Sunday, November 3, 2013

በአቶ መለስ ሞት የውጭ ምንዛሬ እጥረት ተፈጥሮ እንደነበር አይኤም ኤፍ ገለጸ

ጥቅምት ፳፪(ሃያ ሁለት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-አለማቀፉ የገንዘብ ተቋም ባወጣው የ2004-2005 ግምገማ ኢትዮጵያ ድህነትን ለመቅረፍ የምታደርገውን ጥረት አድንቋል። በኢኮኖሚው ረገድ ስኬት እየታየ መሆኑን፣ አገሪቱም የ7 በመቶ እድገት ማስመዝገቡዋን የገለጸው አይ ኤም ኤፍ፣ የዋጋ ግሽበትን ለመቆጣጠር መንግስት የወሰደውን እርምጃንም አድንቋል። የአቶ መለስ ሞት በፈጠረው መደናገጥ ሁሉም የውጭ ምንዛሬ ለመግዛት መገደዱን በዚህም ሳቢያ የተፈጠረው የምንዛሬ እጥረት ተጽኖ መፍጠሩን ገልጿል። የግሉ ዘርፍ ሚና መቀነሱን ያወሳው አይ ኤም ኤፍ ፣ መንግስት በዚህ በኩል ትኩረት እንዲሰጥ ጠይቋል። ከዚህ በፊት ባልተለመዱ መልኩ መንግስት ለሽብር ጥቃት የሚውለውን ገንዘብ እንዲሁም ህገወጥ የገንዘብ ዝውውርን እንዲቆጣጠር ድርጅቱ ጠይቋል። ምንም እንኳ ድርጅቱ ኢትዮጵያ በምን መልኩ ህገወጥ የገንዘብ ዝውውር እንደሚካሄድባት እንዲሁም በየትኛው መልኩ ለሽብርተኞች ጥቅም ላይ የሚውል የገንዘብ ዝውውር እንደሚካሄድባት ባይገልጽም፣ በዚህ ረገድ የሰጠው አስተያየት ኢትዮጵያ ህገወጥ የገንዘብ ዝውውር የሚካሄድባት አገር መሆኑዋና ያመላከተ ሆኗል። አይኤም ኤፍ አብዛኛውን ሪፖርቱን ከመንግስት በሚወስደው መረጃ የሚያወጣ በመሆኑ በኢኮኖሚስቶች የተቻል። ይህን ትችት ግምት ውስጥ ያስገባ በሚመስል መልኩ የኢትዮጵያ መንግስት መረጃዎችን በማሰባሰብ በኩል ጥራት ያለው ስራ እንዲሰራ ፣ ድርጅቱም እገዛ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን ገልጿል። በአገሪቱ ውስጥ ነጋዴዎች ፍትሀዊ በሆነ ሁኔታ እንዲወዳደሩ ሁኔታዎች ሊመቻቹ እንደሚገባም አይኤም ኤፍ መክሯል።

No comments:

Post a Comment