Monday, October 21, 2013

አዲስ አበባ ኗሪዎቿን ዉኃ ማጠጣት ተሳናት

አማርኛ ዜናና መግለጫ | የአፍሪካ መዲናና የኢትዮጵያ የልማት ማዕከል መሆኗ የሚነገርላት አዲስ አበባ በከፍተኛ የዉኃ እጦት እየተሰቃየች መሆኗንና ከ35 በመቶ በላይ የሚሆኑ የከተማዋ ነዋሪዎች የሚጠጣ ዉኃ አጥተዉ እንደሚሰቃዩ የወያኔዉ ጠቅላይ ሚኒስቴር በራሱ አንደበት ተናገረ። ኃይለማርያም ደሳለኝ በቅርቡ አዲስ አበባ ዉስጥ የውኃ ቀለም አይቶ የማያውቅ ህዝብ አለ ወይ ተብሎ የቀረበለትን ጥያቄ ሲመልስ በተናገረዉ መሰረት 20 በመቶ የሚሆነው አዲስ አበባ ነዋሪ (ከ600 ሺ ሰዉ በላይ) ዉኃ የሚያገኘዉ በሳምንት ለአምስት ቀናት ብቻ ሲሆን 15 በመቶ የሚሆነዉ የአዲስ አበባ ነዋሪ (ከ450 ሺ ሰዉ በላይ) ደግሞ ዉኃ የሚያገኘዉ በሳምንት አንድ ቀን ብቻ ነዉ።
በብዙ አፍሪካ አገሮች የተካሄደ ጥናታዊ መረጃ እንደሚያመለክተዉ በአብዛኛው የአፍሪካ ዋና ዋና ከተሞች ዉስጥ ያለዉ የውሀ አቅርቦት ከ75 እስከ 99 በመቶ የሚሆነዉን ነዋሪ የዉኃ ፍጆታ እንደሚያረካ የታወቀ ሲሆን የአፍሪካ መዲና እየተባለች በምትጠራዋ አዲስ አበባ ዉስጥ ግን ከእንድ ሚሊዮን በላይ ህዝብ በየቀኑ የዉኃ አገልግሎት አለማግኘቱ ኢትዮጵያ በአመት 11 በመቶ እያደገች ነዉ እየተባለ የሚነገዉን የወያኔ ፕሮፓጋንዳ ጥያቄ ዉስጥ ከትቶታል። አዲስ አበባን በመሰለ አለም አቀፍ ከተማ ዉስጥ ይህንን የመሰለ ከፍተኛ የዉኃ ችግር የሚታይ ከሆነ ከመንግስትም ሆነ ከአለም አቀፉ ህብረተሰብ እይታ ዉጭ የሆኑት የአገሪቱ የገጠር አካባቢዎች ምን ያህል በዉኃ እጥረት እንደሚሰቃዩ መገመት አያዳግትም ሲሉ ይህንን ዜና አጠናቅረዉ የላኩልን የግንቦት ሰባት ድምጽ ዘጋቢዎች ተናግረዋል።

No comments:

Post a Comment