Wednesday, August 28, 2013

በሹመኛ የመጅሊስ አባላትና በመንግስት መካከል አለመግባባት መንገሱ ተሰማ!! (ድምፃችን ይሰማ) ረቡእ ነሐሴ 22/2005

አንዳንድ የወረዳ መጅሊስ ሹመኞች ‹‹መንግስት በሚያዘጋጀው ሰልፍና ስብሰባ ዲናችንን አናሰድብም›› የሚል አቋም ይዘዋል! በመጪው እሁድ ነሀሴ 26 መንግስት በግዳጅ ሊያካሄደው ካሰበው ሰልፍ ጋር በተገናኘ በሹመኛ የመጅሊስ አባላትና በመንግስት መካከል አለመግባባት መፈጠሩ ተሰማ፡፡ አለመግባባቱ የተፈጠረው በመንግስት የቅስቀሳ ስብሰባዎች ላይ በእስልምና ሃይማኖት ላይ ተደጋጋሚ ዘለፋ እና የማንቋሸሽ ተግባራት በመበራከቱና መንግስትም ሁኔታውን ለመግታት ፈቃደኛ ባለመሆኑ እንደሆነ ተነግሯል፡፡ ባለፈው እሁድ የመንግስት ሀላፊዎች ከመጅሊስ የወረዳ ሹመኞች ጋር ባደረጉት ስብሰባ እና ግምገማ የመጅሊሱ ሹመኞች ለመጪው እሁድ የመንግስት ሰልፍ በቂ ቅስቀሳ እያደረጉ እንዳልሆነና ይህ መስተካከል እንዳለበት ያሳሰቡ የመንግስት ሀላፊዎች የሰጡትን ገለጻ ተከትሎ ሹመኞቹ ባደረጉት ንግግር ‹‹በየስብሰባው የሚገኙ የመንግስት ሰዎች ዲናችንን እየተሳደቡብን ሞራላችን እየተነካ ነው›› ያሉ ሲሆን ‹‹በዚህ አቅጣጫ ህብረተሰቡ አግልሎን በዚህ በኩል ደግሞ መንግስት ዲናችንን እያሰደበብን ከመሀል ሆነን እየተጎዳን በመሆኑ መንግስት ዘለፋውን ያስቁምልን›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
‹‹የሕግ ጉዳይን ለሕግ ትተን አክራሪዎችንና ጽንፈኞችን በሰላማዊ ሠልፍ እናወግዛለን›› የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ተወካዮች በስብሰባው የተገኙ የመንግስት ሀላፊዎች በበኩላቸው የመጅሊሱን ሹመኞች በሰጡት አስተያየት ምክንያት የገሰጿቸው ሲሆን ተሳታፊዎች የፈለጉትን አስተያየት የመሰንዘር መብት አላቸውም ብለዋል፡፡ የመጅሊስ ሹመኞቹ ‹‹ካድሬዎቹ እየሰጡ ያሉት ስሜታዊ አስተያየት ሙስሊሙን እየጎዳ ስለሆነ ሊቆም ይገባል›› በሚል መረር ያለ ወቀሳ ቢያቀርቡም የመንግስት ሀላፊዎች ‹‹የሀገር ጉዳይ ስለሆነ ማንም በስሜት ቢናገር አይፈረድበትም›› በሚል ምላሽ ሰንዝረዋል፡፡ ሀላፊዎቹ አክለውም ሰልፉ ወሳኝ ምእራፍ የሚከፈትበት በመሆኑ ሁሉም የመጅሊስ አባል ከነቤተሰቡ መሳተፍ እንዳለበት አስጠንቅቀው ሰልፉ መንግስት ጠላቶቹን የሚለይት በመሆኑ በሰልፉ አለመሳተፍ የሚያስከፍለው ዋጋ ከፍተኛ እንደሆነ በዛቻ መልክ አስረድተዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት በስድስት ኪሎ ስብሰባ ማእከል የአዲስ አበባ ፍትህና ጸጥታ ቢሮ ባዘጋጀው ስብሰባ ተሳታፊ የመንግስት ካድሬዎች የእስልምናን ክብር የሚያራክሱ ዘለፋዎችና የእምነቱን ተከታዮች ክብር የሚያናንቁ ውንጀላዎች መሰንዘራቸውን መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን በርካታ የመጅሊስ ሹመኞችም አንገታቸውን ደፍተው ከስብሰባው ለመውጣት ተገደዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰኞ እለት ከቀኑ አስር ሰአት ላይ የክፍለ ከተማ ሃላፊዎች በዚሁ ሰልፍ ጉዳይ ላይ ከየወረዳው መጅሊስ ሹመኛ አባላት ጋር ተመሳሳይ ይዘት ያለው ስብሰባ ያደረጉ ሲሆን በዚህም ስብሰባ መንግስት አስደንጋጭ ሪፖርት ቀርቦለታል፡፡ በተለይም በየካ፣ በአራዳ፣ አዲስ ከተማና ቦሌ ክፍለ ከተሞች ያሉ አንዳንድ የመጅሊስ አባላት ባቀረቡት ሪፖርት አባላቱ እንኳን ታች ወርደው ህብረተሰቡን ለመቀስቀስ ቀርቶ የራሳቸው የመጅሊስ አባላቶች እንኳ ለመሳተፍ ፈቃደኞች እንዳልሆኑና ‹‹መንግስት በሚያዘጋጀው ሰልፍና ስብሰባ ዲናችንን አናሰድብም›› የሚል ምላሽ እንዳቀረቡ ታውቋል፡፡ የመጅሊስ ሹመኞቹ የሰልፍ ተሳታፊዎችን ቃል እንዲያስገቡበት በመንግስት በተሰጣቸው ፎርም ምን ያህል ሰው እንዳሰፈሩ የመረመሩት የመንግስት ሀላፊዎች አንዳንዱ እራሱንና ቤተሰቦቹን ብቻ ያስመዘገበ መሆኑና ሌሎቹ ደግሞ ባዶ ወረቀት ማስረከባቸው ሀላፊዎቹን በብስጭት እንዲወራጩ አድርጓቸዋል፡፡ ይህ ሁኔታ ያስደነገጣቸው የመንግስት የክፍለ ከተማ አመራሮች ከዚህ በኋላ የየወረዳ ካቢኔ አባላት ከመጅሊስ ሹመኞች ጋር አብረው እየዞሩ ጥሪ እንዲያቀርቡና ጉዳዩም የሞት ሽረት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ይህ ሰልፍ እንዲሳካ እባካችሁ የምትችሉትን ሁሉ አድርጉ›› በሚል በተማጽኖ ጭምር ትእዛዝ ሲሰጡ የነበሩት የመንግስት ሀላፊዎች የመጅሊስ ሹመኞች ጥሪውን ሲያካሄዱ ሃይማኖታዊ አለባበስን ተግባራዊ እንዲደርጉ አዘዋል፡፡ ‹‹ይህ ሰልፍ ከተሳካ ቀጣዩ ስራችን መስጂዶችን ከሙስሊሙ እየነጠቅን ለናንተ ማስረከብ ነው የሚሆነው›› ብለውም ንግግራቸውን አሳርገዋል፡፡ በአዲስ አበባ ደረጃ ቀጣይ ሪፖርት ለመስማት እና ለመገምገም ነገ ሐሙስ ስብሰባ ይኖራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ እሁድ የሚካሄደውን የግዳጅ ሰልፍ የሃይማኖቶች ጉባኤ ነው ያዘጋጀው በሚል መንግስት ቢገልጽም ሰልፉን ሙሉ በሙሉ መዋቅሩን በመጠቀምና ከፍተኛ ፋይናንስ በማፍሰስ እያስተባበረ ያለው መንግስት መሆኑ ይታወቃል፡፡ source http://freedom4ethiopian.wordpress.com/

No comments:

Post a Comment