Monday, October 21, 2013

ጥቅምት ፲(አስር)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና

በቂ ጥበቃ ማድረግ ያልቻለ መንግስት ስልጣን ለህዝብ ማስረከብ አለበት” ሲል አንድነት ፓርቲ ገለጸ ጥቅምት ፲(አስር)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ፓርቲው ይህን የገለጸው ጠ/ሚ ሀይለማርያም ደሳለኝ ” በቂ ጥበቃ የለንም በሚል ሰላማዊ ሰልፍን እንደሚከለክሉ” መናገራቸውን ተከትሎ በሰጠው መልስ ነው። ” በቂ ጥበቃ ማድረግ ያልቻለ መንግስት ስልጣኑን ለህዝብ በማስረከብ ይቅርታ ጠይቆ መሄድ እንጅ ከአሁን በኋላ መብታችሁን አታገኟትም ” በማለት መዛት ትዝብት ውስጥ የሚጥል ድርጊት ነው ብሎአል አንድነት በመግለጫው፡፡ አንድነት ” ተገዥነቱን ለህዝቡና ለህግ አድርጎ በአምባገነኖች ዛቻ ሳይበረግግ፤ ዘር፣ ፆታ፣ ሀይማኖት፣ ቀለም ሳይለይ ዜጎች የሚያነሱት ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች
እንዲመለሱ፤ የመንግስት በሐይማኖት ጣልቃ ገብነትም እንዲቆም ትግሉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ያረጋግጣል” ብሎአል። ፓርቲው እንደ ኢትዮጵያ አሉ አንዳንድ የአፍሪካ መሪዎች በአለማቀፍ ፍርድ ቤት ላይ የያዙትን አቋምም ተችቷል። ” የአፍሪካ መሪዎች ተሰብስበው እንግደል፣ እንሰር፣ እንጨፍጭፍ፣ ዘር እናጥፋ፣ ዜጎቻችንን እናሰቃይ ግን መታሰርም መከሰስም የለብንም በሚል የያዙት አቋም አሳፋሪና ተቀባይነት የሌለው ነው፣ የሚለው አንድነት፣ ሕግ እየጣሱ በህግ አለመጠየቅ አይቻልም፡፡ ዘር እያጠፉ ያለመታሰር መብት አይኖርም፡፡ ማንም ሰው ከህግ በላይ የመሆን መብት የለውም፡፡” ሲል አክሏል። የአፍሪካ መሪዎች ተሰብስበው ማለት ያለባቸው አይሲሲ ሊከሰን አይገባም ሳይሆን የዜጎቻቸውን እንባ ማበስ ነው የሚለው አንድነት፣ አሁንም ሆነ ወደፊት በዜጎቻቸው ላይ ግፍና ሰቆቃ የሚፈፅሙ ሁሉ ሳይውል ሳያድር ወደ ፍርድ መቅረብ አለባቸው ብሎ ያምናል ሲል አቋሙን ግልጽ አድርጓል፡፡

No comments:

Post a Comment