Thursday, September 26, 2013

አንድነት ሰላማዊ ሰልፉን ለማካሄድ አራት አደባባዮች በአማራጭነት አቅርቦ እየተነጋገረ ነው

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም በመስቀል አደባባይ ጠርቶት የነበረው ሰላማዊ ሰልፍ የከተማው አስተዳደር በአደባባዩ ዙሪያ ኮንስትራክሽን እየተከናወነ ስለሆነ አደባባዩ ማንኛውንም ሰልፍ ስለማያካሂድ ጃንሜዳ በአማራጭነት በማቅረቡ የአንድነት ሰልፍ በመስቀል አደባባይ ማካሄድ አስቸጋሪ ሁኔታ መፈጠሩን ፓርቲው አስታወቀ። የከተማው አስተዳደር የአዋጁን አንቀጾች ጠቅሶ ፓርቲው በመስቀል አደባባይ ሰልፍ ማካሄድ እንደማይችል በመግለፅና አማራጭ አማራጭ እንዲያቀርብ መጠየቁ፤ ከጃንሜዳ እና ከመስቀል አደባባይ ውጪ ሌሎች አራት አደባባዮች በአማራጭነት አቅርቦ
ከአስተዳደሩ እየተነጋገረ መሆኑን የፓርቲው የብሔራዊ ምክር ቤት ዋና ፀሐፊና የሕዝባዊ ንቅናቄ ግብረ-ኃይሉ ፀሐፊ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ለሰንደቅ ጋዜጣ ተናግረዋል። ፓርቲው መስቀል አደባባይ የተከለከለበት ሂደት አሳማኝና ሞራላዊ ባይሆንም ፓርቲው እራሱ መስቀል አደባባይን ጨምሮ ሌሎች አራት አደባባዮችን በአማራጭነት ለማየት ከአዲስ አበባ አስተዳደር ጋር ለመነጋገር መገደዱን ገልፀዋል። ፓርቲው በአማራጭነት ያቀረባቸው አደባባዮች የኢትዮ-ኩባ ወዳጅነት አደባባይ፣ ቴዎድሮስ አደባባይ፣ አራት ኪሎ እና ስድስት ኪሎ አደባባዮች መሆናቸውን በመጥቀስ ከተቻለ የአዲስ አበባ ስታዲዬምም እየታየ መሆኑን አመልክተዋል። ቀደም ሲል ሰልፉን ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ጽ/ቤት መነሻ የማድረጉን ነገር በመቀየር ከተመረጡ ክፍለ ከተሞች ከተለያዩ ቦታዎች ወደ አደባባዮች ሕዝቡ እንዲሰባሰብ መወሰኑን ገልፀዋል። ፓርቲው በሰልፉ ይሳተፋል ብሎ የገመተው ግማሽ ሚሊዮን ሕዝብ በላይ ከአደባባዮቹ ስፋት ጋር ባይመጣጠንም ሰልፉ በጎዳናዎቹ ላይ ጭምር የሚከናወን መሆኑን አመልክተዋል። አንድነት ፓርቲ ጃንሜዳ ላይ ሰልፉን የማያካሂደው በሁለት ምክንያት መሆኑን አቶ ትዕግስቱ ገልፀዋል። የመጀመሪያው በሰላማዊ ሰልፍ አዋጅ ቁጥር 3/1983 ዓ.ም አንቀፅ 7 ንዑስ ቁጥር 2 መሠረት ሰላማዊ ሰልፍ መካሄድ ያለበት ከጦር ካምፓች ቢያንስ 500 ሜትር ርቀት ላይ ነው። ነገር ግን ጃንሜዳ በመቶ ሜትር ርቀት ላይ ትልቅ የጦር ካምፕ በመኖሩ በቀጥታ አዋጁን መጣስ ነው የሚሆነው። ሁለተኛው ምክንያት ቦታው ሣር የበቀለበት ረግረጋማ ስፍራ በመሆኑ በአጠቃላይ ጃንሜዳ ሰላማዊ ሰልፍ ለማካሄድ ከሕግም ሆነ ከአመቺነት አንፃር ተመራጭ ባለመሆኑ ነው ብለዋል። “ሰልፉ በምንም አይነት አይቀርም” ያሉት አቶ ትዕግስቱ አንድነት ፓርቲ የሕዝቡን መብት በድርድር እየጠየቀ አይደለም ብለዋል። ስርዓቱ ፍፁም አምባገነናዊ ስርዓት በመሆኑ አንድነት የተገኘውን ቀዳዳ ሁሉ ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ በሆነ መንገድ እንደሚያስኬድ ገልፀዋል። “አንድነት ሰላማዊ ትግሉን ከዲፕሎማሲያዊ ድርድር ጋር ይዞ ነው የሚሄደው” ያሉት አቶ ትዕግስቱ፤ በሰልፉ ቦታ ላይ ከመንግስት ጋር መደራደሩ ለመንግስት የመንበርከክ ጉዳይ አይደለም ብለዋል። ለጊዜው የሰልፉ ቦታ ባይለይም ኅብረተሰቡ በሰልፉ ላይ እንዲሳተፍ በሦስት ተሽከርካሪዎች የጎዳና ላይ ቅስቀሳ መደረጉን፣ በቤት ለቤት፣ በማኅበራዊ ድረ ገጽ በሌሎች የመቀስቀሻ መንገዶች ቅሰቀሳ እየተካሄደ መሆኑን ተናግረዋል። እንዲሁም ለንግዱ ማኅበረሰብ በልዩ ሁኔታ ጥሪ መደረጉን ገልፀዋል። በተጨማሪም በከተማዋ ውስጥ የሚገኙ መዋቅሮች ስልጠና ተሰጥቷቸው በእንቅስቃሴ ላይ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ሰላማዊ ሰልፉ የ1997ቱ ሰልፍ የሚያስታውስ ሰልፍ እንደሚሆን ተስፋ መኖሩን አመልክተዋል። በሰልፉ ላይ ለመነሻ ያህል አምስት መቶ ሺህና ከዚያ በላይ ሕዝብ የሚሳተፍ ቢሆንም፤ በመንግስት በኩል ፓርቲው የተቃውሞ ሰልፍ በጠራበት ዕለት በተመሳሳይ በየትምህርት ቤቱ የወላጆች ስብሰባ መጥራቱ አግባብ አለመሆኑንም አቶ ትዕግስቱ ተናግረዋል። የወላጆች ውይይት መስከረም 5 ቀን 2006 ዓ.ም ቀደም ሲል አንድነት ሰልፍ በጠራበት ዕለት ተጠርቶ የነበረ ቢሆንም፤ ባልታወቀ ምክንያት ወደ መስከረም 19 ቀን 2006 መቀየሩ ሆን ተብሎ የፓርቲው ሰልፍ ላይ እንቅፋት ለመፍጠር ነው ብለዋል። ሰልፉ የፍትህና የነፃነት ጥሪ መሆኑን ያስገነዘቡት አቶ ትዕግስቱ የፀረ ሽብር ሕጉ እንዲሰረዝ፣ የኑሮ ውድነቱና ስራ አጥነት እንዲቀረፍ፣ የታሰሩ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ መሪዎች እንዲፈቱ፣ በልማት ስም የዜጎችን መፈናቀልን የሚቃወምና መብቱን የሚጠይቅ ማንኛውም ኅብረተሰብ እንዲካፈል ጥሪ መቅረቡን አመልክተዋል። የሙስሊሙ ማኅበረሰብ ጥያቄ ከፀረ-ሽብር ሕጉ በተለየ ሁኔታ የሚያያዝ በመሆኑ ሕጉ እንዲሰረዝ ፍላጎት ካላቸው ጎን ይቆማሉ የሚል እምነት እንዳለ ጠቅሰዋል። በሰልፉ ላይ መኢአድ ከአንድነት ፓርቲ ባልተናነሰ ሁኔታ በሰልፉ መሳተፉንና 33ቱ ፓርቲዎች ንቁ ተሳትፎ እያደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል። አንድነት ፓርቲ ከተመሠረተ አራት ዓመት ቢሆነውም የቀድሞው ሊቀመንበር ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ እንዲፈቱ 250 ሰዎች የተካፈሉበት ሰልፍ ማድረጉ አይዘነጋም። ባለፉት ሦስት ወራትም በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል ሰልፎችና ሕዝባዊ ውይይት ማድረጉም አይዘነጋም::

No comments:

Post a Comment