Monday, February 10, 2014

ህወሓት ከመለስ ጋር አብሮ ተቀብሯል (ክፍል ሁለት)


February 10, 2014
ከነፃነት አድማሱ dalul@gmail.com

የሰው ልጅን ነፃነት የማይገባው ነፃ አውጪ!!

በትግራይ የህወሓት እኩይ ተግባር በቅርብ የተከታተሉት አንድ የሽሬ እንዳስላሴ አዛውንት እንዲህ በማለት በምሬት ይገልፁታል። “ደርግ ሰው ገድሎ በአደባባይ ይፎክር ነበር። ዛሬ ህወሓት ግን ሰው ገድሎ ልቅሶ ይደርሳል” ሲሉ የድርጅቱን እርኩስነት፣ አስከፊነትና የሰብኣዊ ፍጡር ባላንጣነት ካለፈው የደርግ አገዛዝ ጋር በማነፃፀር ቁጭታቸውን በትካዜ ሲናገሩ አጋጥሞኛል። የዛሬው ፅሑፌም ካለፈው ክፍል አንድ የቀጠለ ነው። በክፍል አንድ የተነሱ ዋና ዋና ጥያቄዎችም በኋላ በዝርዝር ለማስቀመጥ እሞክራለሁ። ለዛሬ ግን ቀደም ብዬ በክፍል አንድ የጀመርኩትን “አደናግረህ፣ አስፈራርተህ፣ አሸብረህ፣ ወገን ከወገኑ ጋር አናቁረህና ለያይተህ ግዛ” የሚለውን የህወሓት የደደቢት የደንቆሮ ፍልስፍናና መፈክር በሚመለከት አጭር ማጠቃሊያ በማከል ፅሑፌን እቋጫለሁ።Tigray People Liberation Front Split
አዎ!! ህወሓት ለትግራይ ህዝብ ሶስት ጊዜ ገድለታል። መጀመሪያ ኤርትራን ከእናት ሀገርዋ ገንጥሎ ነፃ ለማውጣት በአስር ሽዎች የሚቆጠሩ የትግራይ ለወጋ ወጣቶች የሻዕቢያን ህይወት ለማዳን ሲባል በሳሕል በረሃ የአሞራ ሲሳይና የአቶ ኢሳያስ አፈ ወርቂ የስልጣን ማዳበሪያ ሆኖው እንዲቀሩ አድርጓል። ሁለተኛው አስከፊ ሞት ህዝቡ የባህር በሩን በመዝጋት ሉዓላዊነቱንና ብሄራዊ ጥቅሙን ከእጁ ነጥቀው ለማዕዳን አሳልፈው በመስጠት በህዝቡ ደም ቀልደዋል። ሶስተኛው አሳፋሪው ሞት ደግሞ ህዝቡ “ሻዕቢያ ይወረናል” እያለ ሲጮኽ ጆሮ ዳባ በመስጠት እንደገና ተመልሶ በኤርትራ ዳግም እንዲወረር በማድረግ ብሄራዊ ክብሩን እንዲደፈር፣ ዳር ድንበሩንና አንጡራ ሀብቱን እንዲዘረፍ፣ እንደ ዓይደር ትምህርት ቤት የመሳሰሉትን ጨምሮ ዳግም የሐውዜን ዓይነት እልቂት እንዲፈጠር አድርጓል። በአጠቃላይ የትግራይ ህዝብ ለባዕድ ጅብ አሳልፈው በመስጠት ለኤርትራ ነፃነት የከፈለውን የወጣቶቹን መስዋእትነት ደመ ከልብ ሆኖ እንዲቀር ተደርጓል።
ይህ በዓይናችን ያየነው በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ ተሰምቶ የማይታወቅ ብሄራዊ ውርደት፣ ሐፍረትና የታሪክ ጉድፍ መሆኑን ማንም ሀገር ወዳድ ዜጋ ሊገነዘበውና ሊቆጨው የሚገባ ጉዳይ ነው። በአባቶቻችን ተጠብቆ የቆየውን ክብራችንና ዳር ድንበራችንን የባዕዳን ደላላ በመሆን ያስደፈረ፣ ያዋረደ፣ የቸረቸረና ይቅር የማይባል ሀገራዊ ክሕደት የፈፀመው በሻዕቢያ ጡጦ ያደገው ህወሓት መሆኑን በያለንበት ለልጅ ልጆቻችንም ሳይቀር መናገርና ማስተማር መቻል አለብን።
አዎ!! የትግራይ ህዝብ ችግር በዚህ ብቻ አላበቃም። ቀደም ሲል ደርግን አሸንፈው ወደ አዲስ አበባ ብሄራዊ ቤተ መንግስት ገብተው ስልጣናቸውን ለማጠናከርና ለማደላደል ህዝቡን እንደ መሳለል አድርገው ከተጠቀሙበት በኋላም ዛሬም ትግራይ የርስ በርስ መበላላት፣ ግድያ፣ ድብደባ፣ አድልዎ፣ ዝርፊያና ሕግ አልባ ድርጊቶችን የሚፈፀምባት የጥፋትና የጭቆና ሞዴል ሆና ትገኛለች። የንፁኃን ደም የስልጣናቸው መቋደሻና መናገሻ አድርገው የሚጠቀሙ የህወሓት ሰበው በላ ካድሬዎችና መሪዎቻቸው ህዝቡን በመናቅና በማንቋሸሽ “ብንደበድብ የት ትደርሳለህ?!! መሳሪያውና ነፍጡ እንደሆነ በእጃችን ነው። ከኛ በላይ ነፋስ እንጂ ሌላ ሀይል የለም። ረግጠን ብንገዛህና የፈለግነው ብናደርገህ ማን ያድናሃል?!! ከኤርትራም ሆነ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር እንደሆነም አጣልተናሃል።!! ስለሆነም ወደድክም ጠላህም ከእጃችን አታመልጥም። ስለዚህ አርፈህ ተገዛ።!! አፍህን ያዝ!! በነፃ መናገር ማን አስተማረህ? …. እያሉ እንደ ህፃን ልጅ በአለንጋ ሲገርፉትና በአደባባይ ሲቀጠቅጡት ይገኛል።
ታዲያ!! ለዚህ ሚስኪን ህዝብ ጠበቃ፣ ደራሽና አለሁልህ ባይ ማን ይሆን?። ትግራይ ብዙ ጀግኖች እንዳልወለደች ሁሉ ዛሬ በባዕድ ወረራ ጊዜ እንኳን በምንም መልኩ ያልታየ ጉድ እያየን ነው። ሰዎች በገዛ ሀገራቸው ጠላት እየተባሉ በአደባባይ የሚደበደቡባት፣ በእስር ቤት ቁም ስቃይ የሚታይባት፣ ህዝቡ ባለቤትና አቤት የሚልበት የፍትሕ ቦታ አጥቶ በሆዱ እያለቀሰ የሚኖርባት ምድራዊት ሲኦልና የጭካኔ ሞዴል ሆና እስከመቼ ትቆይ? እውነት ለራሳቸው ነፃ ያልወጡ የሻዕቢያ ተላላኪ የሆኑት የህወሓት ማፍያ መሪዎች የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጪ ናቸውን? ለሚለው ጥያቄ መልሱና ፍርዱ ለአንባቢዎቼ ትቻለሁ።
ይሁን እንጂ ለባዕድ የማይንበረከክ፣ ጀግናና አትንኩኝ ባይ ህዝብ በላዩ ላይ ይህ ሁሉ ግፍ ሲፈፀምበት እየታየ ለምን ዝም ተባለ? በአካባቢው ሰው የለም ወይ? ያ ሁሉ ጀግና እየተባለ በትጥቅ ትግል ያለፈውና ራሱን ነፃ አውጪ ነኝ ሲል የነበረው ሰፊው የህወሓት ታጋይስ የት ገባ? የለውጥ ቀዳሚና ግንባር ቀደም መሆን የነበረበት የትግራይ ምሁሩና ተማሪውስ ምን ዋጠው? የትግራይ ተወላጅ ሆኖ የገዛ ወንድሙ በአደባባይ እንደ ውሻ በዱላ መደብደብስ የትግራይ ህዝብ ባህል ነው ወይ? ዛሬ በትግራይ ምድር ምን ዓይነት ትውልድ ነው እየተፈጠረ ያለው።? ችግሩ ለምን በትግራይ ያን ያህል የከፋ ሊሆን ቻለ።? ሌላው ኢትዮጵያዊስ በትግራይ አካባቢ ስለሚፈፀመው አስነዋሪ ተግባር ግንዛቤው ምን ያህል ነው።? የሚሉና ሌሎች ተዛማጅ ጥያቄዎችን በመጨመር በሚቀጥለው ሶስተኛ ክፍል ፅሑፌን አስር ነጥቦችን ያካተተ ዝርዝር ሓተታ ይዤ እቀርባለሁ። በቸር ሰንብቱልኝ!!

No comments:

Post a Comment