሰዎችን በዙሪያቸው በማሰባሰብ ህልሞቻቸውን ወይም ያለውን ነባራዊ ማህበራዊና ስነልቦናዊ ጉዳዮች እያነሱ ሰላምን አንድነትን ፍቅርን ይሰብካሉ፤ በስራዎቻቸው ሪፖርት ያደርጋሉ፤ ይተንትናሉ፤ ይቀሰቅሰቀሉ፤ አንዳንድ ድብቅና የታፈኑ ጉዳዮችን ያላቸውን ፀጋ ተጠቅመውም ያጋልጣሉ፤ ብቻ በአጠቃላይ አርቲስቶች ከማዝናናት በዘለለ በአንድ ማህበረሰብ ውስጥ በሚፈጠር እድገት ትልቅ ሚና ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ናቸው፡፡
በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባለ ምስቅልቅል ባለ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ቀውስ ውስጥ በምትገኝ ሀገር ከሁሉ በተሻለ አርቲስቶች ህብረተሰቡን የማረጋጋትና የማቀራረብ እንዲሁም ውስጣዊ ሰላሙን እንዲያገኝ የማስቻል፤ ሀገሪቷንም ነባራዊ ሁኔታ የማሳየትና መፍትሄዎችን እስከመጠቆም ይጠበቅባቸው ነበር፡፡ ነገር ግን እንዳለመታደል ሆኖ ከማንም በከፋ እንደውም አርቲስቶቻችን ለማህበረሰቡ ማበርከት የሚገባቸውን አገልግሎት ትተው፤ ጭራሽ ለየትኛውም ወጣት እና ህጻናት አርአያ መሆን የማይችሉ ንዋይ አምላኪዎች ሆነው እነሱ ራሳቸው ችግር እየሆኑብን ተቸገርን፡፡
እንዲህ እንዳወራ ያደረገኝ ባለፈው ሳምንት ይድነቃቸው ከበደ “በ1ኪሎ ቁርጥ ሥጋ እና በ12 ድራፍት ብርጭቆ – እውነትና ከሕደት…” ብሎ የጻፈውን እንዳነበብኩ በእያንዳንዱ የህብረተሰብ ክፍል ውስጥ ያለው የመንፈስ ክስረትና ክሽፈት ከስርአቱ ጋር የሚደረገውን ትግል ምን ያህል ከባድ እንዳረገው ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፡፡ አርቲስት ደበበ እሸቱ (ጋሽ ደቤ) በኢትዮጵያ ውስጥ አሁን በህይወት ካሉት አርቲስቶች ግንባር ቀደሙና አንጋፋው ስለመሆኑ ለመከራከር መሞከር ሞኝነት ነው፡፡ ጋሽ ደቤ የሰራቸውን ስራዎች መጨረሻ ላይ በከፊል ለማስቀመጥ እሞክራለሁ ግን፡፡ ግን ዛሬ “አርቲስት” ነን የሚሉ ሰዎች ይህንን አንጋፋ የሙያ አባታቸው እና መምህራቸው ፤ እነ ጋሽ ደበበ በስንት መስዋዕትነት የከፈቱላቸውን መንገድ ተጠቅመው ዛሬ ለደረሱበት ደረጃ ሲያበቋቸው ባያመስግኗቸው እንኳ ምናለ እውቅና እንኳ ባይነፍጓቸው፡፡ ጋሽ ደቤ ስንት ትያትሮችን ያዘጋጀበት የተወነበት በስራ አስኪያጅነት የመራበትእና ያስተማረበት ብሔራዊ ትያትር በህይወት ያሉ እና የሌሉ አንጋፋ አርቲስቶችን ለማመስገንና ለማወደስ ያዘጋጀው ፕሮግራም ላይ ጋሽ ደቤን ባለው የፖለቲካ ተሳትፎ ምክንየት እንዳይገኝ እና ስሙ እንዳይጠራ በስምምነት መወሰናቸው፤ ከመካከላቸውም ይህንን ተቃውሞ አንድም አርቲስት ድምጹን ለማሰማት አለመሞከሩ ያለንበት ማህበራዊ ዝቅጠት ደረጃን ዘግናኝ አድርጎታል፡፡ ጋሽ ደቤ በግል ህይወቱ ለማንኛውም ወጣት አርአያ መሆን የሚችል ጠንካራ ቤተሰብ ያለው የተረጋጋ እና ለህሊኒው የሚገዛ ስለመሆኑ የኔ ዲስኩር ሳይሆን እየኖረ ያለው ህይወት ምስክር ነው፡፡ ጋሽ ደቤ እንደሌሎቹ አርቲስት ነን ባዮች ቢያጎበድድ ምናልባትም ሀገሪቷ ውስጥ ካሉ ሚሊየነሮች ተርታ ተሰላፊ እንደ ሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡
በጅብ ሊቀመንበር በጦጣ ጸሀፊ
አንቺ ሰባ ሰባት ቶሎ ቶሎ እነፊ፤
ነበር ያለው የወሎ ሰው፤ ጋሽ ደቤ ለታሪክ የሚተላለፉ ህያው ስራዎች ሰርቷል እነዚህን ስራዎቹን በምንም ሊፍቋቸው እና ሊያጠፏቸው አይችሉም፡፡ የእውነት ዘመን ሲመጣ ለአደባባይ ይበቃሉ፡፡ አያድርገውና ጋሽ ደቤ የሆነ አደጋ ላይ ቢሆን እነዚህ የብሔራዊ ትያትር “አርቲስቶች” የጋዜጦችና መጽሔቶች የሽፋን ገጾችን እንዴት እንደሚያጨናንቁ አስቡት ዛሬ ግን የብሔራዊ ትያትር እንዳይጋበዝ ሲከለከል እንዳቸውም ድምጻቸን ለማሰማት አልደፈሩም፡፡ ነገር ግን ጋሽ ደቤ የእውነት ስራዎቹን የሚያደንቁለትና የእሱን አርአያ የሚከተሉ ወጣቶች አሉ፡፡
“አያናግረንም የያዘን አባዜ
ዝም አያሰኘንም የያዘን አባዜ
እንደው ፍዝዝዝዝ ያሰኘናልሳ
ቅጥ አምባሩ ያጣ የቁም ሞት አባሳ፡፡”
እስቲ ጋሽ ደቤ ከሰራቸው ስራዎች ውስጥ በጥቂቱ እንያቸው፤ በሃገር ውስጥ ካለው ታዋቂነትና ለሙያው ካደረገው አስተዋጽኦ ለመጠቀስ ያህል ፡-
በመድረክ ላይ
በቤተኪነጥበባት ወቴአትር
ያላቻ ጋብቻ ተዋናይ
ሮሚዎባ ዡልየት ተዋናይ
ጠልፎ በኪሴ ተዋናይም አዘጋጂም
ዳንዴው ጨቡዴ ››
ዘ ጌም ኦፍ ቼዝ (በእንግሊዝኛ) ተዋናይ
ኦቴሎ (በአንግሊዝኛ) ተዋናይም አዘጋጂም
አዳ ኦክ አራክል (በእንግሊዝኛ)ከሎ.ጸ.ገ.መ ተዋናይ
በቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ(ብሔራዊ) ቴአትር
የበጋ ሌሊት ራዕይ ተዋናይ
አንድ ዓመት ከአንድ ቀን ተዋናይ
እናት ዓለም ጠኑ ተዋናይ
ኪንግ ሊር ተዋናይ
ዋናው ተቆጣጣሪ ተዋናይ
ጠያቂ ተዋናይ አዘጋጅ
በቀይካባ ስውር ደባ አዘጋጅ
ተሓድሶ አዘጋጅ
የአዘውንቶች ክበብ አዘጋጅ ተዋናይ
በሃገር ፍቅር ቴአትር
ጠልፎ በኪሴ አዘጋጅ/ተዋናይ
የወፍ ጎጆ ተዋናይ
ኪንግ ሊር ተዋናይ
የቬኒሱ ነጋዴ ተዋናይ
ናትናኤል ጠቢቡ ተዋናይ
ድብልቅልቅ ተርጓሚ/ ተዋናይ
ማዕበል ተርጓሚ አዘጋጅ
በፊልም በሃገርና በዓለም አቀፍ
ዘ ሴይለር ፍሮም ጂብራልታር
ሻፍት ኢን አፍሪካ
ጉማ
ዚ አፍሪካን ስፓይ
ዜልዳ
አፍሪካ
ዘግሬቭ ዲገር
ዘ ግሬት ሪቤሊየን
እነዚህ ለምሳሌ ያህል የቀረቡ እንጂ የደበበ ስራዎች በርካቶች ናቸው፡፡ ከመድረክና ፊልም ስራዎቹ ባሻገር ተማሪዎችም አሰልጥኗል፡፡ ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን በብሔራዊ ቴአትር የተዋንያን ስልጠና ማዕከል ሲያቋቁሙ ከመምሃራኖቹ መሃልና በግምባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው መምህር ደበበ ሲሆን ለተማሪዎቹም መማርያ እንዲሆን የተረጎመው የስታንስላቭስኪ የተዋናይ ሀሁ ለበርካታዎች የሙያ ተማሪዎች የሙያቸው ፊደል መቁጠርያ ሆኖ ይገ ኛል፡፡
በትርጉም በኩልም ደበበ ከቴአትር
ያልታመመው በሽተኛ
ድብልቅልቅ
ጎርፉ
ከመጽሐፍ ደሞ
የዳዊት ወልደጊዮርጊስን
የደም እንባ
የራሱን ወጥ ሥራ በተመለከተ
የእምነቴ ፈተና
ሊጠቀሱ የሚችሉ ናቸው
ደበበ ለአፍሪካ ጥበብ ያለውን አመለካከትና ግንዛቤ ከቅኝ ገዢዎች ትርጓሜ ለማውጣትና ሶስተኛው ዓለም ኋላ ቀር ሲባልም በኤኮኖሚና በቴክኒዮሎጂ እንደሆነ፤ ይህም የሆነው ነጩ የአፍሪካን የዋህነት፤ እንግዳ ተቀባይነትና ሩህሩህነት መንጠላጠያ በማድረግ ቅኝ አድርገው ህሊናውን ስለዘጉበትና ስላሰሩት መሆኑን፤በባህል በኩል ግን ጨርሶ ሊደርሱበት የማይችሉትና ሊያጠፉትም ያደረጉት ሙከራ ዋጋ ቢስ ሆኖ እንደቀረ የሚያስረዳ ጥናታዊ ጽሁፍ በማቅረብ ተቀባይነትን አግኝቶ ድል ያደረገና፤ ቀደም ሲል የጀመረውን ትግል አጠናክሮ በመቀጠል በ1985 ዓ/ም እንደ አውሮፓውያን ቆጣጠር በርሊን ላይ በተካሄደው የዩኔስኮ የባህል(አይ ቲ አይ) ኢንተርናሽናል ቴአትር ኢትዮጵያን ወክሎ በመገኘት በአፍሪካ ውስጥ የመጀመርያው ፕሮፌሽናል ቴአትር ቤት የሃገር ፍቅር ቴአትር መሆኑን በማስረጃ አስደግፎ ተቀባይነትን አገኘ፡፡ በዚሁ ዓመት የዩኔስኮ የባሕል ክፍል አይ ቲ አይ የአፍሪካ ተጠሪ ሆኖ በመመረጥ፤ በዚያው ዘመን ዝምባብዌ ላይ በሚካሄደው ቴአትር ለልማትና ዕድገት ወርክሾፕ ላይ በመሪነት እንዲገኝ በዩኔስኮ ተወክሎ በመሄድ ወርክሾፑን በአጥጋቢ ችሎታውና የአመራር ብቃቱ ከመፈጸሙም ባሻገር ለብዙ ጊዜ ተሞክሮ ሲወድቅ ሲነሳ የነበረውን የአፍሪካ የመድረክ ባለሙያዎች ማሕበርን አስተባብሮ በማቋቋም የማሕበሩም መስራች ፕሬዜዳንት ሆኖ ለ12 ዓመታት መርቷል፡፡ አሁንም መስራች ፕሬዛዳንት በመባል ይጠራል፡
ደበበ በችሎታውና በብቃቱ በማስተባበር ችሎታው ዩኔስኮ ዓለም አቀፍ የቴአትር ኢንሳይክሎፒዲያን ለማዘጋጀት ሲወስን ደበበንም አፍሪካን በመወከል የኤዲቶርያል ቦርድ አባል አድርጎ መድቦት ሥራውን በሚገባ ተወጥቷል፡፡
ደበበ ቴአትር ለልማትና ለእድገት በሚል የሚታወቀውን የቴአትር ዲሲፕሊን ስልጠና ለበርካታ ሃገራት ባለሙያዎች ያስተማረ ሲሆን በርካታ ወርክሾፖችም በየሃገራቱ እየተጋበዘ መርቷል፡፡ ይሀን ዘዴ ካዋቀሩትም አምስት አፍሪካዊ ባለሙያዎች አንዱ ደበበ ነው፡፡
ወርክሾፕ የሰጠባቸው ቦታዎች፤
ታንዛኒያ፤ኡጋንዳ፤ኬንያ፤ማላዊ፤ኮንጎ ብራዛቪል፤አይቮሪ ኮስት፤ ካሜሩን፤ ናይጄርያ፤አይርላንድ፤ብራዚል፤ሰሜን አሜሪካ፤እንግሊዝ፤ ኩባ፤ በርሊን፤ካናዳ ይገኙበታል፡፡
ደበበ ላለፉት ከ40 በላይ ዓመታት በቴአትር ጥበብ ውስጥ ኖሮ በ1995 በተካሄደው ሃገራዊ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ‹‹ቀስተደመና›› የፖለቲካ ፓርቲን ተቀላቅሎ፤ በኋላም ቅንጅት ሲፈጠር የምክር ቤት አባልና የሕዝብ ግንኙነት በመሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረገ ቅንጅትን ለድል ያበቃ፤ የሬዲዮና የቴሌቪዥን ዝግጅቶቹ ገዢውን ፓርቲ ያንበረከኩና ቅንጅትና ያገዘፉ ነበሩ፡፡በዚህም ከሌሎች አመራሮች ጋር ለአንድ ዓመት ከአስር ወራት ለእስር ተዳርጓል፡፡ እንዲሁም በ2002 በድጋሚ ለአንድ አመት ታስሮ ተፈቷል፡፡
በሱ ሙያ የተሰለፉ ‹‹አይተነው ጊዜ›› ሲሉ እሱ ግን ‹‹እኔም ድርሻ አለኝ›› በማለት ቤተሰቡን፤ ምቾቱን፤ ተድላውን፤ ሁሉ ችላ በማለት ክግል ይልቅ ለህብረተሰቡ፤ ከራሱ ይልቅ ለወገኑ በመወገን የተሰለፈ ብቸኛ የጥበብ ሰው ነው፡፡አንዳንዶች ሹመትና ገንዘብ ሲያታልላቸው፤ እሱን ያታለለው ግን ነጻነት ፍትህና ዴሞክራሲ ከሰብአዊ መበት መከበር ጋር ነው፡፡ለዚህም ነው ከማንም በላይ ሕዝባዊ የክብር ዘውድ የተደፋለት፡፡ ዛሬ ያንን ዘውድ ደፍቶ ባናየውም ታሪክ ግን እንዳለበሰው ይኖራል አንድ ቀን ይሀም ይፋ ሆኖ ይከበራል፡፡
ደበበ በሃገሩ ለመሸለም ባይበቃም በዓለም አቀፍ ደረጃ ግን ለሽልማቶች የበቃ ባለሙያ ነው፡፡ለዚሁ የሙያ አስተዋጽኦ ክፍተኛው ክብሩ በአትላንታ ጆርጂያ ኖቬምበር 24 የደበበ እሸቱ ቀን ተብሎ እንዲሰየም የከተማው ምክር ቤት ማጽደቁ ነው፡፡
ጋሽ ደቤ ጋደኛም ሚስትም ከሆነችው ከአልማዝ ደጀኔ ጋር 4 ልጆች እና 6 የልጅ ልጆች ያሉት ሲሆን ሰኔ 2005 ዓ.ም 40ኛ ዓመታቸውን ከልጆቻቸው እና የልጅ ልጆቻቸው በተገኙበት አክብረዋል፡፡
ፍቅር ሰላም እና ጤና ለጋሽ ደቤ አብዝቶ ይስጥልን!
(የጋሽ ደቤን ስራዎች በተመለከተ ወንድወሰን አንድአርጋቸው 2001 ዓ/ም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ለመመረቂያ ካዘጋጀው ሥራ እንዲሁም “የእምነቴ ፈተና “ ከሚለው የጋሽ ደቤ መጽሐፍ መግቢያ ላይ አለምፀሀይ ወዳጆ ከጻፈችው ምስክርነት የተገኘ ነው)

No comments:

Post a Comment