Tuesday, November 5, 2013

የኢትዮጵያ መንግስት ፌስቡክን ከጠዋቱ 3 ሰዓት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ሊዘጋ ነው


(ዘ-ሐበሻ) የኢትዮጵያ መንግስት ፌስቡክን ከጠዋቱ 3 ሰዓት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ሊዘጋ 
መሆኑን የዘ-ሐበሻ ታማኝ ምንጮች ገለጹ። ከአዲስ አበባ የመጡ መረጃዎች እንደጠቆሙት ሕዝቡ በተለይ ነፃ ሚዲያ በሌለበት ሃገር መረጃዎችን ከፌስቡክ በቀላሉ ማግኘት በመቻሉና የንቃት ደረጃውም እየጠነከረ በመሄዱ የሃይለማርያም ደሳለኝ መንግስት “በመንግስት መሥሪያ ቤቶች እና በትምህርት ቤቶች በከፍተኛ ሁኔታ የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ቁጥር እየበዛ በመምጣቱ የመማር ማስተማሩን ሂደትም ሆነ የሥራ ሁኔታዎችን አስተጓጉሏል” በሚል ሰንካላ ምክንያት የፌስቡክን አገልግሎት ለማገድ ተዘጋጅቷል።

በግብጽም ሆነ በቱኒዚያ የተነሱት የአረቡ ዓለም አብዮቶች አድማሳቸው በአንድ ጊዜ የተንሰራፋው እንደፌስቡክ ባሉ ቀላል የማህበራዊ ሚዲያዎች መሆኑን የተረዳው የኢትዮጵያ መንግስት ነፃ ጋዜጦችን ዘግቶ ሁሉን ሚዲያ በተቆጣጠረበት በዚህ ዘመን እንደ ዘሐበሻ እና ሌሎችም ያሉ የኢትዮጵያ ድረገጾች ኢትዮጵያ ውስጥ እንዳይታዩ ቢታገዱም በፌስቡክ እና በትዊተር አማካኝነት በሰፊው እየተነበቡ በመሆኑ መንግስት “ተማሪዎች ፌስቡk እየተጠቀሙ በትምህርታቸው ደካማ ሆኑ፤ የመንግስት ሠራተኞችም ሥራቸውን ጥለው ፌስቡክ ላይ እየተጣዱ የመንግስትን ሥራ እየበደሉ ነው” በሚሉ አንካሳ ምክንያቶች ከጠዋቱ 3 ሰዓት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ለማገድ መዘጋጀቱን ምንጮቻችን ጠቁመዋል።

በኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፌስቡክ ተጠቃሚዎች ቁጥር በ እጅጉ እየጨመረ መሄዱና መንግስት እንዲሰሙ የማይፈልጋቸው መረጃዎችም በአጭር ጊዜ ሕዝብ ጋር መድረሳቸው የስርዓቱ ራስ ምታት እየሆነ መምጣቱን በተደጋጋሚ መዘገባችን አይዘነጋም።

No comments:

Post a Comment