Thursday, November 28, 2013

በደላላ ሃገር ሰትመራ! በታደለ መኩሪያ


በደላላ ሃገር ሰትመራ! በታደለ መኩሪያበትግራይ ሕዝብ ነፃነት ግንባር ሽፋን፤ ዛሬ ይህቺን ጥንታዊት ሃገር ኢትዮጵያን እየመራት ያለው ወያኔ የሚባል ቡድን ነው። ይህ የጭንጋፍ ስብስብ  በትግራይ ሕዝብ ልባስ የኢትዮጵያን ለም መሬትና ቡቃቅላ  ልጆቿን በደላላነት ለሳውዲ አረቢያ ሲያቀርብ መቆየቱን ዓለም ያወቀው ፀሐይ የሞቀው ሐቅ ነው። የዚህ ቡድን የጥቅማጥቅም ተቋዳሾችና አልጠብባዮች ጋር በመተባበር ቤሔራዊ ኩራታችንን አደጋ ላይ ጥለውታል።እነዚህ የዕንግዴ ልጆች  ሆድ አደሮች ፤ትውልድም፣ የገዛ ልጆቻቸው የሚያፍሩባቸው ናቸው። ይህቺን በደምና አጥንት የቆመች ሃገር በአደባባይ እንድትዋረድ አደርገዋታል፤የቤሔራዊ ውርደት እንድንከናነብ አድርገውናል፤ በአባቶቻችን መሰዕዋትነት ለዘመናት  አንገታችንን  ቀና እንደላደረግን ዛሬ በውርደታችን አፍረን አቀርቀረናል። ውርደታችንን ከማይጠገን ደረጃ ያደረሰው ደግሞ  የአዲሰ አባባ ከተማ ኗሪ ሕዝብ በልጆቹ ላይ በሳውዲ አረቢያ በተፈጸመው የግድያ፤የአስገድዶ መድፈርን፣ የንብረት ዘረፋውን ተቋሞ ለማሰማት  ወደ ሳውዲ ኢንባሲው በሄዱት ዜጎች ላይ ድብደባና እስራት መፈጸሙ ወያኔ የሳውዲ አረቢያ ደላላ ጥቅም አስጠባቂ፣ አለቅላቂ ቡድን መሆኑን ፍትው አድርጎ አሣይቶናል። የኢትዮጵያ ሕዝብ ልጆቹንና ቤሔራዊ ክብሩን  አስቀምቶ ይቀመጣል ማለት የማይታሰብ ነው። ይህ ወደፊት የምናየው ነው። አንድ መታወቅ ያለበት ለራሱ ነፃነት ከራሱ በላይ የሚያውቅለት እንደሌለ ነው። የተቃዋሚ ድርጅቶች መሪዎች ለራሳቸው ነፃነት የሚወጉ ከሆነና በተግባራቸው የተመሠከረላቸውን መከተሉ ከታለመው ግብ በጋራ ለመድረስ አስፈላጊ ነው። የፓለቲካው ጫወታ ሲደራ አለን ማለት የቢሊጮን ተረት ነው የሚሆነው።አስታውሳለሁ 1961 ዓ ም ነበር፤ አንድ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሲሪያ አይሮፕላን ማረፊያ  በኤርትራ አመጸኞች ቦንብ ይጣልበታል፤ ያንን የሰማ የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍቃድ ከመንግሥት ሳይጠይ ዳር እስከዳር  ወጥቶ አረቦች ይውጡልን  በሚል ቁጣውን ገለጿል። እንኳንስ እስራትና ድብደባ ግልምጫም አልደረሰበትም፤  ወታደሩ ሲቨል ለብሶ ተካፋይ እንጂ ቆመጥ ይዞ ዜጎችን አልደበደበም። በአሁኑ ጊዜ በአዲስ አበባ የሚገኙ የተቋሚ ድርጅቶች  ማወቅ ያለባቸው  ቤሔራዊ  ክበሬ ተነካ የሚል ዜጋን ወንጀሉን የፈጻሚውን ቡድን  ፍቃድ ጠይቀን ሰላማዊ ሰልፍ እንወጣለን ማለት በሕዝብ ቆጣ ላይ ውኃ መቸለስ ነው።  ውርደት አድራሹን  ፍቃድ ጠይቆ አደባባይ ከመውጣት ለሕዝቡ ያለውን ነግሩ መቀመጡ ይመረጣል። ሕዝቡ በሚፈልገው መንገድ  ቤሔራዊ ኩራቱን ማስከበር ይችላል፤ ማንም ሊያስጠብቅለት እንደማይችል አምኖም የራሱን ምርጫ ይወስዳል፤ እንዲወስድ መተውው ከጣልቃ ገብነት ያድናል።  ከግሩ ጥፍር እስከ ፀጉሩ ጫፍ የታጠቀውን ቡድን የሕዝብ ኃይል ሸባ እንደሚያደርገው እያወቅን አፍ ሞልቶ ኢትዮጵያ መንግሥት አላት  ማለቱ ከቃል ያለፈ በተግባር የሚታይ አይደለም፤ የሚታየው የወያኔ መንግሥት ነኝ ባዩ ዜጎችን ከአጸመ ርስታቸው አፈናቅሎ ለአረቦች ለቻይናዎች ለሕንዶች ለም መሬቷን ሸጦ፣ ያ ሳይበቃው  ዜጎቿን ለባርነት  በደላላነት የሚሸጥን ቡድን አፍ ሞልቶ መንግሥት ነው ማለት የፍረሃት መግለጫ ከመሆን ሌላ  ፍቺ የለውም።
<!–[endif]–>
ስለ ፍረሃት ከተነሣ በሕበረተሰባችን ከጥንት ጀምሮ የሚፎከር ፉከራ ልተርክላችሁ፤
 የአካባቢዬ ጎሮምሶች ለአቅመ አዳም የደረሱ የተፈሪ ሱሪያቸውን እጀጠባብ ሸሚዛቸውን ለብሰው፤ ቡሽ ባርኔጣቸውን ደፍተው፣ መውዜር ጠመጃቸውን በትከሻቸው አድርገው፣ ይህቺን ሲንኝ ሲያጎራጉሩ በልጅነቴ፣ እነርሱን ለመሆን ነበር ምኞቴ፤
ይሙት ጎበዝ፣
ይሙት ጅግና፣
ፈሪ ይኑር ቢሻው፣
አተላ መሸከም ይችላል ትከሻው። የሚል ነበር።
ይህቺን ስንኝ በአንድ ወቅት  አንድ አዛውንት ለኔው ለራሴ ደገሙልኝ። አስተማሪ ሆኛለሁ በጣም የጣፈጠ ኑሮ እኖራለሁ፣የፍረሃት ችግኙ በእኔ ውስጥ እያቆጠቆጠ መሆኑ ይሰማኛል፣ ግን አውጥቼ አልነገረውም፣ ፈሪ ላለመሆኔ  ማስተባበያዎቼ በሽበሽ ናቸው፣ እንደአስፈላጊነታቸው እመዛቸዋለሁ።አንድ አባባል አለ ‘የስው ፍረሃቱ ከነፃነቱ የመሸሹ መገለጫ ነው’ ይላሉ።  እኛ አዛውን ያቺን ስንኝ በፉከራ ለኔ ያሉበትን ምክንያት ልተርክላችሁ፤
ዓመተ ምህረቱ 1967 በሚያዚያ ወር ነበር፤ ሥፍራው ባሌ ጎባ ነው፤ ደግለሃን ጋሻ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ቡድንና የፖሊስ ሠራዊት ቡድን መካከል የእግር ኳስ ውድድር ለዋንጫ ይደረጋል። የመጫወቻው ሜዳ በፖሊስ ቅጥር ጊቢ ነበር። የፖሊሱ ቡድን በግብ ሲበለጥ ቡጢ ይጀመራል፤ ጫወታውን ዳኛው አቁሞ ፣ተመልካቹም ወደየቤቱ ያመራል። ወጣቶች እየጨፈሩ ሲወጡ አንድ ዘብ የቆመ ፓሊስ ተኩሶ አንዱን አስራ ሁለት ዓመት ዕድሜ ያለውን ይገለዋል። በነጋታው የሁለተኛ ደረጃው ተማሪዎችና መምህራን ሥራ ያቆማሉ፤ በአካባቢው የነበሩ የስድስት አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህራን  የሥራ ማቆሙን ተግባር ይቀላቀላሉ፤ የክፍለ ሃገሩ ምክትል አስተዳዳሪና የለውጥ ሃዋሪያቱ አስር አለቃ መምሀራንን ሰበስበው ወደማስተማሩ ሥራ እንዲመለሱ ከማስጠንቀቂያ  ጋራ ትዕዛዝ ይሰጣሉ። የሁለተኛ ደረጃ መምህር የነበረው አስፋው ዘለቀ ተነስቶ ‘የዚህ ተማሪ ደም ፍትህ ካላገኘ ማስተማሩም መማሩም ፋይዳ የለውም’ ብሎ ተቀመጠ። መምህራኑም በሥራ ማቆሙ ጸኑ፣ ተማሪዎቹም ወደየመጡበት ወረዳዎች ተበተኑ።
በወቅቱ በደርግ ጽፈት ቤት የአስተዳደር ክፍል ተጠሪ የነበረው ሻለቃ ደበላ ዲንሳ ሦስት ራሱን ሆኖ ሉካን መርቶ ወደክፍለሃገሩ መጣ። የመምህራኑ ተወካዮችን ጠርቶ ስብሰባ እንዲጠሩ አዘዘ። መምህራን በትምህርት ቤቶች ጽፈት ቤት ቅጥር ጊቢ መስክ ላይ ተሰበሰቡ።ሻለቃ ደበላ ስለአብዮት ደሰኮረ፤ አንድ መምህር ተነሣና ሻለቃ አንተ ሐረር ውስጥ ቀይ ኮፍያ በማድረጋችን ኮሚኒስት ትለን ለነበርነው ስለአበዮት ለእኛ አትነግረንም ብሎት ተቀመጠ። አንደኛ መምህር ተነስቶ ጥያቄው ስለቅሪላ ማልፋት ጎል ማግባት አይደለም። ወታደር ሥልጣን ላይ ወጥቷል ብለው መሣሪያቸውን ወደሕዝብ ያዞሩት ፓሊሶች አስቁምልን ነው ጥያቄው ብሎት ተቀመጠ። መምህር አስፋው ዘለቀ ከመቀመጫው ተነሳ፡ የሁለት ወር ዕድሜ ያለው ሕፃን ልጅ አባት ነኝ፤ እንዲህ በሃገሬ ፍትህ መጓደሉን በግልጽ ገብቶኝ ኖሮ ትዳሩም በቀረበኝ ልጁም ባልተወለደ ነበር፤ መቅደም ያለበትን ባለማስቀደሜ አዝናለሁ ብሎ ተቀመጠ። በሦስተኛው ቀን አነጣጣሪ ተኳሾች ተመርጠው በፓሊስ ሲሲና አይሮፕላን መጥተው አሰፋው ዘለቀ ከሚዝናናበት ቡና ቤት በራፍ ላይ ጠብቀው አነጣጥረው ገደሉት።
አስከሬኑን ከሆስፒታሉ ታዛ ሥር ባለው ጠረጴዛ ላይ ያጋደሙትን፣ ከበን፣ ስናለቅስ  በአካባቢው የሚያውቁኝ አዛውት ጋቢ ለብሰው ፈንጠር ብለው ከቆሙበት ጠቀሱኝ፤ አኔም ሄድኩኝ፤ ስማ አሉኝ ‘እናንተ ወንዶቹ ምን ይሁን ብላችሁ ነው የምታለቅሱት?’  ይሙት ጎበዝ፣
ይሙት ጀግና፣
ፈሪ ይኑር ቢሻው፣
አተላ መሸከም ይችላል ተከሻው። ብለው ተኮሳትረው ሄዱ።
መምህር አስፋው ዘለቀ፤ ዕውቅ ወጣት ገበሬዎች የዓለም ማያ መሩቃን ነጋሽ ሣህሌ ታደሰ ይርገጤ ፍትህ በሌለበት ምንም ሊሠራ እንደማይቻል አውቀው እንዲቻል ለማድርግ ሲታገሉ አለፉ። እኔን መሰሉ አተላ መሸከምን ሥራችን ያደረግን ይሄው አለን፤ በወቅቱ ሃያ ሰባት ሚሊዮን የነበረው የሕዝባችን ቁጥር ወደ ዘጠና ሚሊዮን ተቃርቧል፤ አንድ ዮኒቨርሲቲ የነበረው ሰላሳ ሁለት ሆኖል፤ የመምህራኑ ቁጥር የተማሪዎቹ አምስት እጥፍ ጨምሯል፤ ግን ስንቱ መምህር ተማሪ ስለፍትህ አውቆ እየታገለ ነው? ከሃገር የተሰደደው ዜጋ ቁጥር የደብረዘይትን ከተማ ኗሪ ያህላል፤ የሃገራችን መሬት በውጭ ሃገር ተይዞ የነበረው የኢንባሲዎች መኖሪያ ብቻ ነበር፣ ዛሬ ከትግራይ ክፍለሃገር በስተቀር  በቀሩት ክፍለሃገሮች ባዕዳን ለም መሬቶቻችንን በልማት መልክ ተከራይተው ለተወሰነ ጊዜ ብቻ  እንዳያመርት ባልታወቀ ነጥረ ነገር አፈሩን እንዳሻሮ እየቆሉት ነው። መምሀር አሰፋው  ዘለቀ የጠየቀው የፍትህ ጉዳይ እስከዛሬ መልስ አላገኘም። ከነአካቴው ዜጎች ሃገር አልባ እየሆኑ ነው ፣ የተፈጠሩባትን ምድር ተነጥቀዋል፤  በትግራይ ሕዝብ ነፃነት ግንባር ደላላነት ለም መሬታችንም  ልጆቻችን ተሸጠው  ከነ አረጓዴው ቢጫው ስንደቃችን ‘ከልብ ውሻ’  እየተባሉ በሳውዲ አረቢያ ሲገደሉ፣ ሴት ልጆቻችን ለአራት ለአምስት ሲደፈሩ አይተን እንዳላየን ነን፤ የዓለም ሕዝብ ያየው ስለሆነ  ለማስተባበል ብንሞክር ግምል ሰርቆ አጎብሶ ሆኖብናል፤ ለዚህ ውርደት መንስኤውም ፣ መፍትሔውም፣ ያለው በእኛው  በኢትዮጵያውያ እጅ ነበር። የተሰበረን ቅስም ለልጅ ልጅ ማስተላለፍ ወይም እንደመምህር አስፋው ዘለቀ ከሁሉም በፊት ፍትህ ይቅደም  ብሎ ዳር እስከዳር በዚህ ጠባብ ቡድን ላይ ከመነሣት ሌላ አማራጭ የለንም። ይህን የአረብ ምደኛ ደላላ የሆነ መንግሥት ነኝ ባይ ጭንጋፈ ማስወገድ ወይም ቤሔራዊ ክብርን አስረክቦ አንገትን ደፍቶ በባርነት መኖር ሌላው ምርጫችን ነው። በተለይ የትግራይ ክፍለሃገር ሕዝብ በሰሙ የሚደረገውን የኢትዮጵያዊነት የማዋረድ ተግባር የለሁበትም ፣ በስሜም መጠቀሙ ይቁም  ማለት አለበት። የዛሬውን ጥቅም በማየት ይህ ውርደት አይመለከተኝም  ቢባል አንኳን ታሪክ መሠረቱን አይስትም። ያለንበት ዘመን ታሪክ አጣሞ የሚታለፍበት ዘመን አይደለም። ለትውልድ ለሚተላለፈው አሳፋሪና አንገት አስደፊ ተግባር አካል ያለመሆንን ማሳወቁ በራሱ  ለልጅ ልጅም  ክብርና አኩሪ  ታሪክም ነው።ኢትዮጵያ በቆራጥ ልጆቿ  ቤሔራዊ ክብሯን ታስመልሳለች!
ታደለ መኩሪያ    

No comments:

Post a Comment