Tuesday, February 11, 2014

የአ.አ ፍትህ ቢሮ የሙስሊሙን ትግል አዳክመውልኛል ያላቸውን የመንግስት ሃላፊዎችን እና የህገ ወጡ መጅሊስ አባላትን በሽልማት አንበሸበሸ




ከአብዱ ዳውድ ኡስማን
መንግስት በኢስላም ሀይማኖት ላይ ጠልቃ እንደገባ የህወሃት መስራች አቦይ ስብሃት ለመጀመሪያ ጊዜ አምነዋል ፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍትህ ቢሮ አማካኝነት የተዘጋጀው ይሄው የሽልማት ስነስርዐት ዋነኛ አላማው የሙስሊሙ ትግልን ለማዳከም ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል ያላቸውን የመንግስት አካላትና የህገ ወጡ መጅሊስ አባላትን ለማነቃቃት እንደሆነ ታውቋል ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በቀጣይ ከምርጫ ቅስቀሳ ጋር ተያይዞ ለሚኖረው እንቅስቃሴ አባላቱ በሞራል እንዲሰሩ ለማድረግ ታስቦ እንደሆነ በስብሰባው የነበሩ ምንጮች ገልፀዋል ፡፡
ከትላት በስቲያ እሁድ የካቲት 2\2006 ከጠዋቱ 3፡30 ጀምሮ ስድስት ኪሎ በሚገኘው የስብሰባ ማእከል በተካሄደው በዚህ የሽልማት ስነስርዐት ላይ የህወሃት አባት የሚባሉት አቦይ ስብሃትን ጨምሮ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍትህ ቢሮ ሃላፊ አቶ ፀጋዬ ሀይለማሪያም ፣ የህገ ወጡ መጅሊስ ፕሬዚደንት ዶክተር አህመድ አብዱረህማን ፣ የፌዴራሉ ህገ ወጥ መጅሊስ ምክትል ፕሬዚደንት ታጋይ(ሸይክ ከድር ) ፣ የአንዋር መስጂድ ኢማም ሀጂ ጡሃ ሃሩን ፣ የ10 ሩም ክፍለ ከተማ ሃላፊዎች ፣ የወረዳና የክፍለ ከተሞች መጅሊስ አመራሮች እንዲሁም ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል ፡፡

ከሽልማቱ ቀደም ብሎ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ መስተዳድሩ የ42 መስጂዶችን ካርታ ለአዲስ አበባ ህገ ወጡ መጅሊስ ፕሬዚደንት ዶክተር አህመድ እንዳስረከቡ ገልፀዋል ፡፡ በቀጣዩ ሀገራዊ ምርጫም የመጅሊሱ አባላትም ሆኑ ሌሎች አካላት ከዚህ ቀደም ወደ 54 መስጂዶች ካርታ እንደሰጠን በዛሬው እለት ደግሞ የ42 መስጂዶችን ካርታ እንደሰጠን ለሙስሊሙ በማስተጋባት የምርጫ ስራ እንዲሰራ ጠይቀዋል ፡፡
በእለቱ የሙስሊሙን ትግልና ኢስላምን አዳክመዋል የተባሉ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ፣ እንዲሁም የህገ ወጡ መጅሊስ አባላት ከአዲስ አበባ ፍትህ ቢሮ ሽልማት የተበረከተላቸው ሲሆን ተሸላሚዎቹ በየተራ ንግግር አድርገዋል ፡፡ የሙስሊሙን እንቅስቃሴ በጥረታቸው እንዲገታ አድርገዋል ተብለው ሽልማቱ ከተበረከተላቸው መካከል አቦይ ስብሃት ነጋ ፣ ዶክተር አህመድ አብዱረህማን ፣ ሸህ ጡሃ ሃሩን ፣ የ10ሩም ክፍለ ከተማ ህግና ፍትህ ቢሮ ሃላፊዎች እና የ10ሩም ክፍለ ከተሞች የመጅሊስ ሊቀመንበሮች እንደሆነ ታውቋል ፡፡

ከሽልማቱ በኋላ ንግግር ያደረጉት አቦይ ስብሃት መንግስት በሙስሊሙ ጉዳይ ጠልቃ እንደገባ የሚያረጋግጠውን ንግግራቸውን አድርገዋል ፡፡ አቦይ ስብሃት በአዳራሹ ለተገኘው ሰው ባደረጉት ንግግር “ … ማንኛውም ነገር ከፍተኛ ጥረት ከተደረገበት ስኬት ይኖረዋል ፡፡ የሙስሊሙ ትግል ሲጀመር በጣም ተደናግሮን ነበር ፡፡ በኋላ ብዙ አስበንበት ስናበቃ ለምን መንግስትን የሚደግፍ መጅሊስ አናቋቁምም አልንና ጥረት ጀመርን ፡፡ እኔ እራሴ ሄጄ ግዴላችሁም ከየክፍለ ከተማው ሙስሊም ሆነው መንግስትን የሚደግፉ ሁለት ወይም ሶስት ሰዎችን ብቻ ፈልጉልኝ አልኩ …፡፡

የጀመርነው ከቦሌ ክፍለ ከተማ ነው ፡፡ ወደ አምስት ሰዎችን አገኘንና እነሱን አደራጀን ፡፡ በኋላ ሌሎችም ክፍለ ከተሞች የቦሌን ተሞክሮ እንዲተገብሩ አደረግን ፡፡ ሁሉም ክፍለ ከተሞች ጥቂት ሙስሊሞችን አደራጁ ፡፡ ከዚህ በኋላ ነገሩ ሁሉ የተቃና ሆነ ፡፡ እኛም በሁሉም ክፍለ ከተሞች በተወሰኑ ሰዎች መደራጀቱን ስናውቅ ጉዳዩን የአዲስ አበባ ፍትህ ቢሮና ክፍለ ከተሞች እንዲረከቡንና በበላይነት እንዲቆጣጠሩት አደረግን ፡፡ እንዲህ እያለ የሄደው ጥረት አሁን አክራሪዎችን ለማቆም የሚያስችል ጉልበት እንድናገኝ ረድቶናል … ” ብለዋል ፡፡


(የአዲስ አበባ ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ)   
ይህ የአቶ ስብሃት ነጋ ንግግር መንግስት በሙስሊሙ ጉዳይ ጠልቃ አልገባሁም እያለ ከሚያስተባብለው ጋር የሚጋጭ እንደሆነ ተገልፇል ፡፡ በበርካታ ጉዳዮች ንግግር ያደረጉት አቦይ ስብሃት ኢስላምን የሚያጥላላ ንግግርም አድርገዋል ፡፡ “ ቅድም የፌዴራሉ መጅሊስ ምክትል ሰብሳቢው ሸህ ከድር እንዳለው የዱሮው እስልምና ሌላ ነው ፡፡ እኔ ከድርን በፊት ጀምሮ ትግራይ ውስጥ አውቀዋለሁ ፡፡ ምርጥ የህወሃት ታጋይ ነበር ፡፡ አብሮን ታግሏል ፡፡ አሁን ደግሞ ሙስሊሙን እያገለገለ ነው ፡፡ እስልምና እነዚህ የታሰሩት ሰዎች እንደሚሉት አይመስለኝም ፡፡ እስልምና እነዚህ ሰዎች እንደሚያሳዩት ዓይነት ዕምነት ከሆነ እንደ ዕምነት አያስፈልግም ፡፡ ፈፅሞ ሰዎቹ ለሀገር አይሆኑም ” ብለዋል ፡፡ በዚህ ንግግራቸው በቦታው የነበሩ ሙስሊሞችም ጭብጨባ ለግሰዋቸዋል ፡፡

የፌዴራሉ ህገ ወጥ መጅሊስ ምክትል ፕሬዚደንት የሆኑት ሸህ ከድርም በጫካ ከነ አቦይ ስብሃት ጋር ስላሳለፉት የትግል ህይወት እና በልጅነታቸው ስለቀሩት ቁርዐን አጠር ያለ ንግግር አድርገዋል ፡፡


ሌላኛው ተሸላሚ የሆነው የአዲስ አበባ ህገ ወጡ መጅሊስ ፕሬዚደንት ዶክተር አህመድ ሲናገርም “ መስጂዶቻችንን ሁሉ ተረክበናል ፡፡ መስጂዶች የማይሆን ዳዕዋ ማድረጊና የተቃውሞ መፈንጫ እንዳይሆኑ የሁሉም መስጂዶች ኢማም እንዲቆጣጠሩ ስልጠና ሰጥተናቸዋል ፡፡ አቶ ድሪባ ኩማም ዛሬ ለ42 መስጂድ ካርታዎን እውቅና እንደሰጡልን አረጋግጠዋል ፡፡ ከዚህ በኋላ ልማታችንን ማፋጠን ነው ፡፡ በቀጣይ ከመንግስታችን ጎን ሆነን እንሰራለን ” ብለዋል ፡፡

ለአቦይ ስብሃት ነጋ እና ዶክተር አህመድ አብዱረህማን ለጊዜው ምንነቱ ያልታወቀ ሽልማት የተበረከተላቸው ሲሆን የአንዋር መስጂድ ኢማም ሃጂ ጡሃ ሃሩን ላፕቶፕ ፣ የ10ሩም ክፍለ ከተማ ፍትህ ቢሮ ሃላፊዎች ደግሞ ለእያንዳንዳቸው ዘመናዊ ሞባይል እንደተሸለሙ ታውቋል ፡፡ ሌሎቹም እንዲሁ በተዋረድ ሽልማቱ እንደተበረከተላቸው ምንጮች ገልፀዋል ፡፡

በመጨረሻም የአዲስ አበባ ፍትህ ቢሮ ሃላፊው አቶ ፀጋዬ ሀይለማሪያም ተሸላሚዎቹ ሙሉ ለሙሉ ያልቆመውን የሙስሊሙን ትግል ለማዳፈን ጠንክረው እንዲሰሩ ፣ እንዲሁም በቀጣይ ምርጫውን አስመልክቶ ከመንግስት ጎን ሆነው እንዲሰሩ የሚያሳስብ ንግግር ካደረጉ በኋላ ተሰብሳቢዎቹ ወደተዘጋጀላቸው ምሳ እንዲሄዱ አብስረው የሽልማቱ ስነ ስርዐት እንደተጠናቀቀ ምንጮች ጨምረው ገልፀዋል ፡፡
አላህ በዳዬችን ያዋርዳቸው !!

No comments:

Post a Comment