Monday, September 23, 2013

አወይ ሶሪያ….የኢትዮጵያ ጠላት!

September 23, 2013 (በሰሎሞን ተሰማ ጂ.) የሶሪያ ጉዳይ ከዕለት ወደ ዕለት እየከፋ መጥቷል፡፡ በስልጣን ላይ ያለው ጎሳ “የአላዊት ጎሳ” ይባላል፡፡ አላዊቶችና በደዊኖች በሽፍትነትና በባህር ላይ ውንብድና ስማቸው የገነኑ ናቸው፡፡ በደዊኖች፣ ሶሪያን ለዘመናት ያህል ሲፈልጧትና ሲቆርጧት ኖረዋል፡፡ እንደነሱ ዘረኛ፣ እንደበደዊኖች ጠባብ፣ አክራሪና ቁመኛ ታይቶም-ተሰምቶም አይታወቅም፡፡ አላዊቶችም ቢሆኑ “አልሸሹም ዞር አሉ” ናቸው፡፡ እነዚህ ወገኖች፣ የሶሪያን ሀገረ-መንግሥት (State apparatus) ከተቆጣጠሩበት ዘመን ጀምሮ ለኢትዮጵያ በጎ ተመኝተውላት አያውቁም፡፡ ይባስ ብሎ ደግሞ፣ ከ1950ዎቹ መጀመሪያ ወዲህ እጅግ በከፋ መልኩ የኢትዮጵያን ጥቅምና ሉዓላዊነት በሚፈታተን መልኩ በግትርነት ቆመው ነበር፡፡ በጣም በተጋነነና በመረረ ኹናቴ መንቀሳቀስ የጀመሩት ግን ከ1953ዓ/ም ወዲህ ነው፡፡ በዚህ ዓመትም በጂዳ-ሳዑዲት ዓረቢያ የተቋቋመውን “የኤርትራ ነፃ-አውጪ ድርጅት” (ወይም በተለምዶ አጠራሩ ጀ.ብ.ሐ) እየተባለ የሚታወቀው፣ በአሳውርታ የሚኖሩት የቤንአሚር ጎሳ ተወላጆች ቡድን ለመደገፍ በደዊኖች ተሯሯጡ፡፡ ከእነርሱም ቀጥሎ ወደስልጣን የመጡት አላዊቶች ተመሳሳይ ተግባር ፈፀሙ፡፡ ያለምክንያት አልነበረም፤ በአሳውርታ የሚወለዱት ቤንአሚሮች “የበደዊንና የአላዊት ደም አላቸው” ከሚል ጎሰኛ ቀመር ተነስተው ነው፡፡ Syria officially the Syrian Arab Republic ስለሆነም፣ በ1955ዓ/ም በይፋ ለጀ.ብ.ሐ አገናኝ ቢሮ በደማስቆ ከተማ ተከፈተለት፡፡ ከዚያም ጊዜ ጀምሮ፣ በርካታ ፀረ-ኢትዮጵያ እንቅስቃሴዎችን መደገፍ ጀመሩ፡፡ በ1960 እና 1961ዓ.ም ብቻ እንኳን፣ “ነፃነትን-መደገፍ” በሚል ስም፣ እ.አ.አ እስከ 1970 ድረስ በበደዊን ጎሳዎች የሚመራው የሶሪያ መንግሥት በርካታ የአጋሚዶ/የውንብድና ተልዕኮዎችን ከአፍ-እስከ-ገደፉ ደግፏል፡፡ (ይሄንን በተመለከተ፣ በ1933ዓ/ም በደቀሽሐይ-ሐማሴን የተወለደውና በጀብሐ ውስጥ የ5ተኛው ወታደራዊ ክፍል/ምድብ ዋና መሪ የነበረው፣ ወልዳይ ካህሳይ ብዙ-ብዙ ነገር ያወሳናል፡፡ ወደኋላ ላይ እንመለስበታለን፡፡) በዚህ የመቀራረብና የመተሳሰብ ዘመን በሆነው በ21ኛው ክፍለ ዘመን፣ በደዊኖችና አላዊቶች ከአንድ መንግሥት የሚጠበቀውን ዓለም አቀፍ ኃላፊነት ዘንግተው፣ ዓለም አቀፍ ውንብድና ውስጥ ሙጭጭ አሉ፡፡ በዘመናዊ አስተዳደር፣ ሃይማኖትና ጎሳ እምብዛም ቦታ እንደሌላቸው ያልተገነዘቡት በደዊኖችና አላዊቶች፣ በዘር፣ በጎሳና በሃይማኖት ጥላ ስር የተሰባሰቡትን ወንበዴዎች ሁሉ በወታደራዊ ስልጠናና በትጥቅ ሲረዱ ኖረዋል፡፡ በዚህም አቋማቸው የተነሳ በመካከለኛው ምስራቅ ውስጥ የተነሱትን ማናቸውንም ግጭቶች ቤንዚን በማርከፍከፍ ሲጋግሙት ኖረዋል፡፡ ወይም በሀገራችን አባባል ጭድ ሲነሰንሱበት ኖረዋል፡፡ ሊባኖስ ቀንደኛዋ ተጎጂ ናት፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሯ ሐሪሪ ሳይቀሩ የተገደሉት በሶሪያ ጎሰኞች መሰሪ ደባ ነው፡፡ (በአሜሪካዊያኑና በበርካታ የዓረቡ ዓለም ሰዎች የተጠላውና የተወገዘው-“ጫማ ሳይቀር የተወረወረበት”-ትንሹ ጆርጅ ቡሽ እንኳ፣ “የዳቢሎስ ዛቢያ (Evil Axes)” ብሎ እስኪጠራት ድረስ፣ የበደዊኖቹና የአላዊቶቹ ሶሪያ፣ እጅግ አገደኛ ምሳር ናት፡፡) ከአላዊቶች ጎሳ/ወገን የሆነው የሶሪያው ፕሬዝዳንት፣ በሺር አላሳድ ይባላል፡፡ ከደማስቆ ዩኒቨርሲቲ በዓይን ሕክምና (Ophthalmology) ዶክተር ነው፡፡ እ.አ.አ ከ2000ዓ/ም እስካሁን ድረስ በስልጣን ላይ ተፈናጧል፡፡ ከእርሱ በፊትም አባትየው ሀፊዝ አላሳድ (እ.አ.አ ከ1971-2000) ሶሪያን አንቀጥቅጦ ገዝቷታል፡፡ የጦር ጀነራልና ከ1946 (እ.አ.አ ጀምሮ የባዐዝ ፓርቲ አባልና መሪም ነበር፡፡) አላዊቶችም የበደዊኖቹ በሽታ አለባቸው፡፡ እነርሱም ከላይ እንደገለጽነው-ዘረኝነት፣ ጠባብነትና አክራሪነት ናቸው፡፡ ከ1957ዓ.ም ጀምሮ በኮሚኒዝም ስብከትና አስተምህሮት ናላቸው የዞሩትን ተማሪዎችና ወጣቶች ለመደገፍ የሩሲያ፣ የቼኮዝሎቫኪያና የቻይና መንግሥታት ያልተገደበ ጥረት አድረገዋል፡፡ ለዚህም ማሳያው ደግሞ፣ በመጋቢት 4/1961ዓ.ም ሁለት የሩሲያ፣ ሦስት የቼኮዝሎቫኪያና ሁለት የቻይና ዜጎች ኢትዮጵያን በ24 ሰዓታት ውስጥ ለቀው እንዲወጡ ተደርገዋል፡፡ ሁሉም፣ ኮሚኒዝምን በየትምህርት ቤቱና በየኮሌጆቹ ለማስረጽ በመሞከራቸውና ወጣቶችን ለዓመጽ በመቀስቀሳቸው ነበር፡፡ ይህ ሴራቸው የተደረሰባቸው ሦስቱ አገሮች ጀብደኛውን የሶሪያ ጎሰኛ መንግሥት እንደፈለጉት ተጠቅመውበታል፡፡ እነዚህ ጊዜ የሠጣቸው ኃያላን መንግሥታት፣ የራሳቸውን ተጽዕኖ ኢትዮጵያ ላይ ለመጣልና በሀገራችን ጉዳይ ጣልቃ ለመግባት ያልፈነቀሉት ነገር አልነበረም፡፡ ያ ስር የማይሰድላቸው ቢመስላቸው፣ የሶሪያን ጣልቃ ገብነት ተማፀኑ፡፡ አርቀው የማያዩትም የሶሪያ መሪዎች ዘው ብለው ገቡበት፡፡ ምክንያታቸው ግልጽ ነው፤ የሶሪያ ጣልቃ ገብነት ለሌሎች ኃያል ኮሚኒስቶች መሣሪያና ስልጠና መሸጋገ ድልድይ በመሆን ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ፣ “ነጋዴ ራሱ ስለተቀማ ሳይሆን፣ ሌላው ነጋዴ ስለዳነ ይቆጫል፤” በሚለው የአገራችን ምሳሌ አማካይነት ሊተረጎምም ይችላል፡፡ የሶሪያ መንግሥት በሀገሩ ውስጥ ያለውን ሁከት፣ ትረምስና ብጥብጥ፣ ከዚያም አልፎ ከእስራኤል ጋር ከነበረው የተደጋገመ የተጠቂነት ሽንፈት የዜጎቹን አስተሳሰብ ለማስቀየስ፣ ሌሎች የእስራኤል መንግሥት ወዳጆች ናቸው ያላቸውን አገሮች በመተናኮል ሊወጣ ሞክሯል፡፡ ይህ አባዜ፣ “ወድቆ የቆመው እንደመጎተት” ዓይነት ነው፡፡ ከላይ እንደገለጽነው፣ የሶሪያ መንግሥት በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባት ከጀመረና ኢትዮጵያን መተናኮልም ከጀመረ ቆይቷል፡፡ በ1958ዓ.ም ከኢትዮጵያ ተጠልፎ ወደካርቱም የተወሰደውን የኢትዮጵያ አይሮፕላን የጠለፈው ወጣቱ ከበደ ደበላ፣ መጀመሪያ ጥገኝነት ያገኘው ሶሪያ ደማስቆ ነበር፡፡ የፈረንጆቹ 1969 ዓ.ም ደግሞ የሶሪያ የጠላትነት ሽፍንፍን ቅልጥጥ ብሎ የወጣበት ዓመት ሆነ፡፡ በዚሁ ዓመት ከተሞከሩት የኢትዮጵያን አየር መንገድ የማጥቃት አምስት ሙከራዎች ውስጥ አራቱ የሶሪያ መንግሥት ቀጥተኛ ድጋፍ ነበራቸው፡፡ በዕለተ ማክሰኞ መጋቢት 2/1961ዓ.ም ፈራንክፈርት አይሮፕላን ማረፊያ በቆመበት በሁለት ፈንጂዎች የተቀጣጠለውን ቦይንግ 707 አይሮፕላን በስልጠናና በትጥቅ የደገፈችው ሶሪያ ነበረች፡፡ በዚሁ ዓመት፣ በሚያዝያ 2/1961ዓ/ም በካይሮ ከተማ አቅራቢያ (105 ኪ.ሜ በስተደቡብ) ከወደቀው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋግላስ ሲ-47 አይሮፕላን አደጋ ጀርባም ያለችው መሰሪ ሶሪያ ነበረች፡፡ በሰኔ 11/1961ዓ.ም ከምሽቱ 1፡15 ላይ ካራቺ አይሮፕላን ማረፊያ እንደቆመ ነበር በእጅ መትረየስ ከ50 ሜትር ርቀት ላይ አደጋውን የያሉት፡፡ እነዚህ ሦስት ሽፍቶች ከሶሪያ ተነስተው ካርቱም ላይ ሴራቸውን ካቀነባበሩ በኋላ፣ ወደ ቤይሩት በረሩ፡፡ ከዚያም ፓኪስታን ሁለተኛዋ ከተማ ካራቺ ደረሱ፤ አደጋውንም ጣሉ፡፡ ስማቸውም-መሐመድ ኢድሪስ፣ ፍስሐዬ አብርሃምና ዓሊ አብደላ የሚባሉ ናቸው፡፡ ሦስቱም ስልጠናቸውንና ትጥቃቸውን ከሶሪያ መንግሥት ያገኙ የጀብሐ አባሎች ነበሩ፡፡ ከእነዚህም የሶሪያ ቅጥረኞች ቀጥሎ፣ በዕለተ ሰኞ ነሐሴ 5/1961ዓ.ም ከአስመራ ተነስቶ በባሕር ዳር በኩል ወደአዲስ አበባ ይጓዝ የነበረውን ንብረትነቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የበረራ ቁጥር-231፣ DC-3 አይሮፕላን ባህር ዳር ከተማ ላይ ተሳፍረው ሲጠለፉትና ወደካርቱም ሲወስዱት ያሉት ነገር ቢኖር፣ “እኛ በማኦሴቱንግ ፍልስፍና የምናምን ኮሚኒስቶች ነን፡፡ አይሮፕላኑንም አስገድደን ወደካርቱም ያመጣነው ወደኮሚኒስት ቻይና ለመሄድ ላቀድነው ጉዞ ልንጠቀምበት ነው፤” ነበር ያሉት፡፡ እነዚህም የሲቪል አቬሽን ወንበዴዎች፣ በቀጥታ ከሶሪያ ጋር ግንኙነት ባይኖራቸው በርዕዮተ-ዓለማቸው የግራ ክንፍ አቀንቃኞች ነበሩ፡፡ የዚህኛው ጠለፋ አድራጊዎች ደግሞ፣ ሰባት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ሲሆኑ፣ በአንዳንድ የባዕዳንን ሴራ ባልተረዱ ወገኖች በበጎ የሚነሱም ናቸው፡፡ ለምሳሌ በ1960 እና 1961ዱ የተማሪዎች ዓመጽ ዋነኛ አስበጥባጭና ተከሳሽ የነበሩት ዋለልኝ መኮንንና ማርታ ይገኙበታል፡፡ ከኋላቸው የነበሩት አገሮች ሩሲያና ቼኮዝሎቫኪያ ናቸው፡፡ በመስከረም 3/1962ዓ/ም ከድሬዳዋ ወደጂቡቲ ሲበር የነበረውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ DC-6B አይሮፕላን መንገድ አስቀይረው ወደ የመን-ኤደን የወሰዱት የጀብሐ ሰዎች ተቀማጭነታቸው ሶሪያ-ደማሽቆ ነበር፡፡ ይህ አይሮፕላን 39 መንገደኞችና አምስት የአውሮፕላኑን ሠራተኞች ይዞ የነበረ ሲሆን፣ ሁሉም በደህና ሁኔታ በመስከረም 5/1962ዓ.ም ከቀትር በኋላ ወደአዲስ አበባ ተመልዋል፡፡ አይሮፕላኑን ሳልይዝ ወደኢትዮጵያ አልመለስም ያሉት ካፒቴን ቀፀላ ኃይሌና ጠለፋውን ያከሸፈው ም/የአስር አለቃ ካሳዬ ታደሰ ኤደን ቀርተዋል፡፡ (በነገራችን ላይ፣ ካሳዬ ታደሰ የሻለቃ ማዕረግ አግኝተው በጡረታ ከሠራዊቱ ከተገለሉ በኋላ፣ ኑሯቸውን በሎስ አንጀለስ አድርገዋል፡፡) አደጋው በደረሰበት በመስከረም 3/1962ዓ/ም አመሻሹ ላይ መቀመጫውን ሶሪያ-ደማስቆ ያደረገው የኤርትራ ነጻ-አውጪ ድርጅት (ጀብሐ) ኃላፊቱን ወሰደ፡፡ ጠለፋውን ያደረኩት “እኔ ነኝ” አለ፡፡ ከነዚህ “የቻይና ኮሚኒስት ነኝ!” “የአልባኒያ ኮሚኒስትን የሚከተል ከኔ በላይ ላሳር!” “የሩሲያን ኮሚኒዝም ጡት እየመገመገ ያደገ ማን እንደኔ!” ወይም ደግሞ “በመኮሚኒስትነት እኔ የቼኩ ምልምል አሽከር ጋር የሚፎካከር ማነው?” የሚሉት ወገኖች ሁሉ አንድ ናቸው፡፡ ሁሉም የግለሰብን መብት ለመደፍጠጥና የመንጋ (“ተራማጅ ነን ባዮችን”) መዋቅር እንደሸረሪት ድር ለማቆሸሽ የሚተጉ ናቸው፡፡ በጋማል አብደል ናስር ኮትኳችነት የተጀመረውና የዓረቡን ዓለም በኮሚኒዝም ርዕዮት-ዓለም ለማስተሳሰር የጣረው ባአዝ (BAAZ Party) የሶሪያ አውራ ፓርቲ ሆኖ ነበር፡፡ በገለልተኛ ሀገሮች ስራችነቷ ፀንታ ለመቆም የምትፍጨረጨረውን ኢትዮጵያን ኮሚኒስቶቹ አገሮች በጥላቻ ነበር የሚመለከቷት፡፡ ለዚህ ብያኔያን ጥሩ ማሳያ የሚሆነን የጀብሐ 5ተኛ ወታደራዊ ምድብ/ክንፍ አላፊ የነበረውና ይህንን ቃለ-ምልልስ ሲያደርግ የ29ዓመት ወጣት የነበረው ወልዳይ ካሕሳይ ነው፡፡ እስከ 12ተኛ ክፍል ድረስ በአስመራ ኮምቦኒ ትምህርት ቤት ተምሯል፡፡ ከዚያም በትውልድ መንደሩ በደቀሽሐይ-ሐማሴን ለሁለት ዓመታት ያህል አስተምሯል፡፡ በጥቅምት 25/1960ዓ.ም ካርቱም ለሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ እጁን ሰጠ፡፡ ይህም ቃለ-ምልልስ የተደረገለት ካርቱም ሳለ ነበር፡፡ ወልዳይ ስለድርጅቱ እንዲህ አለ፤ “የጀብሐ መሪዎች እኔን የ5ተኛው ወታደራዊ ክፍል አላፊ ያደረጉኝ ወደው አይደለም፡፡ ‘በድርጅቱ ውስጥ አንድም ክርስቲያን ወታደራዊ መሪ የለም!’ ለሚለው የደጋው ኤርትራዊ ቅሬታ ማስተንፈሻ ሲሉ ነው እንጂ፤ በእውነተኛነት አስበውት አይደለም፡፡ እኔ ከምመራው ወታደራዊ ክፍል ውጪ ያሉት አራቱም ክፍሎች አንድም ክርስያቲያን ተዋጊ እንኳን የላቸውም፡፡ ለዚህ ደግሞ በቂ ምክንያት አለው፤ ድርጅቱ የሚሠራው ለአንዳንድ የዓረብ አገሮች ነው፡፡ ተዋጊዎቹም ሆኑ አመራሮቻቸው ስልጠና የሚያገኙት ወደሶሪያ እየሄዱ ነው፡፡ ለሽፍትነት ስልጠና ወደሶሪያ ከሄዱት 300 (ሦስት መቶ) ሰልጣኞች መካከል፣ አንድም ክርስቲያን አልነበረባቸውም፡፡ አምስት አረቢኛ ተናጋሪዎች ብንኖር እንኳን፣ ስማችንን እንድንለውጥ ተደርገናል፤” እያለ ያብራራል፡፡ ወልዳይ ለጀብሐ ርዳታ ስለሚያደርጉትም አገሮች ተጠይቆ ሲያብራራ እንዲህ ብሎ ነበር፤ “ሶሪያና ኢራቅ ወታደሮችን በማሰልጠን በኩል ሲረዱ፣ ሶሪያ በተለይ የጦር መሳሪያም በገፍ ታቀብለናለች፡፡ እንደሚታወቀው፣ ጀብሐት እ.አ.አ በ1961 ጂዳ-ሳዑዲ የተመሠረተ በመሆኑ፣ የሳዑዲ መንግሥትና ሕዝብ በገንዘብ በኩል ይረዳል፡፡ ከጎረቤት አገሮችም መካከል ግብጽ፣ ሱዳን፣ ሶማሊያና ጅቡቲ ሽፍቶቹ በዓረብ አገሮች በሚዘዋወሩበት ጊዜ የሚያገለግላቸውን ፓስፖርት በመስጠትና በልዩ ልዩ መንገዶችም ይረዳሉ፡፡ በተለይም ግብፅ የመሳሪያ እርዳታዋን ነፍጋን አታውቅም፤”በማለት ገልፆ ነበር፡፡ “ቻይናም የወታደሮች ልብስ ሰጥታ፣ ልብሱ ግን ለበረሃው ሊያገለግል ሳይችል ቀርቷል፡፡ በቅርቡ ለከፍተኛ የወታደራዊ ስልጠና ስኮላርሺፕ ሰጥታ-20 ሰዎች ተመርጠው ወደቻይና ለመሄድ ወደሶሪያ እያመሩ መሆናቸውንም” አመልክቶ ነበር፡፡ ወልዳይ እንዲህም ሲል አከለ፣ “በአሁኑ ሰዓት በኤርትራ ውስጥ 65% ክርስቲያኖችና 35% ደግሞ ሙስሊሞች ይገኛሉ፡፡ እስከ 4ተኛ ክፍል ድረስብቻ የነበረውም ትምህርት እስከ ዩኒቨርሲቲ ድረስ አድጓል፡፡ ታዲያ እኔ ለምን ብዬ ይሄንን እውነታ ከካዱ ሰዎች ጋር እሰለፋለሁ?” ሲል ተደምጧል(አዲስ ዘመን፣ ጥቅምት 1/1960ዓ/ም፣ ገጽ-1፣5 ይመልከቱ)፡፡ ማጠቃለያ፤ ከሰሞኑ፣ የበሺር አላሳድ መንግስት ላይ የወታደራዊ ጥቃት ለመክፈት አሜሪካንና ፈረንሳይ ቆርጠው ተነስተዋል፡፡ የባዝ ፓርቲና የአላሳድ ወዳጆች ሩሲያና ቻይናም እየተከላከሉለት ናቸው፡፡ የፀፅታ ምክር ቤትም በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ከሳዳም ሁሴን የተቀበላቸውን የኬሚካል የጦር መሳሪያዎች የአላሳድ መንግስት እንዲያስወግድ ቀን ተቆርጦለታል፡፡ የምዕራባዊያኑ አካሄድ፤ ወድቆ የቆመውን እንደመጎተት ያለ ነው፡፡ ሳዳምንም እንዲሁ ነበር ያደረጉት፡፡ ከ80ኪ.ሜ በላይ የሚወነጨፉትን አልሳሙድ ሚሳይሎቹን እንዲያስወግድ ነገሩትና አስወገደ፡፡ ከዚያም፣ ወረሩት፡፡ ይህ ሶሪያም ላይ እንደሚደገም ቅንጣት ታክል ጥርጠሬ የለኝም፡፡ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያውያን ታሪካዊ ጠላቶች አሳር መከራቸውን ሲበሉ በማየቴ ምንያህል እደለኛነት እንደሚሰማኝ ልሸሽገው አልዳዳም፡፡ ኢትዮጵያና ሰላም ወዳድ ኢትዮጵያውያን በነፃነታቸው ለዘላለም ትኑሩ! ጠላቶቻቸውም ኹሉ በሰፈሩት ቁና ይሠፈሩ!….. Source/WWW.ECARDF.com

No comments:

Post a Comment