Saturday, October 26, 2013

የኢህአዴግ መንግስት መለያ ባህሪያት

ከአቶ አስገደ ገብረስላሴ (የህወሓት መስራች የነበሩ ከመቀሌ) 1. ህግ የማያከብር መንግስት የኢህአዴግ መንግስት የፍትህ የዳኝነትና የፖሊስ አካላት እንዲቋቋሙ አድርጓል፡፡ እነዚህ የፍትህ አካላት አንዳንድ የሚወስዱትን ህገ-ወጥ እርምጃ ሳይ የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ ሳይሆን የኢህአዴግን መንግስት ለሚቃወሙ ግለሰቦች፣ ቡድኖች፣ የፖለቲካ ድርጅቶች በአጠቃላይ የተለየ ሐሳብ የሚያራምዱ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለመጫን የተመሰረቱ ይመስሉኛል፡፡ በማንኛውም ወንጀል የተጠረጠረን ግለሰብ ፖሊስ መጀመርያ ግለሰቡን ..ከኢህአዴግ የፖለቲካ ታማኞች.. አንዱ መሆኑን እና አለመሆኑን ከኢህአዴግ ባለስልጣናት ይሁንታ ካላገኘ የማሰር አቅም አይኖረውም፡፡ የፍትህ አካላትም ክስ የሚመሰረቱበትን የግለሰቡን ማንነት አስቀድመው ከኢህአዴግ የፖለቲካ ታማኞች ውጭ መሆኑን ማረጋገጥ የግድ ይላቸዋል፡፡ ዳኞችም እንግዲህ በአንፃሩ ከኢህአዴግ መንግስት በአመለካከት ያልተለዩ ከሆኑ ወንጀል ቢፈፅምም ተጠርጣሪ ጠያቂ አለበት
ማለት ይከብዳል፡፡ የፖለቲካ ታማኝነቱ ሳይታወቅ የተከሰሰ ..አባል.. እንኳ በችሎት ላይ እያለም ክሱ እንዲሰረዝለት የሚደረግበት አጋጣሚ አለ፡፡ የኢህአዴግ መንግስት ሁሉም ዜጋ በህግ ፊት እኩል ነው እያለ ሲፅፍና ሲናገር እንሰማለን፡፡ ኢህአዴግ ይህንን ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ በአመለካከት ከኔ እስካልተለያየህ ድረስ ማለቱ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ በአስተሳሰብ የተለየ እስካልሆንክ ሰው ብትገድል እንኳ በእርቅ ነፃ መውጣት ትችላለህ፡፡ ስልጣንህን ተገን በማድረግ የህዝብ ንብረትና ገንዘብ ብትዘርፍ ዘመነኛ ተብለህ ልትሸለማለህ ትችል እንደሆነ እንጂ ሙሰኛ አያሰኝህም፡፡ 2.ፀረ ዴሞክራሲያዊ መንግስት የህግ የበላይነት ባልተከበረበት ሀገር ስለዴሞክራሲያዊ መብቶች ማንሳት ተገቢ አይደለም፡፡ ሁለቱን ለብቻቸው ነጥሎ ማየት ሁኔታውን ጎልቶ እንዲታይ ያደርገዋል፡፡ የኢህአዴግ መንግስት ዴሞክራሲ እየገነባ እንደሆነ በየቀኑ ከመቶ ጊዜ በላይ ራሱ በሞኖፖል ይዞ በሚቆጣጠራቸው የተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን እየነገረን ነው፡፡ ..ማን ይናገር የነበረ ማን ያርዳ የቀበረ.. ነው በሚለው ብሂል ሄደን እኔ የምኖርበትን ትግራይ ያለውን ሃቁን ብናይ እንኳን ፍፁም ፀረ-ዴሞክራሲያዊ ተግባራት በላዩ ላይ ተንሰራፍቶበት ይገኛል፡፡ ተቃዋሚዎች መዘጋጃ ቤት ላይ ስብሰባ ህዝቡን ሲጠሩት አስቀድሞ ፖሊሲ በመላክና በማስፈራራት እንዲበተኑ ያደርጋል፡፡ የመንግስት ሰራተኛ ከሆነ በነጋታው ግምገማ እንቀመጥ ተብሎ በተቃዋሚዎች ስብሰባ የተገኘበትን እንደ ምክንያት በመፈለግ እንዲቀጣ ነጋዴ ከሆነ ደግሞ ግብር እንዲጨመርበት ይደረጋል፡፡ በዚህ ምክንያት ሃሳብን በነፃ እንዳይገልፅ ታፍኖ እየኖረ ነው፡፡ ሌላው ይቅርና በየቀኑ ለሚገጥመው ችግር እንኳ አቤት ማለት አይችልም፡፡ በመቀሌ ከተማ ካሉት ችግሮች አንዱ የንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ነው፡፡ በወር ሁለት ጊዜ ብቻ ውሃ የሚያገኝ ቀበሌ አለ፡፡ ህዝቡ ለእንደዚህ አይነት ችግሮች ለባለስልጣናት አቤት ማለት ሳይፈታ ሲቀርም በሰላማዊ ሰልፍ ችግሩን ለመግለፅ አይፈቀድለትም፡፡ በኑሮ ውድነት አብዛኛው የመቀሌ ህዝብ እየተሰቃየ ባለበት ወቅት ህወሓት/ኢህአዴግ እኛ ከሌለን ትግራይ/ኢትዮጵያ ተበታተናለች፤ ህዝቡም ይጠፋል የሚል መዝሙር እንዲዘመር ያደርጋል፡፡ የመንግስት ሰራተኛው፤ ባለስልጣናት የሚፈፅሙትን የሙስና ቅሌት እያዩ ለማጋለጥ አይችሉም፡፡ በወገን፣ በአድልዎ፣ በዘመድ አዝማድ የማይገባቸውን ጥቅም ሊያገኙ እያዩ እንዳላዩ፣ እየሰሙ እንዳልሰሙ ሆነው ቀኑን እየቆጠሩ ይገኛሉ፡፡ የመንግስት ሰራተኛ የህወሓት/ኢህአዴግ አባል ካልሆነ የተለየ አመለካከት አለው በሚልና ይህ አመለካከት ደግሞ ኢትዮጵያን የሚበታትን፣ የትግራይ /ኢትዮጵያ ህዝብ እንዳይኖር ስለሚያደርግ ግለሂስ አድርግ እየተባለ እየተገደደ ይገኛል፡፡ ይህ ሁሉ ታዲያ ፍፁም ፀረ-ዴሞክራሲ ተግባር አይደለም ትላላችሁ? 3. ወጣቱንና ምሁራኑን የመንግስት ጥገኞች ያደረገ መንግስት የኢህአዴግ መንግስት የትምህርት ጥራት ዜሮ እንዲሆን በማድረግ ወጣቱ ተወዳዳሪ የሚያደርገውን እውቀትና ክህሎት እንዳይገበይ በማድረግ በራሱ የሚተማመን፣ እሱነቱን የሚያውቅ፣ ለማንም እጅ የማይነሳ የተማረ የሰው ኃይል እንዳይፈራ በማድረግ የወጣቱና የምሁሩ ክፍል ለኢህአዴግ ፓርቲና መንግስት እንዲያጎበድድ በተጨማሪም ጥገኛ እንዲሆን ያደረገው ያላሰለሰ ጥረት ተሳክቶለታል፡፡ በጣም ብዙ ወጣቶች በኮሌጆችና በዩኒቨርስቲዎች ..እንዲያልፉ.. እና ..ምሩቃን..ን ብቻ በማፍራት ከእውቀት ይልቅ ወረቀትን በመስጠት የኢህአዴግ ድርጅት ..ትእዛዝ.. ተጠባባቂ እንዲሆኑ በማድረግ ጥገኛ ኃይል (ጥገኛ ልማታዊ ሰራዊት) እንዲፈጠር እያደረገ ይገኛል፡፡ የኢህአዴግ መንግስት በተለያየ መንገድ ገንዘብ በመሰብሰብ ብድር የሚሰጠው፣ ወለድ የሚሰበስበው ወጣቱን ..አደራጅቶ.. ስራ የሚሰጠው፣ መንገድ ላይ ቆሞ ታክሲዎች ወደ ሰሜን ሂዱ ደቡብ ሂዱ እያለ ትእዛዝ የሚያስተላልፍ፣ ራሱ በሆነበት በአሁኑ ወቅት ወጣቱና ምሁሩ ከመንግስት ..ረጅም እጅ.. ሊያመልጡ በፍፁም አይችሉም፡፡ ለጊዜውም ቢሆን ለኢህአዴግ ታማኝ ካልሆነ ወጣቱ የሚያገኘው ነገር አይኖርም፡፡ በእውቀቱና በችሎታው የሚተማመን ወጣት እንዳይሆን አስቀድሞ ሰርቶታል፡፡ 4. ርስተ ጉልት ተመልሶ እንዲመጣ ያደረገ መንግስት በፊውዳል ስርዓት ጊዜ ፊውዳሎች መሬትን በራሳቸው ቁጥጥር ስር በማዋል የገበሬ ጉልበት ተጠቅመው የዓመት ምግባቸውን ይሰበስቡ ነበር፡፡ ፊውዳሉ ለአንድ ዓመት የሚሸፍን ምግብ ካገኙ ለዘር ማንዘራቸው ብለው የሚሰበስቡት ሃብት አልነበረም፡፡ የኢህአደግ መንግስት ከፊውዳል ስርዓት የሚለየው ከመሬት በሚያገኘው ጥቅም ብቻ ሳይሆን ለዘር ማንዘሩም ጭምር ብሎ ለብዙ ዓመታት የሚሆን የሚሰበስበው ሃብት መኖሩ ነው፡፡ ..መሬት.. የመንግስትና የህዝብ ነው በማለት መሬት ከገበሬዎች እየነጠቀ ቢፈልግ ለራሱ ህንፃ፣ ቢፈልግ ለሃብታሞች በመስጠት፣ የጥቅም ተካፋይ በመሆን፣ ቢፈልግ ለውጭ ዜጐች በመሸጥ በድሃው ህዝብ ሃብታም መንግስት ሊሆን ችሏል፡፡ 5. በሉዓላዊነት የማይታመን መንግስት ኃ/ስላሴ እና የደርግ መንግስታት በሌላ ችግር ካልሆነ በቀር በሀገርና በሉዓላዊነት ጥያቄ ዙሪያ የሚታሙ አልነበሩም፡፡ የኢህአዴግ መንግስት በዚህ ጉዳይ የማይታመን መንግስት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ኢትዮጵያ በኤርትራ መንግስት ሉአላዊነቷ እንዲደፈርና ባድመን ለሻዕብያ መርቆ የሰጠ መንግስት ነው፡፡ ሻዕብያ ተዳክሞ ለኢትዮጵያ ሰላም አስጊ የማይሆንበት ደረጃ እንዲደርስ አይፈቅድም፡፡ በመሆኑም ኤርትራን የሚያዋስኑ የትግራይና ዐፋር አካባቢዎች በትልቅ ችግር ላይ ወድቀው ይገኛሉ፡፡ 6. የግለሰብ ፈላጭቆራጭ የተረጋገጠበት መንግስት በደርግ ጊዜ መንግስቱ ኃ/ማርያም ብዙ ስልጣን ጠቅልሎ በመያዝ በመዳፉ ስር አስገብቶ ነበር፡፡ ..ከቆራጡ መሪ መንግስቱ ኃ/ማርያም አመራር ጋር ወደፊት..፣ ..ያለጓድ መንግስቱ ኃ/ማርያም ቆራጥ አመራር አብዮቱ ግቡን አይመታም.. ይባል ነበር፡፡ የመንግስቱ ኃ/ማርያም ፎቶ ግራፍ በየመ/ቤቱና አደባባዩ መለጠፍ አንዱ የስርዓቱ መገለጫ ነበር፡፡ አሁን ..ያለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቆራጥ አመራር ኢህአዴግ ሊኖር አይችልም..፣ ..ኢትዮጵያ ትበታተናለች.. እየተባለ እየሰማን ነው፡፡ ኢትዮጵያ ባለሁለት አሃዝ እድገት ለማረጋገጥ የግድ የእርሳቸው አመራር ያስፈልገናል እየተባለ የጠቅላይ ሚኒስቴር ፎቶ ግራፎች በየመ/ቤቱ በየአደባባዩ ይለጠፋል፡፡ በትጥቅ ትግል ጊዜ እንኳን እንደዚህ አይነት የግለሰብ ፈላጭ ቆራጭ አካሄድ ሊኖር ቀርቶ በጊዜው ይታተሙ የነበሩ መጽሐፍት እንኳ ማን እንደፃፋቸው የሚታወቅበት ሁኔታ አልነበረም፡፡ በትጥቅ ትግል ጊዜ በባለስልጣናት መካከል ያለው ግንኙነት እንኳን ብንመለከት የአስተማሪና የተማሪ ዓይነት ነበር፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ የኢህአዴግ ም/ቤት ስብሰባን ሲመሩ የስራ ሪፖርት ሲያቀርቡ፣ ግንኙነቱ የጠያቂና የተጠያቂ ሳይሆን እሳቸው እንዳስተማሪ የተቀረው የም/ቤት አባል እንደተማሪ ቁጭ ብሎ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ሪፖርት ደብተርና እስክርቢቶ ይዞ መገልበጥ ብቻ ነው፡፡ የሚነሳ ጥያቄ ካለም የቃላትና የፊደል ግድፈቶችን በሚመለከት ብቻ ነው፡፡ ለወደፊትማ ደበተሩ ላይ በደንብ ያልገለበጠ፣ የኢህአዴግ ም/ቤት አባል በማብዛት በምርጫ ጊዜ አባል ያልሆነን እንዴት መቆጣጠር እንዳለባቸው ዝርዝር ስልት በመንደፍ የሚቆጣጠሩት ነው የሚመስለኝ፡፡ የአለፈውን ምርጫ እንኳ ብናይ በየአንዳንዱ ቤት የኢህአዴግን አባል በመመደብ አስቀድመው ማንን ለመምረጥ እንደተዘጋጁ እንዲያስታውቅ አድርገዋል፡፡ መምረጥ የፈለጉትን መናገር ያልፈቀዱ ግለሰቦችን እንደ ተቃዋሚ በመፈረጅ የተለያየ የማስፈራራት እርምጃዎች ፈጽመውባቸዋል፡፡ ከምርጫ በኋላም እንደ ጠላት በመፈረጅ ብዙ ግፍ እያደረሰባቸው ይገኛል፡፡ ' ኢህአዴግ ከሁሉም በላይ የሚጠላው የሓሳብ ልዩነት የሚይዝና የሚያራምድ ህዝብ፣ ግለሰብ፣ ቡድን፣ ፖለቲካዊ ድርጅትን፣ ነው፡፡ ልዩነት የሚያስፈራው የተለየ መንግስት ኢህአዴግ ብቻ ነው፡፡ የሚገርመው ጥይትና መድፍ ሰው ይገድላል ቢባል እንኳን የተለየ ሓሳብ የሚገድለው ፍጡር በሌለበት ምድር ሀሳብን እንደ አጥፊ ማሳሪያ መቁጠር ተገቢ አይደለም፡፡ የኢህአዴግን መንግስት የሚገድለው ከጥይት ይልቅ በሀሳብ ልዩነት መሆኑ ነው፡፡ ኢህአዴግ የሃሳብ ልዩነትን ለመፍራት ምክንያታዊ ነው ባይ ነኝ፡፡ ምክንያቱም ግልጽ ሀሳብና መድረክ ከህዝቡ ከከፈተ ህዝቡ ተቆጥሮ የማያልቅ የኢህአደግን ችግር ያነሳል፡፡ የፍትህ እጦት፣ የሃብትና ገንዘብ ዝርፊያ፣ የመሬት ዝርፊያ፣ አድልዎና ጉበኝነት ወዘተ በማንሳትና ኢህአዴግ ከነዚህ ችግሮች ከባህሪው ስለሚያያዙና ሊመልሳቸው ስለማይችል ለግድያው (ለሞቱ) ምክንያት ስለሚሆኑ ነፃ ሀሳብን ማፈን ይመርጣል፡፡ 7. ክህደት በመፈጸም የሚታወቅ መንግስት በትጥቅ ትግል ጊዜ አንድ አንድ ሰዎች የህወሓትን ስብስብ ..የሰዎች ብስብስ ነው ወይስ ሰዎች መስለው መላእክት ናቸው የተሰባሰቡበት.. የሚል ጥርጣሬ ውስጥ እሁ እስከመግባት ደርሰው እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ እንደ ዛሬ አያድርገውና በጊዜው የህዝብን ችግር ለመፍታት ህወሓት መስዋእትነት ለመክፈል ተወዳዳሪ አልነበረውም፡፡ የህወሓት መሪዎች ታጋዩ ለመስዋእትነት እንደተፈጠረና የሱ መስዋእትነት ሰላም፣ ብልጽግና፣ ለሁሉም ዜጋ እኩል የስራ እድል፣ ትምህርት እንደሚያገኝ፣ በህግ ፊት ሁሉም ዜጋ እኩል እንደሚሆን በማስተማርና በማሳመን ፈንጅ እንዲረግጥ አድርገውታል፡፡ የዚያ ዘመን ትውልድ የመስዋእት ትውልድ እንደሆነ ተቀብሎና አምኖ ታሪክ ሰርቶ አልፎዋል፡፡ አንድ ግዳጅ አለና ቅድሚያ መስዋእት ለመክፈል ዝግጁ የሆነ ማን ነው ተብሎ በሚጠየቅበት ጊዜ ልክ ተማሪዎች ክፍል ውስጥ ጥያቄ ሲቀርብላቸው ለመመለስ እኔ እኔ እያሉ እንደሚሽቀዳደሙ ሁሉ ታጋዩ ለአንዴና ለመጨረሻ ህይወቱን ለመክፈል ይሽቀዳደም ነበር፡፡ አሁን ያለው ሁኔታ ይመጣል ብሎ አልገመተማ፡፡ በዚሁ ጊዜ አድልዎ ተፈጸመ ሊባል የሚችለው ለመስዋእትነት ቅድሚያ አልሰጠም በማለት ታጋዩ ለበላይ አለቃው (ጠርናፊው) ሂስ ማቅረብ ነበር፡፡ እንደ ዛሬ የህዝብና የመንግስት ሃብት መውረር የሚባለ ነገር አልነበረም፡፡ ታጋዩ ለመስዋእትነት ..እኔ ልቅደም.. እና ..የለም እኔ ነኝ መቅደም ያለብኝ.. ሲል ግን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ህይወቱን እያጣ መሆኑን ዘንግቶት አልነበረም፡፡ ዳግም ተመልሶ በሱ መስዋእትነት የተገኘውን ድል እንደማያየው አስረግጦ ያውቅ ነበር፡፡ በእኔ መስዋእትነት ጥቂቶች ያውም ፈንጅ እርገጥ ብለው ትእዛዝ በመስጠት የህዝብ መስዋእትነት ከንቱ ነገር ያተርፉበታል የሚል እምነት አልነበረውም፡፡ መስዋእትነቱን ከድተው በስልጣን ይጨማለቃሉ ብሎ አልገመተም ነበር፡፡ ጀግናው አሞራው በደርግ ቁጥጥር ስር ወድቆ ለምንድን ነው በረሃ የሄድከው ሲሉት እንደሚገድሉት እያወቀ ስልጣኑን በህዝብ ለሚመረጥ መንግስት ለማስረከብ ነው አለ፡፡ ለዚህም መስዋእትነት የግድ እንደሚልና ለመስዋእትነት ዝግጁ እንደሆነ በጠላቶቹ ፊት ሆኖ የመለሰው የውስጡን እምነት ደብቆ ጠላት ወይም ደርግ የሚፈልገውን ሃሳብ ተናግሮ ህይወቱን ማትረፍ አቅቶት አልነበረም፡፡ ወይም ደርግ እንደሚረሽነው ዘንግቶትም አይደለም፡፡ ነገር ግን በእሱ መስዋእትነት ህዝቡ ሰላምና ብልጽግና ያገኛል፤ ሁሉም ዜጋ በነፃ የሚኖርባት ኢትዮጵያ ትመጣለች በሚል ቅንነት ነበር፡፡ ህዝብ የመረጠው መንግስት ይመሰረታል፤ ህዝብ የሚቆጣጠረው መንግስት እንጂ መንግስት ህዝብን የሚቆጣጠርበት እና የሚያስፈራራበት አመራር በእኔ መስዋእትነት ይወገዳል የሚል እምነትም ስለነበረው ነው፡፡ በሱ መስዋእትነት፣ በታጋዮች ቤተሰብ እና በጭቁኑ ህዝብ የተመረጠው መንግስት ህዝብ የሚቆጣጠረው ይሆናል ብሎ ነበር፡፡ በተገላቢጦሽ በዚሁ ጊዜ በጠላትነት ተሰልፈው ይዋጉት የነበሩና አሁን ከመስዋእትነት ከተረፉ በስልጣን ላይ ያሉ ታጋዮች የታጋዩን እናት አባትና ልጆች እንደ ጠላት ፈርጀው ያሰቃዩታል የሚል እምነት አልነበረውም፡፡ ፈንጅ እርገጥ እያሉ መስዋእትነት እንድንከፍል ትእዛዝ ይሰጡን የነበሩ ሰዎች በወላጆቻችንና ልጆቻችን ላይ ክህደት ይፈጽማሉ ብሎ ማን ይገምታል፡፡ ግን በተግባር ክህደት ተፈጸመ፡፡ የታጋዩ እናት ..ልጅሽ በረሃ የገባው ተርቦ ነው እንጂ፤ ለኛ ብሎ አልወጣም.. እየተባለች እያለቀሰች ትገኛለች ፡፡ እነኛ ፈንጅ እርገጥ ካንተ መስዋእትነት በስተጀርባ ድል አለ፤ ብልጽግና አለ ይሉት የነበሩ መሪዎች አሁን በስልጣን ኮርቻቸው ላይ ተፈናጠው ፍጹም ጸረ-ዴሞክራሲና ሙሰኞች ሆነው ይገኛሉ፡፡ ተወዳዳሪ የማይገኝላቸው ጉበኞች ፣ የመሬት ሻጮች ፣ አገር ሻጮች ሆነው አርፈውታል፡፡ ክህደት የፈፀመ ልዩ መንግስት የተባለበትም ለዚሁ ነው፡፡ .

No comments:

Post a Comment