Thursday, November 7, 2013

አብዮት እና ወጣትነት – በወጣት ሃብታሙ አያሌው (የአንድነት ፓርቲ ም/የህዝብ ግንኙነት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ)



አዲሱን አመት ተቀብለን ሁለት ወራት ሳንሻገር ጥቅምት 11 ቀን የኢትዮ ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ እና ሥራ አሥኪያጁ ጋዜጠኛ ሚሊዮን ደግነው ክስ ተመስርቶባቸው ፍርድ ቤት ቀረቡ፤ በዳግም ቀጠሮ ዕረቡ ጥቅምት 20 ቀን በሐዋሳ ከተማ ጋዜጠኞቹ ለፍርድ ቤት ቀጠሮ ሄደው በስልት የተቀናበረ በሚመስል ሆኔታ ለመኪና አደጋ ተዳርገው ጋዜጠኛ ኤፍሬም የከፋ አደጋ ሲደርስበት ዋና አዘጋጁ ጌታቸው እና ሥራ አስኪያጁ ጋዜጠኛ ሚሊዮን በመለስተኛ ጉዳት መትረፋቸው ተሰማ፤ ጥቅምት 13 ቀን እኔን ጨምሮ ሌሎች ሦስት ጓዶቼ አንድ አመት በተጓተተ ክስ ፍርድ ቤት ቀርበን ክሱ ለህዳር 24 ተቀጠረ፡፡

ጥቅምት 15 ቀን የኢትዮጵያ ህዝብ አብዝቶ የሚሳሳለት ጋዜጣኛ ተመስገን ደዳለኝ ፍርድ ቤት ቀርቦ አንደ ገና በድጋሚ ቀጠሮ ጠቅምት 21 ውሎው ፍርድ ቤት ሆነ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስተር ኃይለማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው መንግስታዊ ስልጣናቸውን በመጠቀም በሀሣብና በአመለካከት ጎራ ለይተው በሚታገሏቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ላይ ፍረጃ አና ዛቻ ሲሰነዝሩ ከረሙ፤ ፕሬዝዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ ቤተ መንግስቱን ለቅቀው በየወሩ ግማሽ ሚሊዮን ወደ እሚከፈልበት ቤታቸው ሲያመሩ ዶ/ር ሙላቱ ፕሬዘዳንት የሚል ስያሜ በመያዝ ሰተት ብለው ወደ ቤተ መንግስቱ መግባታቸው ተሰማ፡፡
መከላከያ የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር ሞት ተከትሎ በህገ መንግስት በተደነገገው መሰረት የጦር ጠቅላይ አዛዥ የሚሆነው ሌላኛው ጠቅላይ ሚኒስትር ከመሾሙ በፊት 26 የሚሆኑ ከፍተኛ ወታደራዊ ሹመቶችን ማፅደቁ ሲገርመን፤ ከሰሞኑ ሁለተኛውን ዙር የሹመት እደላ ይፋ አደረገ፡፡ የፀረ ሙስና አቃቤ ህግ በሙስና ጉዳይ በቂ መረጃ ለማግኘት ከሁለት አመት በላይ ስዘጋጅ ቆይቼ ነበር በማለት ባሰራቸው በእነ መላኩ ፈንታ ጉዳይ እንደገና መረጃ እየሠበሰብኩ ነው በማለት ለ 4 ወር ጊዜ ቀጠሮ ሲጠይቅ መክረሙ አጃይብ ሲያሰኘን “አቃቤ ህግ አቶ መላኩ ፈንታ የሦስት ልጅ እናትን ከባሏ አፋትቶ አግብቷል ሲል ከሰሰ” የሚል ዜና የሚዲያ ቀለብ ሆኖ ሲቀርብ ታዘብን፡፡
……..ሰሞነኛው አስገራሚ ሆኖ ቀጠለ፤ ለጥቂት ጊዜ እንደ ማንኛውም እስረኛ በጠያቂ የመጎብኘት ህገ መንግስታዊ መብታቸው የተከበረላቸው እነ አንዱዓለም አራጌ፤ ርዕዮት አለሙ እና እስክንድር ነጋን የመሳሰሉ እስረኞች በቀጭን ትዕዛዝ ይህ መብታቸው እንደ ገና ማዕቀብ እንደ ተጣለበት ሰማን፤ በአንፃሩ የኢትዮጵያ መንግስት አዲስ አበባ በተስተናገደው የአፍሪካ ህብረት ስብሰባ ሁነኛ ተዋናይ ሆኖ የአፍሪካ መሪዎች ዜጎቻችንን ብንጨቁንም ‘’አይሲሲ’’ ICC ሊከሰን አይገባም የሚል አቤቱታ ሲያሰሙ ከረሙ፤ የኑሮ ውድነቱ እንደ ባስ ሲቀጥል፤ በዚች ደሀ ሀገር ስም በብድር ያለጥናት የተሰሩት መንገዶች መመረቃቸው ሳይሰማ እንደ ገና መቆፈራቸው የዕለት ተዕለት ስራ ሆኗል፤ የትራንስፖርት ጥበቃው ሰልፍ በአራትና በአምስት ዙር ጨምሮ እየባሰ ሲደራረብ፤ የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አና አባላትን ባሰኛቸው ግዜ አፍነው አየወሰዱ የሚያሰሩና የሚያንገላቱ ስውር እጆች የበለጠ ተጠናክረው የቀጠሉበት ሰሞን ነበር፡፡
አንቺ አገር እንዴት ነሽ …..? እንዴት ነሽ? እንዴት ነሽ?…….መንግስትሽ አደገች፤ ተመነደገች፤ በለፀገች፤ ሰላም ሰፈነባት፤ እኩልነት ፍትህ ተረጋገጠባት ይልሻል፡፡
ንገሪን ይህ እውነት ነው? አንቺ አገር እንዴት ነሽ? እንዴት ነሽ……? እንዴት ነሽ?
ህዝቡ የእለት ተእለት ኑሮ ሰቀቀን ሆኖአል፤ ፍትህ የለም፤ በገዢው እና በህዝቡ መካከል የመደብ ልዩነት ተፈጥሯል፤ አንዱ የእንጀራ ልጅ፤ ሌላኛው ልጅ ሆኗል፡፡ ሠብአዊ ዴሞክራሲያዊ መብት ተጥሷል፤ እስር እንግልት ድብደባ፤ ስደት፣ ሞት፣ የእለት ተእለት ዜና ሆኗል ይላል፡፡
መስክሪ ይህ እውነት ነው? አንቺ ሀገር እንዴት ነሽ? እንዴት ነሽ?……..እንዴት ነሽ…..?
እቺ ሀገር መለሰች………እኔ ታዛቢ እንጂ ፈራጅ ማን አረገኝ፤
ፍትህ በሌለበት ምስክር መሆንስ ለኔ ምን ሊጠቅመኘኝ?
ከጥንት ከጠዋቱ ለዚህስ ልምድ አለኝ፤
ግፍ ፅዋው ሲሞላ መሸከም ሲያቅተው
ጀግና እምቢ ማለቱ የማይቀር ነገር ነው
መልሴ እሱ ብቻ ነው፡፡
አንቺ አገር ልክ ነሽ……..ልክ ነሽ……….ልክ ነሽ……ልክ ነሽ
አቢዮትና ወጣትነት
ወጣትነት በማህበራዊ ስነ ልቦና ደረጃ ውስጥ አንድ ወሰን የሚይዝ በተፈጥሮ ሳይንስ “ባይሎጂ” የዕድገት ደረጃ እድሜን ማዕከል የሚያደርግ ከሰው ልጅ የህይወት ዘመን ከልጅነት “ህፃንነት” እርከን በኋላ የሚከተል ነው፡፡
ይህ የሁለተኛው እርከን የወጣትነት ዘመን በአካላዊ እድገት ለአካለ መጠን የሚደረስበት፤ ንቁና ስሜታዊ የወጣትነት ባህሪ የሚቀረጽበት ፤ በማህበራዊ እረገድ ከቤተሰብ ጥገኝነት ነፃ ለመሆን እራስን የመቻል ውሳኔ ላይ የሚደረስበት እና ኃላፊነት መሸከም የሚጀመርበት የዕድሜ ክልል ነው፡፡ ስለ ወጣትነት የሚመራመሩ በርካታ ምሁራን የሚስማሙበት፤ ቁጥራቸው ቀላል ያልሆኑ ሀገራት የፖሊሲያቸው አካል ያደረጉት የወጣትነት የእድሜ ክልል መጀመሪያው ከ 14 -16 ዓመት፤ የማብቂያ ጣሪያውም ከ 25- 36 እንደ ሆነ ይናገራል፡፡
በዚህ የእድሜ ክልል ውስጥ የሚደረገው የባህሪ ቀረፃ ከግለሰቡ “ከወጣቱ” ባሻገር ማህበራዊ እና ሀገራዊ ፋይዳው ከፍተኛ ነው፡፡ በባህሪ ቀረፃው ላይ ከፍተኛ ሚና የሚጫወቱት ቤተሰብ፤ ትምህርት ቤት፤ የመገናኛ ዘዴዎች፤ የእድሜ እኩያ አጋሮችና የሀይማኖት ተቋማት ሚና ተኪ የሌለው ሲሆን የእነዚህ ተቋማትና ስብስቦች ተልዕኮ ከፍ ላለ ሀገራዊና አለም አቀፋዊ ጥቅም እንዲውል ከማድረግ አንፃር አቅጣጫ በመምራት የአንበሳውን ድርሻ የሚይዘው በመንግስትነት ስልጣን ይዞ ሀገርን በፖሊሲ የሚመራው አካል ነው፡፡
ወጣትነት በእድሜ በሚመነጭ ስነ ልቦናዊ ባህሪያት የሚገልፅ የሰው ልጅ የተፈጥሮ እርከን እንደ መሆኑ መጠን ወካይ በሆነው ማህረሰብ ውስጥ እውን የሆነው ወይም የተዘረጋው የስርአት ውጤት እየሆነ የሚታደግበት ተፈጥሮአዊ ሀቅ በመሆኑ ከፍ ያለ የሞራል ልዕልና በሌለው የመንግስት አስተዳደር ውስጥ የሚገኙ ወጣቶች በአመዛኙ ሱሰኞች፤ ወንጀልን እንደ እለት ተዕለት ተግባር የተላመዱ፤ ሀይማኖታዊ እሴት የሌላቸው እና እራሳቸውን የማያከብሩ ስለሚሆኑ የሚፈጥሩት ማህበራዊ ቀውስ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን የሚከሰት በመሆኑ ሀገር እንደ ሀገር መቀጠልና አለመቀጠሏ የሚወሰነው ወይም የአንድ ሀገር ህልውና ማዕከላዊ እንብርቱ ወጣት ነው ብሎ በድፍረት ለመናገር በቂ መከራከሪያ አለ ማለት ይቻላል፡፡
አብዮት የሚለው ቃል ፈጣን የለውጥ ግስጋሴ “ተራማጅ አስተሳሰብን” ይወክላል ካልን፤ ተራማጅ አስተሳሰብ እና ፈጣን የለውጥ ፍላጎት እጅግ በጋለ እና በዳበረ ሁኔታ የሚገለፀው በወጣትነት የዕድሜ ዘመን መሆኑን ለመቀበል አንቸገርም፡፡ ይህ ደግሞ ከተራ መላምት እና የትርጉም ስልት የሚመነጭ ሳይሆን የማህበራዊ ሰሳይንሱ ተጨባጭ እውነት መሆኑን ማረጋገጥ የሚቻልበት ሰፊ ቀዳማይ፤ ዳህራይና ነባራዊ የታሪክ ሁነቶችን በአስረጅነት ማቅረብ ይቻላል፡፡
አብዮታዊ ባህሪው በከፍተኛ ደረጃ በሚዳብርበት የወጣትነት የእድሜ ክልሉ፤ ማህበራዊ ደረጃውን በውል በመለየት የፖለቲካና የሲቪል መብቶች እንዲከበሩ የሚፈልግበት፤ ከቤተሰብ ጥገኝነት በመውጣት ኃላፊነት ለመሸከም የሚወስንበት፤ ተፈጥሮአዊና ሣይንሳዊ ክስተቶችን በጥልቀት ለመመርመር ወይም ያስፈልገኛል ብሎ ያመነውን ሁሉ ለማግኘት አቅሙን አምጦ የሚሰራበት ወቅት በመሆኑ አብዮታዊ ባህሪው በልኬት ከጉልምስና አና ከዚያ በላይ ካለው የእድሜ ክልል ጋር ሲነፃፀር በእጅጉ የተለየ እና ከፍ ያለ መሆኑ የሚፈጥርለትን አቅም በአሉታዊም ሆነ በአዎንታዊ መንገድ ሲጠቀመው የተሻለ የውጤት ለውጥ ስለሚያመጣ ወጣትነት ጥንቃቄ የሚፈልግ አደገኛ የእድሜ ክልል ነው ለማለት ይቻላል፡፡
በአለም የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ የማይተካ ሚና እንደ ነበረው የተመዘገበለት ወጣት የማህበረሰብ ክፍል ለአዎንታዊ ተፅዕኖውም ሆነ ለአሉታዊ ውጤቱ ዋነኛ አመላካች እና ባህሪውን በመቅረፅ እረገድ ሰፊውን ድርሻ የሚወስዱት በእድሜ የሚልቁት የስርዓት መሪዎች በመሆናቸው ወጣቱ ትውልድ በየዘመኑ የስርአት ዘዋሪዎች ዋነኛ መሳሪያ ከመሆን ባሻገር በራሱ እንደ መደብ የማይቆጠር እና በመደቦች ውስጥ እንደየ ስሜቱ ከመስራት ባሻገር እምቅ ኃይሉን ለመጠቀም የሚያስችል ምቹ ሁኔታ ያልነበረው ነው ማለት ይቻላል፡፡
በማህበረሰብ እድገት ውስጥ ወጣትነት የቤተሰብ አባል እንጂ መሪ የመሆን እድል ስለማያስገኝለት አቅምን አሟጥጦ የሚጠቀመው የቤተሰቡን ሁለንተናዊ አቅም ለመገንባት ይሆናል፡፡ ጎበዝ ገበሬ ወይም ሞያዊ ሰራተኛ ቢሆን፤ ወታደር ወይም ሐኪም ቢሆን በተሰማራበት መስክ ሁሉ ቤተሰቡን ወይም ማህበረሰቡን የሚያገለግልበት ወቅት እንጂ ለውሳኔ ሰጪና ለአመራርነት የሚያበቃ ሁኔታ አልነበረውም፡፡
በጥንታዊ የጋርዮሽ ስርዓት ዋነኛ አገልጋይ፤ በባሪያ ፍንገላው ዘመን ተፈላጊ ሆኖ ለሽያጭ የቀረበ፤ በቡርዣው ሥርአት፤ በማርክሲስቱ ዘመን፤ በሶሻሊስት የማህበረሰብ እድገት እና በካፒታሊስቱ ዕርዮተ ዓለም ውስጥ ሰፊውን ድርሻ በመውሰድ፤ በዘመን ውስጥ እየዘመነ ሲሻገር አብዛኛው በባህሪ ቀረፃ የወለደው ስርአት እራሱ ስለሚባለው ወጣትነትን ሳይሻገር ለማለፍ ይገደድ ነበር፡፡
ይህም ሲባል ወጣት በሙሉ በሞት አልቋል ወደሚል ጥግ የሚወስድ ሳይሆን ቁጥሩ ቀላል ያልሆነ በየዘመኑ ፊት አውራሪ ሆኖ መርገፉን ማመላከት ነው፡፡ በቀደመው ዘመን ወጣቱ ትውልድ ባህሪውን በሚቀርፁት ከሱ በቀደመው ሀይሎች ሥርአት ለመኖር የሚገደድ እና አሁንም ከዚያ ኋላ ቀር ተፅዕኖ ያልተላቀቁ መሪዎች ባሉበት ሀገር ሁሉ የአምባ ገነኖች ሰለባ ሆኖ መቀጠሉ ይስተዋላል፡፡ በቀደመው ዘመን ቦርዣዎች ቡርዣ ሲያደርጉት፤ ባሪያ ፈንጋዮች ሲሸጡት፤ ሶሻሊስቶች አብዮተኛ አድርገው ሲማግዱት ኑረው በሊብራላዊ አስተሳሰብ ተወዳዳሪ የመሆን መብት እስካገኘበት ጊዜ ለሁለተኛ ወገን መሳሪያነት ከመዋል ባሻገር ትርጉም ያለው ሚና መጫወት ሳይቻለው የቆየ በመሆኑም ማህበራዊ ችግሩ እንደከፋ እንዲቀጥል አድርጎታል፡፡
የቡርዣው ምሁራን በማህበራዊ የስነ ምግባር ችግር የሚከሰተውን ሥርአት አልበኝነት የወጣትነት ተፈጥሮአዊ መገለጫ፤ አካላዊና ስነ ልቦናዊ ችግር አድርገው ከማቅረባቸው በላይ የመደብ ሥርአት አራማጆች በዘመናቸው ወዛደሩን ሊተካ የሚችል እራሱን የቻለ አንድ ማህበራዊ መደብ የሚለውን የተሳሳተ ስሌታቸን አጠናክረው በስርአቱ ልክ የሰፉትን ወጣቱ እንዲያጠልቀው ማስገደድ አንደ አማራጭ መከተላቸው ያስከተለው ከፍተኛ ቀውስ እንደ ጥሩ ማሳያ ሊወሰድ ይችላል፡፡
ወጣቱ ትውልድ በማንኛውም ህብረተሰብ ውስጥ ግማሽ ያህል የሚሆነውን ቁጥር የሚሸፍን በመሆኑ በዚያ ዘመን በነበረው የመደብ ትግል ውስጥ ጉልህ ስፍራ መያዙ አልቀረም፡፡ ይህ ማለት ግን አንደ ማርክሲስታውያን ወጣቱ አንድ ውጥ መደባዊነት ነበረው ማለት ሳይሆን ወጣት ወዛደር በተሰማራበት የወዛደር መደብ ወጣት ገበሬ ወይም ተማሪ እንዲሁ በየመስኩ ከእድሜ አንድነት በላይ አንድ በሚያደርገው የፍላጎት እና የልዩ ልዩ መብት ማረጋገጫ የትግል አውድ ውስጥ ተሰባጥሮ እየገባ አይነታኛ ሚና የሚጫወት ነበር ለማለት የሚያስችል ብቻ ነው፡፡
የቡርዣውን ምሁራን ፍልስፍና ውድቅ በማድረግ ላይ ተመስርቶ በዝባዥና ተበዝባዥነትን እታገላለሁ በማለት የተስፋፋው ሶሻሊስታዊ የፖለቲካ ኃይል በበኩሉ ወጣቱን እንደ አንድ መደብ ባይቆጥርም ወጥ የሆነ የአደረጃጀት ቅርጽ አንዲይዝ በማድድረግ ለአብዮት ማቀጣጠያ በፍጆታነት በመጠቀም እረገድ መጠነኛ ስኬት አሳይቷል፡፡
በመካከለኛው የታሪክ ዘመን በአውሮፓ የነበረውን የፌውዳል ፈላጭ ቆራጭ ስርአት ለመታገል በሚል የመጀመሪያው የወጣት ተማሪዎች ማህበር የተደራጀው የካፒታሊስት ማህበረሰብ በሚባለው ፖለቲካዊ ምዕራፍ ነበር፡፡ ይህ የካፒታላዊ ስርዓት ከቡርዥው ስርዓት ሁለት ምዕራፍ ኮስሻሊስታዊው መደባዊ ስርዓት ቢያንስ በአንድ ምዕራፍ ወደ ፊት የተሻገረ በመሆኑ የወጣቱን ጉዳይ በመጠቀም እረገድ የተሻለ አቅጣጫ መያዙን አመላክቶ ነበር፡፡
በቅድመ መደብ ታሪክ ማህበራዊ ስርአት በአብዛኛው ባይሎጂካዊ “የተፈጥሮ ሳይንስ” ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ለተፈጥሮ የሥራ ክፍፍል ዋነኛ መሳሪያ በመሆን የሚያገለግሉት እድሜ እና ፆታ ስለ ነበሩ ማንኛውም ሥራና ማህበራዊ ግዴታ በዕድሜው ሊለካ በሚችል የጉልበት መጠን ወይም በፆታ ከሚከፋፈለው በቀር ሁሉን በጋራ ይከውን ስለ ነበረ ሶሻሊስታዊው የመደብ ሥርአት ወደ ዴሞክራሲያዊ ባህሪ ማዝመም እስከ ጀመረበት ዘመን ወጣትነት አግባብ ያለው ትርጉም ይዞ ሚናውም በውል ተለይቶ ይታወቅ ነበር ማለት አይቻልም፡፡

No comments:

Post a Comment