Friday, November 22, 2013

Blue Party Ethiopia

የዜጎችን ሰቆቃ እና በደል ችላ ማለት ከግፈኞች ጋር እንደመተባበበር ይቆጠራል!!
******************************************************** ሰማያዊ ፓርቲ በሳውዲ አረቢያ የሚገኙ ዜጎቻችን ላይ የሳውዲ መንግስት እያደረሰ ያለውን እስራት፣ ስቃይ እና ግድያ በመቃወም እና ህይወታቸው ላለፈ፣ ለተደበደቡ እንዲሁም የአካል ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች ህዝቡ ሃዘኑን እንዲገልጽ በመጪው እሁድ በሚደረገው ታላቁ ሩጫ ላይ የሚሮጡ ተሳታፊዎች ጥቁር ሪቫን አድርገው እንዲሮጡ ጥሪ ማስተላለፉ የሚታወቅ ነው፡፡ ይሁን እንጂ የታላቁ ሩጫ አስተባባሪዎች ይህንን ጥሪ እንደሚቃወሙት እና በፕሮግራሙም ላይ ጥቁር ሪቫን ያሰረ ተሳታፊን እንደተሳታፊ እንደማይቆጥሩ መናገራቸው ፓርቲያችንን እጅግ አሳዝኖታል፡፡ ፓርቲያችን ይህንን ጥሪ ሲያስተላልፍ አላማው ፍጹም ፖለቲካዊ አንድምታ የሌለው ሲሆን ጥያቄውም በዜጎች ላይ የሚደርሰውን ጥቃት እና ግድያ እንዲቆም እና ፍትሃዊ እርምጃም እንዲወሰድ ለመጠየቅ ብቻ እና ብቻ እንጂ ሌላ አላማ እንደሌለው እየታወቀ የታላቁ ሩጫ አስተባባሪዎች ግን ጉዳዩ ከፖለቲካ ጋር ለማያያዝ መሞከራቸው የሚያስተዛዝብ እና ህዝባዊ ወገንተኝነታቸውን ጥያቄ ውስጥ የሚከት ነው፡፡ ስፖርት ሰላማዊ ነገር የሚሰበክበት እንዲሁም እኩይ ተግባራት የሚወገዙበት መድረክ ነው፡፡ በአለማችን ላይ በተለያዩ ጊዜያት በተከሰቱ አሰቃቂ ሰው ሰራሽ አደጋዎች በተለያዩ ስፖርታዊ ዝግጅቶች ላይ ሲወገዙ እንዲሁም ለሰለባዎች ሃዘን የመግለጽ ስነ ስርዓትና የህሊና ጸሎት ሲደረግ መመልከት የተለመደ ነው፡፡ ታዲያ በጠራራ ፀሀይ በአደባባይ እናት ልጆችዋ ፊት እንዲሁም ሴት ልጅ ቤተሰቦችዋ ፊት ስትደፈር ከማየት የዘለለ ምን እኩይ ተግባርስ ሊኖር ነው? ታዲያ ስፖርት ይህንን ካላወገዘ ምንን ሊያወግዝ ነው? በመጨረሻም የታላቁ ሩጫ አስተባባሪዎች የፓርቲውን ጥሪ መቃወማቸው ፓርቲያችንን ያሳዘነ እና ያስቆጣ መሆኑን እየገለጽን አሁንም ፓርቲያችን በድጋሜ በዝግጅቱ ላይ ተሳታፊዎች ጥቁር ሪቫን አድርገው እንዲሮጡ እየጠየቀ ጥቁር ሪቫኖችን ማግኘት ለማትችሉ በሰማያዊ ፓርቲ ጽህፈት ቤት ተገኝታችሁ መውሰድ የምትችሉ መሆኑን እናስታውቃለን፡፡ ክብር ለዜጎቻችን ይሁን!!

No comments:

Post a Comment