Sunday, November 3, 2013

“ከ6 ሚሊዮን የኢህአዴግ አባል አንዱ ብሆን ምን ችግር አለው;” አቶ ልደቱ አያሌው



አቶ ልደቱ አያሌው
“ከ6 ሚሊዮን የኢህአዴግ አባል አንዱ ብሆን ምን ችግር አለው;”
አቶ ልደቱ አያሌው
“ወ/ት ብርቱካን የተሰጣት ኃላፊነት አግባብ አይደለም”
“እንባ አውጥቼ አልቅሼ ኃላፊነት በቃኝ እያልኩ ነው የተመረጥኩት”
“ከኢንጂነር ኃይሉ እንዲሕ ያለ ውሸት አልጠብቅም ነበር”

CC“የእስክንድር ነጋ ጋዜጣ ቅንጅትን ወደተሳሳተ አቅጣጫ ገፍቷል”አቶ ልደቱ አያሌው በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ጎልተው መውጣት የጀመሩት በ1990ዎቹ ሲሆን፣ ከምርጫ 97 ዋዜማ አንስቶ አነጋጋሪነታቸው በእጅጉ ጨምሯል፡፡ ከሁለት ዓመት የእንግሊዝ ቆይታ በኋላ ወደ ሀገር ቤት ከተመለሱት አቶ ልደቱ አያሌው ጋ፣ የሎሚ መፅሔት አዘጋጅ ቶማስ አያሌው ያደረገው ቆይታ እንደሚከተለው አሰናድቶታል፡-
ሎሚ፡- ለረዥም ጊዜያት ከሚዲያም ከፖለቲካም ርቀኻል፤ በሠላም ነው;
ልደቱ፡-እንደሚታወቀው ሀገር ውስጥ አልነበርኩም፡፡ በኢዴፓ ውስጥ የነበረኝን የሥራ አስፈፃሚ ኃላፊነትም አስረክቤ ስለነበር ወደ ሚዲያ የምመጣበት ዕድል አልነበረም፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ ፖለቲካችን ወደተስተካከለ መስመር ለመግባት ስለተቸገረ፤ አንዳንድ ጊዜ ለሀገር፣ ለሕዝብ ይጠቅማል ብለህ የምትሰራውና የምትናገረው ነገር በሌሎች ዘንድ ትርጉሙ እየተለየ ሲያስቸግር፣ ሰዎች በነገሮች ላይ የማሰቢያ ጊዜ እንዲያገኙ ፋታ መስጠትም ይጠቅማል ብዬ ነው፡፡ እንጂ ሌላ ምክንያት ኖሮኝ አይደለም፡፡
ሎሚ፡- ከፓርላማ የአምስት ዓመት ቆይታህ በኋላ የነበረው ጊዜህን በምን ነበር ያሳለፍከው;
ልደቱ፡- ፓርላማ አምስት አመት ነው የቆየሁት፡፡ የፓርላማው አሠራር በሚፈቅደው መሠረት እንደ ፓርቲያችንን ወክለን ተሣትፎ ስናደርግ ነበር፡፡ በተለያዩ ቋሚ ኮሚቴዎች ውስጥም የተወከሉ ነበሩ፡፡ ከኛ ፓርቲ አቅማችንና ሁኔታው በፈቀደው መጠን ለነዛ ኮሚቴዎች ገንቢ የሆነ ተሣትፎ ለማድረግ ጥረት አድርገናል፡፡ እኔም እንደ ሕዝብ ተወካይነቴ ክርክሮችና ውይይቶች ሲኖሩ የራሴን ዝግጅት አድርጌ ከፓርቲያችን አቋም አንፃር ሃሣቡ ተቀባይነት ያግኝም አያግኝም የሚታየኝን፣ የሚመስለኝን አቋም በማራመድ በጐ ተሣትፎ አድርጌያለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ ከሞላ ጐደል ጠቃሚ ተሣትፎ ነበረን ብዬ አምናለሁ፡፡ እኛ ፓርላማ ብንገባም ባንገባም፣ የተቃዋሚው ጎራ በአብዛኛው ወይም ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ከፓርላማ መውጣቱ ያሳዝነኛል፡፡ ይህ ሂደት ተጠናክሮና ጐልብቶ ፓርላማችን የተለያዩ አስተሳሰቦች የሚንፀባረቁበት መድረክ ሆኖ የሚቀጥል መስሎኝ ነበር፡፡ አለመታደል ሆኖ ወደኋላ ነው የሄድነው፡፡
ሎሚ፡- በርካታዎች በምርጫ 97 ሠሞን ኢትዮጵያ ውስጥ ለውጥ ይመጣል ብለው ይገምቱ ነበር፤ አንተስ;
ልደቱ፡- Well እንግዲህ፡፡ በ1997 ዓ.ም. ለውጥ ለማምጣት አንድ ዕድል ነበር ብሎ መውሰድ ይቻላል፡፡ ግን መጀመሪያ ለውጥ ማለት ምንድነው? በሚለው መስማማት አለብን፡፡ ምናልባት ለውጥ ለማምጣት 97 ላይ ዕድል ነበር ሲባል አንዳንድ ሰዎች እንደሚያስቡት መንግስታዊ ለውጥ ማምጣት ከሆነ የተለየ ነው፡፡ እኔ በዚህ በኩል ብዙ ዕድል ነበር ብዬ አላምንም፡፡ ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታው ገንቢ የሆነ ለውጥ ማምጣት ይቻላል ከሆነ እስማማለሁ፡፡ ሰዎች ለውጥን የሚያዩበት መንገድ ይለያያል፡፡ ለእኔ 1997 ዓ.ም. የመንግስት ለውጥ የሚመጣበት ጊዜ አልነበረም፡፡ ያን ደግሞ የምናውቀው ምርጫ ውስጥ ከገባን በኋላ ሳይሆን ወደ ምርጫ ለመግባት ዝግጅት ስናደርግ ነው፡፡ ይህንንም በኢዴፓ ደረጃ ተወያይተንበት፣ ነባራዊ ሁኔታውን ገምግመን የያዝነው ጉዳይ ነበር፡፡ “…በዚህ ምርጫ አሸንፈን አዲስ አበባ ከተማን እንቆጣጠራለን፤ በቂ የሚባል የፓርላማ መቀመጫ እንይዛለን፤ ይሄን ውጤት ይዘን ከአምስት አመት በኋላ በሚደረግ ምርጫ ደግሞ መንግስት ለመሆን የሚያስችለንን ዕድሉን እናገኛለን” ብለን ነው ተሳትፎ ያደረግነው፡፡በምርጫ ስትሣተፍ “አሸንፋለሁ” እያልክ ነው መቀስቀስ ያለብህ፡፡ ይህ የግድ ነው፡፡ ከዛ ውጪ ግን በውስጣችን ከነበረው ነባራዊ ሁኔታ አንጻር በ97 መንግስት ለመለወጥ የሚያስችል ሁኔታ አልነበረም፡፡ አንድ ቀላል ምሣሌ ላንሳ፤ ቅንጅት በዚያ ምርጫ ከባድ ተፎካካሪ ሆኖ ነው የቀረበው፡፡ ግን በ130 ወረዳዎች ተፎካካሪ አላቀረብንም፡፡ ይሄ በራሱ ሙሉ ለሙሉ እንዳናሸንፍ ያደረገ አንድ ችግር ነበር፡፡
በወቅቱ እኛ ብቻ አልነበርንም በተቃዋሚነት ምርጫ ፉክክር ውስጥ የገባነው፡፡ “ህብረት” ውድድር ውስጥ ነበር፤ እኛና ህብረቱ የምንካፈለው የሕዝብ ድምፅ ነበር፡፡ ሁለታችን ለየብቻ ስለተወዳደርን የተቃዋሚውን ድጋፍ ለሁለት እንካፈለዋለን፡፡ ይህ ደግሞ ኢህአዴግ በብዙ ቦታዎች ላይ በአነስተኛ ድምፅ የሚያሸንፍባቸውን ሁኔታዎች ፈጥሮ ነበር፡፡ ሌላው እንደተቃዋሚ ብዙ ያልሰራንባቸው ብዙ ነገሮች ነበሩ፡፡ ቅንጅቱን እንደ ነፍጠኛ እና እንደ አማራ ኃይል የሚያይና በኢህአዴግ ተጠቃሚ ነኝ የሚል ክፍል ነበር፡፡ እነዚያ የሕብረተሰብ ክፍሎች እኛን እንደማይመርጡ ግልፅ ነበር፡፡
ምርጫው ግልፅና ፍትሃዊ እንደማይሆንም ቀድመን እናውቅ ነበር፡፡ ለምሣሌ ወደ 905 ሺህ ሰው በታዛቢነት ማቅረብ ነበረብን፡፡ እኛ ያቀረብነው 15 ሺህ ታዛቢ ነው፡፡ ይህ የሚያሣየው ወደ 85 ሺህ ታዛቢ ልናቀርብበት የምንችልበት ቦታ ክፍት መሆኑን ነው፡፡ በኒዚያ ቦታዎች የማጭበርበሩን ሁኔታ ማስቀረት ይቅርና ታዛቢ ባቀረብንባቸው ቦታዎች እንኳን ምርጫው ስለመጭበርበሩና አለመጭበርበሩ መረጃ ልናቀርብ የምንችልበት ዕድል አልነበረም፡፡ ታዛቢ አጥተን ያላቀረብንበት ሁኔታ ነው የነበረው፡፡ ከነዚህ አጠቃላይ ሁኔታዎች አንፃር በ97 ምርጫ ለውጥ ለማምጣት ዕድል አልነበረም፡፡
ሎሚ፡- አሁን ከዘረዘርካቸው ምክንያቶች በተጨማሪ በምርጫ 97 የተቃዋሚዎችን ዕድል ያጨናገፈው አቶ ልደቱ አያሌው መሆኑ ይነገራል፤ አሁን ላይ ሆነህ ምን ምላሽ ትሰጣለህ?
ልደቱ፡- ይባላል! በነገራችን ላይ ለዚህ ጥያቄ ብዙ ጊዜ መልስ ሰጥቻለሁ፡፡ መሠረት የሌለው ጥያቄ ነው፡፡ አሉባልታ ነው፡፡ ተጨባጭ ነገር አይደለም፡፡ ግን ዞሮ ዞሮ ደጋግሞ ይመጣብሀል፡፡ እኔ ስለ አሉባልታ ማውራት ትቻለሁ ብቻ ሳይሆን ተጠይፌያለሁ፤ አንገፍግፎኛል፡፡ ግን አንዳንድ ጊዜ አንዳንድ ሰዎች ወይም አንዳንድ ድርጅቶች በሃሣብ ደረጃ ስትሞግታቸው መልስ የሚሰጡህ በሀሣብ አይደለም፡፡ በአሉባልታ ነው፡፡ ስለዚህ ያን ለማስተባበል አንተም አሉባልታ ማፍራት ትጀምራለህ፡፡ ሁሉም ይቆሽሽና ፖለቲካው አስቀያሚ ይሆናል፡፡
ጥያቄውን ለመመለስ ያነሳኸው ጉዳይ ሲባል እሰማለሁ፤ ቅንጅትን ልደቱ አፈረሰው ይባላል፡፡ እንደዚህ የሚሉ ሰዎች አንዳች ተጨባጭ መረጃ የላቸውም፡፡ እኔ አንድ ግለሰብ ነኝ፡፡ ቅንጅት የአራት ፓርቲዎች ውህደት ወይም ጥምረት ነው፡፡ አንድ ግለሰብ ቅንጅትን ባሻው ጊዜ፣ በራሱ ፍላጐትና እምነት ተነስቶ የሚያፈርስ ከሆነ ምን ዓይነት ቅንጅት ነበር?… የአራት ድርጅቶች ሕብረት አልነበረም ማለት ነው፡፡ እኔ ስፈልግ የማፈርሰው ከሆነ ደግሞ ራሴ ብቻዬን ቅንጅት ነበርኩ ማለት ነው፡፡
ሰዎች ለቅንጅት ያላቸው አመለካከት የተለየ ነበር፡፡ በጣም ጠንካራና ግዙፍ አካል አድርገው ነበር የሳሉት፡፡ በሌላ በኩል ያን አግዝፈው የሳሉትን ቅንጅት “ልደቱ” የሚባል አንድ ግለሰብ አፈረሰው ይላሉ፡፡ ይህ ስህተት ነው፡፡ አይደለም ልደቱ፣ ኢዴፓ የሚባል ፓርቲ ቅንጅትን ሊያፈርሰው አይችልም፡፡ ምክንያቱም የአራት ፓርቲዎች ጥምረት ነውና፡፡ ከአራቱ ፓርቲዎች አንዱ ፓርቲ ፍላጐት ሣይኖረው ቢወጣ ሦስቱ ፓርቲዎች ቅንጅት ሆነው መቀጠል ስለሚችሉ ሊያፈርሰው የሚችል ምክንያት የለም፡፡ አንድም ቀን “ቅንጅት የኛ ቅንጅት ሆኖ አይቀጥልም” ብለን ክስ አቅርበን አናውቅም፡፡ መስማማት ከቻልን በጋራ መቀጠል እንችላለን፤ ካልቻልን ግን እኛን ተዉንና እናንተ ቀጥሉ ነው ያልነው፡፡
ሦስቱ ድርጅቶች ቅንጅት ሆነው መቀጠል ይችሉ ነበር፡፡ ስለዚህ አሉባልታው ምንም መሠረት የለውም፡፡ አንዳንድ ሰው ልደቱ ያፈረሰው ሊመስለው ይችላል፡፡ በሆነ አጋጣሚ የተወሩትን አሉባልታዎች መሠረት አድርጐ ወይም ከቅንጅት አገኘዋለሁ ብሎ የነበረውን አጉል ተስፋ ሲያጣ ጥፋቱን የሆነ አካል ላይ ወርውሮ በእከሌ ጥፋት ነው ቅንጅት የፈረሰው ሊል ይችላል፡፡ አልፈርድም! ሰው ብዙ ተስፋ አድርጐ ነበር፡፡ ያንን ተስፋ ሲያጣ፣ ተስፋ የጣለበትን ምክንያት የሆነ አካል ላይ መወርወር ነበረበት፡፡ ስለዚህ እኔ ላይ ወረወረው፡፡ ችግሩን ልረዳ እችላለሁ፡፡
ቅንጅትን በማፍረስ ረገድ ሚና ካለኝ እኔ ከቅንጅት ተለየሁ አይደል?… የቅንጅት አመራሮች እስር ቤት ገቡ፤ ከሁለት አመት የእስር ቤት ቆይታ በኋላ ወጥተው አንድ ላይ መስራት ጀመሩ፡፡ ችግሩ እኔ ከሆንኩ እኔ በሌለሁበት ቅንጅት ጠንካራ ሆኖ መቀጠል ነበረበት፡፡ ግን ቀጠለ?… የቅንጅት አመራሮች ከእስር ቤት ከወጡ በኋላ አብረው መስራት ቢጀምሩም ወደ ስምንትና ዘጠኝ ቦታ ከመከፋፈል አልዳኑም፡፡ ስለዚህ ቅንጅትን ያፈረሰው ልደቱ አልነበረም፤ የማፍረስ አቅምም አልነበረውም፡፡ ቅንጅት የፈረሰው በራሱ ውስጣዊ ድክመት ነው፡፡ እኛ ፓርላማ እንግባ ነው ያልነው፡፡ አዲስ አበባን ያኔ ተቀብለን ይዘን ቢሆን ኖሮ አሁን ያለው የትግል ሁኔታ በጣም የተለየ ይሆን ነበር፡፡
ሎሚ፡- በወቅቱ የያዛችሁት አቋም “እውነተኛውን ዴሞክራሲ መፍጠር” የሚል ነበር፤ በዚህ መንገድ እየተጓዛችሁ ሳለ አንተ ግን ቅንጅት ሲዋሃድ የሥልጣን ጥያቄ ማቅረብሕና በኋላም ማኩፈፍህ ነበር የተነገረው፤ ይህ ለምን ሆነ;
ልደቱ፡- ልደቱ “ስልጣን ይገባኛል ብሎ ነበር” ብሎ በመረጃ አስደግፎ የሚመጣ ሰው ካለ ሌላ ጉዳይ ነው፡፡ እኔ ኃላፊነት መውሰድ እችላለሁ፡፡ በነገራችን ላይ የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ ገብተህ የስልጣን ጥያቄ ማቅረብ ስህተትም ወንጀልም አይደለም፡፡ ፖለቲካ የስልጣን ጥያቄ ነው፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ እኔ በኢዴፓ/መድህን ውስጥ በመጀመሪያዎቹ ሰባት አመታት ሳልፈልግ ተመርጬ ነው አመራር የሆንኩት፡፡ ሳልፈለግ ስልህ አልፈልግም ብቻ ሣይሆን በአንደኛው ጉባኤ እንባ አውጥቼ አልቅሼ ኃላፊነት በቃኝ እያልኩ ነው የተመረጥኩት፡፡
በኋላ በነበሩት ሂደቶች ኢዴፓ አጣብቂኝ ውስጥ ገብቶ፣ ችግር ላይ ስለነበር የአመራርነቱን ሚና ትቼ መሄድ አልፈለግኩም፡፡ ፈልጌም ነው የተመረጥኩት፡፡ በተለይ ደግሞ የቅንጅት አመራር ሆኜ ስመረጥ የመመረጥ ፍላጐት አልነበረኝም፡፡ እንባ አውጥቼ መድረክ ላይ ወጥቼ ለምኛለሁ፡፡ እምቢ ተብዬ ነው የሆንኩት፡፡ ቅንጅት ውስጥ እያለሁ ከኃላፊነቴ ለመልቀቅ ሦስት ጊዜ መልቀቂያ አቅርቤያለሁ፡፡ የኃላፊነት ፉክክር ውስጥ አንድም ቀን ገብቼ አላውቅም፡፡
ሎሚ፡- ኢንጂነር ኃይሉ ከሥልጣን ወርደው አንተ ለመሾም ጥያቄ አላቀረብክም?
ሰሞኑን ኢ/ር ኃይሉ ሻውል ያወጡት መፅሐፍ ላይ “ልደቱ እጁን አውጥቶ ኢ/ር ኃይሉ ሻውልን ከስልጣን አውርዳችሁ እኔን ሊቀመንበር አድርጉኝ” ብሏል ብለው መፃፋቸውን ሰምቻለሁ፡፡ በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ በቅንጅት ውስጥ ብዙ ሰዎች ነው የነበሩት፡፡ ኢ/ር ኃይሉ ያሉት “እውነት ነው ውሸት ነው” ማመዛዘን የሚችልና ህሊና ያለው ሰው ሊፈርድ ይችላል፡፡ አንድ ኢትዮጵያዊ ፖለቲከኛ መድረክ ላይ እጁን አውጥቶ እከሌን አውርዱትና እኔን ሹሙኝ ብሎ አይጠይቅም፡፡ በፍፁም እንደዚህ ዓይነት ነገር አድርጌ አላውቅም፡፡ ተመኝቼውም አላውቅም፡፡ ቅንጅት ውስጥ በነበረው ሂደት ያለመመረጥ፣ ስልጣን ያለመያዝ ፍላጐት ነው የነበረኝ፡፡
ምናልባት ፕ/ር መስፍን በጋዜጣ ፅፈውት አንብበህ ሊሆን ይችላል፤ “ልደቱ ሁልጊዜ መመረጥ የሚፈልገው ቤቱ ቁጭ ብሎ ነው፤ ሎቢ ማድረግ አይፈልግም” ብለው ነው የተናገሩት፡፡ እኔ በትግሉ ውስጥ ተሣትፎ ማድረግና የሚገባኝን ስራ መስራት ነው የምፈልገው እንጂ ስልጣን መያዝ አይደለም፡፡ ነገሮች ከአንዱ ወደ ሌላው እየዘለሉ ከአቅሜ በላይ በሆነ ምክንያት “ታስፈልገናለህ” እየተባልኩ ነው ስመረጥ የነበረው፡፡ ብጠይቅ ችግር ነው፣ ስህተት ነው እያልኩ አይደለም፡፡ አጋጣሚ ሆኖ ጠይቄ አላውቅም፡፡ አንተ ጋዜጠኛ ነህ፤ የቅንጅት አመራር የነበሩ አራት አምስት ሰዎችን ጠይቀህ፣ ሁለትና ሦስት ሰዎች “ልደቱ የሥልጣን ጥያቄ ነበረው” ካሉህ እኔ ተሳስቻለሁ ማለት ነው፡፡ ይቅርታም እጠይቃለሁ! ሊሉህ እንደማይችሉ ግን እርግጠኛ ነኝ፡፡ እንግዲህ እኚህ ሰውዬ ትልቅ ሰው ናቸው፤ አቋማቸው ይጣመኝም አይጣመኝም ትግሉ ውስጥ ለከፈሉት ዋጋ አክብሮት አለኝ፡፡ ግን እንደዚህ ዓይነት ውሸት አልጠብቅም ነበር፡፡ ቅንጅትን ስንመሰርት ሊቀመንበር ሆኖ የመቀጠል ዕድል ነበረኝ፡፡ ግን “አይሆንም፤ የበሰሉ ሰዎች ቢመሩት ይሻላል” ብለን ነው ዶ/ር ኃይሉ እና ዶ/ር አድማሱን ከቤታቸው አምጥተን ስልጣኑን እንዲይዙትና እኛ የበታች ሆነን እንድንሰራ ያደረግነው፡፡ ይህንንም በተግባር አሳይተናል፡፡
ሎሚ፡- ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ የቅንጅት ም/ሊመንበር ሆና ስትመረጥ፣ አንተ ለቦታው ራስህን አጭተህ ስለነበር በእጅጉ መበሳጨትህ ተሰምቷል፤ ይሕ ደግሞ በአንድ ሰው የተገለፀ ሳይሆን በርካታ የቅንጅት አመራሮች በተለያየ አጋጣሚ ደጋግመው የገለፁት ነው፤ ሥልጣን ካልፈለግክ ምን ነበር ያበሳጨህ;
ልደቱ፡- ቅድም እንዳልኩት ሰዎች እንዲሕ ሊሉ ይችላሉ፡፡ የሆነውን ነገር ግን ልነግርህ እችላለሁ፡፡ ወ/ት ብርቱካን በቅንጅት ውስጥ የተሰጣት ኃላፊነት አግባብ ነው ብዬ አላምንም፡፡ እንድትመረጥ የተደረገው በድርጅታዊ አሠራር መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ወ/ት ብርቱካን ወደ ትግል እንድትመጣ ከማንም በላይ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ እንደውም መመረጧ ደስ ብሎኝ በግንባር ቀደምነት ነው “እንኳን ደስ ያለሽ” ያልኳት፡፡ መድረክ ላይ የሆነው ይሄ ነው፡፡ የተወራው ደግሞ ሌላ ነው፡፡ አዝናለሁ፡፡ እየተዳኘሁ ያለሁት በምሰራው ሥራ ወይም ባራመድኩት አቋም አይደለም፡፡ ሰዎች ስለኔ ባወሩት ወሬ ነው እየተዳኘሁ ያለሁት፡፡ ብርቱካን አልሞተችም አለች… እሷን ማነጋገር ትችላለህ፡፡
ሎሚ፡- ቅንጅት ውስጥ አለመግባባት በነበረበት ወቅት “የምሁራን ስብስብ ተፅዕኖ ሊፈጥርብን አይችልም” የሚል ንግግር ተናግረህ እንደነበር ታስታውሳለህ;
ልደቱ፡- አልገባኝም;…
ሎሚ፡- ወ/ት ብርቱካን እና ኢ/ር ኃይሉ ሻውል በቅንጅት አመራርነት ከተመረጡ በኋላ “የምሁራን ተፅእኖ ሊኖር አይገባም” ብለህ ነበር?…
ልደቱ፡- እንደዚያ ብዬ የተናገርኩበት ጊዜ አልነበረም፤ አላስታውስም፡፡ ግን በአጠቃላይ በሕይወትህ ምን ስህተት ሰርተሀል? ምን ዓይነት አመለካከት ነበረህ? ብትለኝ አንዱ ስህተት ለምሁራን የነበረኝ አመለካከት ነው፡፡ እንደ አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ፕሮፌሰርን፣ ዶክተርን… የፖለቲካ ሊቅ አድርጌ ነበር የማየው፡፡ ለዚያም ነው ኢዴፓን ስንመሰርት እኛ መስርተን እኛው መምራት የለብንም ብለን ምሁሮችን ከቤታቸው አምጥተን ኃላፊነት ላይ ያስቀመጥነው፡፡ ምናልባት ባላጋንነው ምሁር የሆነ ሰው የሚዋሽ አይመስለኝም ነበር፡፡ የስልጣን ጥማት ያለው አይመስለኝም ነበር፡፡ ሀገር ወዳድ ይመስለኝ ነበር፡፡ ሃቀኛ ነበር የሚመስለኝ፡፡ ግን በጣም የተሳሳተ አመለካከት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ግን እንደዚህ አላስብም፡፡ ስለተማረና ስላልተማረ አይደለም፤ አንድ ሰው ምሁር ሆኖም የፖለቲካ ሴረኛ ሊሆን ይችላል፡፡ ያልተማረም የፖለቲካ ሴረኛ አለ፡፡ በዚህ ረገድ ድሮ የነበረኝና አሁን ያለኝ አመለካከት ተቀይሯል፡፡ ግን አንተ እንዳልከው ቅንጅት ውስጥ ምሁራንን የተናገርኩበትን ጊዜ አላስታውሰውም፡፡
ሎሚ፡- ከጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ጋር ተገናኝታችሁ ያወራችሁበት ጊዜ ነበር;
ልደቱ፡- ይመስለኛል፤ ሁለት ሦስት ጊዜ፡፡
ሎሚ፡- “እየሄድክበት ያለው መንገድ ጥሩ አይደለም፤ ለኢህአዴግ እየሰራህ ነው፤ ይህም ታውቋል፤ ስለዚህ ራስህን ከቦታው ብታገልል ጥሩ ነው” ያለህ ጊዜ ነበር;
ልደቱ፡- እስክንድር እንደዚህ ብሎኝ አያውቅም፡፡ ስለኔ ብዙ ነገር መፃፉን ግን አውቃለሁ፡፡ እስክንድር ፓርቲ አይደል መሪ አይደል፤ ከሂደቱ ውስጥ ውጣ አትውጣ ብሎ ሊያዘኝ የሚችልበት ምክንያት አይኖርም፡፡ እኔ እና እሱ በእንዲህ ዓይነት ጉዳይ ዙሪያ አውርተን አናውቅም፡፡
ሎሚ፡- ታዲያ “የአረም እርሻ” በሚለው መፅሐፍህ ውስጥ ሰፊ ቦታ ሰጥተህ ለምን ወቀስከው;
ልደቱ፡- ቅንጅት ውስጥ በነበርኩበት በተለይ ፓርላማ “ይገባ አይገባ” በሚባልበት ወቅት እሱ ያራምደው የነበረው አቋም ተገቢ አልነበረም፡፡ በእኔ እምነት ቅንጅትን ወደተሳሳተ አቅጣጫ እንዲሄድ ከገፉት መካከል አንዱ የእስክንድር ጋዜጣ ነው፡፡ በዛ ምክንያት በመጽፌ ተችቼዋለሁ፡፡ እሱ በየሳምንቱ ይተቸኝ አልነበር? ታዲያ እኔ ብተቸው ምን ችግር አለው?
ሎሚ፡- እሱ የተቸህ እኮ አንተ የቅንጅት አመራር ሆነህ “ከኢህአዴግ ጋር በጐን እየሰራህ ነው” ብሎ ነው…
ልደቱ፡- ይሕን ለኔ… ነግሮኝ አያውቅም፡፡ እስክንድር እንደ አንድ ጋዜጠኛ ወይም እንደ አንድ የጋዜጣ ባለቤት የነበረው አቋም ስህተት ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ እሱ በቅንጅት ውስጥ ያራምደው የነበረው አቋም ስህተት ነው ብሎ እንደሚያምነው፣ እኔም እሱ ያራመደው አቋም ስህተት ነው ብዬ ፅፌያለሁ፡፡ ይህ ችግር ያለው አይመስለኝም፡፡ በምትለው መልኩ ግን “ለኢህአዴግ እየሰራህ ነው” ብሎ የነገረኝ ጊዜ የለም፡፡
ሎሚ፡- ከቅንጅት ዕውቅና ውጪ ከአቦይ ስብሀት ነጋ ጋር የተገናኘኸው በምን ምክንያት ነው;
ልደቱ፡- የት ነው የተገናኘነው? አንተን ልጠይቅህ እስኪ፤
ሎሚ፡- በወቅቱ መረጃው የወጣው “መዝናኛ” በተሰኘ ጋዜጣ እንደሆነ አትዘነጋውም፤ ሁለታችሁ የተገናኛችሁትም በተጠቀሰው ዕለት ከቀኑ 11፡30 በኢንተር አፍሪካ ግሩፕ ቢሮ ውስጥ መሆኑም ተገልጿል…
ልደቱ፡- ዞሮ ዞሮ ይሄ ወሬ በተወራበት ወቅት ከአቶ ስብሀት ጋር አልተገናኘሁም፡፡ ይሄ ጉዳይ ሲወራም አቶ ስብሀት የተባሉትን ሰው በዓይኔም አይቻቸው አላውቅም ነበር፡፡ እንደ ማንም ሰው መፅሔት ላይ ፎቶግራፋቸውን ከማየት ውጪ አቶ ስብሓት ነጋ ቀይ ይሁኑ ጠይም፣ ረዥም ይሁኑ አጭር አላውቅም ነበር፡፡
ሎሚ፡- ከአቦይ ስብሃት ጋ አልተገናኛችሁማ?
ልደቱ፡- ይሔ ወሬ ሲወራ አንተዋወቅም፡፡ አቶ ስብሀትን በአካል ያየኋቸው ወይም ያገኘኋቸው ይሄ ወሬው ከተወራ ከሁለት አመት በኋላ ይመስለኛል፡፡ የቅንጅት ችግር ከተፈጠረ ከሁለት ዓመት በኋላ ፈረንሣይ ኤምባሲ አንድ የኮክቴል ግብዣ ላይ ነው ያገኘኋቸው፡፡ ግን ያኔ በሆነ አጋጣሚ ተገናኝተን ቢሆን እንኳን ምንም የሚያሳፍረኝ ነገር የለም፡፡ ደስ የሚለኝ ነገር ነው፡፡ የሚያሳዝነኝ ግን የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች (በገዢውም በተቃዋሚም ያለነው) በሀገር ጉዳይ ላይ እየተገናኘን አለመነጋገራችን ነው፡፡
ሎሚ፡- አንዳንድ ምንጮች ልደቱን ብአዴን/ኢህአዴግ አስቀድሞ ያዘጋጀው ሰው ነው ይላሉ፤ ተቃዋሚ መስለሕ ለማደናገር ወደ ፓርቲዎቹ እንደገባሕም ይነገራል፤ ያንተ ምላሽ ምንድነው;
ልደቱ፡- አሁን ለዚህ መልስ ብሰጥህ ምን ጥቅም አለው?… ኢህአዴግ በዚያ ደረጃ አዘጋጅቶ ወደ ተቃዋሚ ጐራ ሰርጌ እንድገባ ያደረገኝ ሰው ከሆነ የምሰጠው መልስ ይታወቃል፡፡ አይደለሁም ነው የምልህ፡፡ ግን ኢህአዴግን ለመጥቀም ከተፈለገ ለምንድነው ተቃዋሚ ውስጥ የምገባው? ኢህአዴግ ተቃዋሚ በዝቶበት አይደል እንዴ የተቸገረው፡፡ እንደዚህ ብለው የሚናገሩ ሰዎች መረጃቸውን ማቅረብ ይችላሉ፡፡ ኢህአዴግ ወደ ስድስት ሚሊዮን የሚጠጉ አባላት አሉት፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ ብሆን ችግር የለውም፤ መሆን ብፈልግ ማለት ነው፡፡ የሚያሣፍርም ነገር የለውም፡፡ የኢህአዴግን የፖለቲካ አመለካከት አልወደውም፣ አላምንበትም እንጂ ባምንበት እኮ ኢህአዴግ እሆናለሁ፡፡ የሚያሳፍር ነገር አይደለም፡፡ የኢህአዴግ አባል የሆኑ ብዙ ጓደኞች አሉኝ፤ ወንድሞች እህቶች አሉኝ፡፡ ግን አጋጣሚ ሆኖ የኔና የኢህአዴግ የፖለቲካ አመለካከት ስለማይጣጣም አልሆንኩም፡፡
ሎሚ፡- ቅንጅት በአንተ ላይ ጠንከር ያለ እርምጃ ወስዶ ነበር፤ ወደ ስብሰባ አዳራሽ ስትገቡ ፍተሻው ሁሉንም የሚያካትት ቢሆንም መንስዔው ግን የአንተ ተጠርጣሪነት ነበር…
ልደቱ፡- ስለጉዳዩ ላስረዳህ፤ ፍተሻ ነበር፡፡ ያ የሆነው የቅንጅት አመራር የሚነጋገርባቸው አጀንዳዎችና ቃለ ጉባኤዎች በማግስቱ “ኢፍቲን” በሚባል ጋዜጣ ይወጣ ስለነበረ ነው፡፡ በኋላ ላይ በስልክ ወይም በዘመናዊ መሣሪያ የሚቀርፅ ሰው አለ ተባለ፡፡ ሁላችንም ሞባይላችንን ውጪ እየተውንና እየተፈተሽን እንግባ ብለን ተነጋግረን ወሰንን፡፡ ሞባይላችንን ውጪ እያስቀመጥን እየተፈተሽን መግባት ጀመርን፡፡ እንግዲህ በዚያ ጊዜ የሚጠረጠሩ ሰዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ እኔ ግን በተፈጠረው አለመግባባት መልቀቂያ ጠየቅኩኝ፡፡ ዶ/ር ብርሃኑ ያንን ፊርማ ከፈረመ በኋላ ከሕዝብ ግንኙነት ኃላፊነቴ ለቀቅኩ፡፡ እኔን ተክቶ ዶ/ር ኃይሉ አርአያ ገባ፡፡ ከአመራር ውስጥ ወጣሁ፡፡
ከወጣሁ በኋላም “ኢፍቲን” ጋዜጣ ያንን ነገር መዘገቡን ቀጠለ፡፡ ፍተሻውም ይካሄዳል፡፡ እኔ ብሆን ኖሮ እኔ ስወጣ መቆም ነበረበት፡፡ ግን ቀጠለ፡፡ ቃለ ጉባኤ የያዝንበት ምስጢር እየወጣ ስንቸገር እስቲ አንዳንድ ቁልፍ የሆኑ ጉዳዮችን ሌሎቻችን በሌለንበት አራቱ የድርጅት መሪዎች ለብቻቸው ይነጋገሩ አልን፡፡ በአንድ ጉዳይ ላይ አራቱ የድርጅቱ መሪዎች (ዶ/ር ብርሃኑ፣ ዶ/ር አድማሱ፣ ኢ/ር ኃይሉ ሻውል እና ዶ/ር አለማየሁ) ሰሜን ሆቴል ስድስተኛ ፎቅ አጀንዳ ይዘው ውይይት አደረጉ፡፡ አራቱ ብቻ ናቸው የተገኙት፡፡ የተነጋገሩበት አጀንዳ በነጋታው “ኢፍቲን” ላይ ወጣ፡፡
ታስታውስ እንደሆነ “ህብረት” ሲመሠረት ስብሰባው ላይ ለመካፈል ዋሽንግተን ዲሲ ሄጄ ነበር፡፡ ውይይት ስናደርግ አንዳንድ የሀሣብ ግጭቶች ተፈጠሩ፡፡ በእኛና በኢህአፓዎች መካከል ልዩነቶች ሲፈጠሩ፣ ሀሣብን በሀሣብ ማሸነፍ ሲገባቸው አሉባልታ አስወሩብኝ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ፣ አንድ የግል ጋዜጣ “አቶ ልደቱ የሕብረቱን ስብሰባ በቴፕ ሲቀዱ ተያዙ” ብሎ ዜና አወጣ፡፡ ስብሰባው አላለቀም፤ እዚያ ተቀምጠናል፡፡ በኋላ ተደውሎ ከኢትዮጵያ ተነገረኝ፡፡ በማግስቱ ስብሰባው ይቀጥል ስለነበር ወደ ስብሰባው ገብቼ “ኢትዮጵያ ውስጥ እንደዚህ ተብሎ ተፅፏል፤ ይሄ ነገር ሀሰት መሆኑን አይታችኋል፤ ማስተካከል የለባችሁም ወይ?” ብዬ ጠየቅኳቸው፡፡ ኢህአፓዎች ይህንን ነገር ለመቀበልና ለማስተባበል አልፈለጉም፡፡ ለእንደዚህ ዓይነት ነገር ምላሽ አንሰጥም ተብሎ ታለፈ፡፡ ሀሳብን በሀሣብ ማሸነፍ ሲያቅታቸው እንዲህ ያስወሩብሃል፡፡
ሎሚ፡- ኢህአዴግ በወቅቱ አንተ በነበረህ ድጋፍ ተጠቅሞ በቅንጅት ውስጥ ልዩነት ፈጥረህ እንድትወጣ ግፊት አድርጓል ተብሏል፤ አንተ ስትወጣ ቅንጅት ለሁለት ይከፈላል ቢባልም ለግለሰብ ሳይሆን ለፓርቲ ቅድሚያ ተሰጥቷልም ተብሏል፤ ይህን ጉዳይስ እንዴት አየኸው;
ልደቱ፡- ሂደቱን የግል ጉዳይ አድርገህ አትየው፡፡ ልዩነቱ የተፈጠረው በእኔና በቅንጅት መካከል አይደለም፡፡ በኢዴፓና በቅንጅት ነው፡፡ እኔ ያራመድኳቸው ሀሳቦች የግል አቋሜ ሳይሆን በሙሉ ኢዴፓ ያመነባቸው ናቸው፡፡ ሌላ ውጫዊ አካል ተፅዕኖ አድርጐብን የያዝነው አይደለም፡፡ ያንጸባረቅነው መቶ በመቶ የምናምንበትን አቋም ነበር፡፡ ኢህአዴግ ስለገፋኝ ወይም ተፅዕኖ አድርጐብኝ አይደለም፡፡ አቋምህን ቀይር ተብዬ ተጠይቄም አላውቅም፡፡ ይሔ ልደቱን የኢህአዴግ ሰው ለማስመሰል የተደረገ ጉዳይ ነው፡፡
ከኢህአዴግ ጋር በፖለቲካ አቋም የምጣጣም ብሆን ኖሮ፣ ለእንደዚህ ዓይነቶቹ አሉባልተኞች በደንብ አድርጌ አሳያቸው ነበር፡፡ ኢህአዴግ መሆን ምንም ማለት እንዳልሆነ አሳያቸው ነበር፡፡ አጋጣሚ ሆኖ ግን ኢህአዴግ መሆን አልችልም፡፡ የሚመኙትን ምኞት በደንብ በተግባር አሳያቸው ነበር፡፡ ኢህአዴግ የሆኑ ጓደኞች አሉኝ፡፡ እነሱ ያላቸውን አስተሳሰብ አከብራለሁ፡፡ ምርጫቸው ነው፡፡ ከእነሱ ውስጥ አንዱ ብሆን ምንድነው ችግሩ; ከስድስት ሚሊዮን የኢህአዴግ አባል አንዱ ብሆን ምን ችግር አለው; ያ የፖለቲካ አመለካከት ነው፡፡ ተቃዋሚም ሆኜ የተቃዋሚው ሚና ካልጣመኝ ሀሣቤን ከቀየርኩ ኢህአዴግ መሆን እኮ መብቴ ነው፡፡ ትናንት ተቃዋሚ ነበርክና ዛሬ የኢህአዴግ አባል መሆን የለብህም የሚባል ነገር የለም፡፡ ትናንት ኢህአዴግ የነበሩ ሰዎች ዛሬ ተቃዋሚዎች ሆነው የለ እንዴ? እነ አቶ ስዬና ዶ/ር ነጋሶ እኮ ትናንት የኢህአዴግ አባላት ነበሩ፡፡ በኋላ ተቃዋሚ ሆነዋል፡፡ ካመንኩበት እኔም ዛሬ ተቃዋሚ ሆኜ ነገ ኢህአዴግ ብሆን ምን ችግር አለው?…
…ይቀጥላል…

No comments:

Post a Comment