Monday, November 10, 2014

ሌ/ጄነራል አበባው ታደሰ ወደ ውጭ ሊወጡ ሲሉ ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ በደህንነቶች ተመለሱ


(ከኢየሩሳሌም አርአያ)

ጄ/ል አበባው ታደሰ ወደ ውጭ ለመውጣት ሲሉ ከቦሌ አየር ማረፊያ በደህንነቶች እንዳይወጡ
መደረጋቸውን ታማኝ ምንጮች ጠቁመዋል።ከመከላከያ የጦር አዛዥነታቸው በጄ/ል ሳሞራ የኑስ
እንዲነሱ የተደረጉት ጄ/ል አበባው ከአገር እንዳይወጡ የተደረገበት ምክንያት ግልፅ እንዳልሆነ ምንጮቹ
አያይዘው ገልፀዋል።  በመከላከያ ሰራዊቱ ውስጥ የተለያዩ ጥያቄዎች እንዳሉ በመግለፅ 
ለኢታማጆር ሹሙ ጄ/ል ሳሞራ ከረር ያለ ሪፖርት ያቀረቡት ጄ/ል ሰዓረ፣ ጄ/ል ሞላና ጄ/ል 
አበባው መሆናቸውን የጠቆሙት ምንጮቹ በሳሞራ የተሰጠው መልስ « የትምህክተኞች ጥያቄ ነው፤ 
ችግር የለም..» የሚሉና ጥያቄዎቹን 
የሚያጣጥሉ እንደነበሩ አስታውሰዋል።ሶስቱ ጄኔራሎች በሳሞራ ምላሽ በመበሳጨት ከስልጣናቸው ለማስነሳት በምስጢር ቢመክሩም መረጃው ባልታወቀ 
መንገድ አፈትልኰ ጄ/ል ሳሞራዘንድ በመድረሱ ጄ/ል ሰዓረ ከሰሜን ዕዝ አዛዥነታቸው፣ ጄ/ል ሞላ ከአየር ሃይል እንዲሁም ጄ/ል አበባው ከያዙት
ስልጣን በሳሞራ በአስቸኳይ እንዲነሱ ሲደረግ በተለይጄ/ል አበባው ከ2 ወር በፊት ከመከላከያ እንዲባረሩ መደረጉን ምንጮቹ አስረድተዋል። 
በጄ/ል ሰዓረ ቦታ ጄ/ል ገብራት አየለ ሲተኩ በጄ/ል ሞላ ደግ የአግአዚ ክ/ሰራዊት አዛዥ ጄ/ል አደም መሐመድ መተከታቸውን አስታውቀዋል።
ሁለቱ ጄኔራሎች ዝቅ ባለ ደረጃ ተራ የመምሪያ ሃላፊ ተደርገው መሾማቸውን ምንጮቹ ገልፀዋል። ጄኔራል የመሾምና የመሻር ስልጣኑ የጠ/ሚ/ሩ እንደሆነ
ህገመንግስቱቢደነግግም ነገር ግን የተጠቀሱት ጄኔራሎች የተነሱት በጄ/ል ሳሞራ ትእዛዝ፣ የተተኩትም በሳቸው ውሳኔ እንደሆነና ጠ/ሚ/ር ሃ/ማርያም
ከወራቶች በኋላ እንዲያውቁ ተደርጐ ለተሾሙት ጄኔራሎች የማእረግ እድገት እንዲሰጡ መደረጉን ምንጮቹ አስረድተዋል። ጄ/ል አበባውና ጄ/ል ሰዓረ  
በሙስና ከተዘፈቁ የጦር አዛዦች እንደሚጠቀሱ አክለው ገልፀዋል። ..ይህ በእንዲህ እንዳለ በመከላከያ ከፍተኛ ግመገማ ከሰሞኑ እየተካሄደ ሲሆን ስር
የሰደዱ ቀውሶች እየፈነዱ መሆኑ ታውቋል።

No comments:

Post a Comment