Wednesday, November 19, 2014

ተስፋዬ ገ/አብ (ተስፋዬ ተስፋ ሲቆርጥ /ክፍል 2) – በጋዜጠኛ ሰናይ ገ/መድህን እይታ



ሠናይ ገ/መድህን ይባላል። በኤርትራ ቴሌቪዥን እና ሬድዮ የአማርኛ አገልግሎት ክፍል ውስጥ እ.አ.አ. ከ1998 እስከ 2011 ድረስ ሰርቷል። በዚሁ የረዥም ጊዜ የጋዜጠኝነት ሙያው ነበር ሰናይ ከተስፋዬ ገ/አብ ጋር አስመራ ውስጥ በቅርብ ለመተዋወቅ የበቃው። ዛሬ ኗሪነቱ ሜልበርን፣ አውስትራሊያ የሆነው ኢትዮጵያዊ ኤርትራዊ ጋዜጠኛ ሰናይ ገ/መድህን ለስለስ ብሎ በተጻፈ ቋንቋ አመሻሹ ላይ የሻእብያ ሰላይ መሆኑን በተረጋገጠው “የቢሾፍቱ ልጅ” እንዲህ እያለ ክፍል ሁለትን ይተርክልናል። መልካም ንባብ።
* * * * *
የጋዜጠኛዉ ማስታወሻ እየተተረከ በነበረበት ሰሞን ከአንድ አሁን ስሙን መጥቀስ ከማልችለዉ የኤርትራ የደህንነት ባልደረባ ኮ/ል ጋር አንድ ምሽት ቁጭ አልንና መሎቲ ቢራ እየተጎነጭን ወግ ጀመርን፡፡ ጭዉዉታችን ወደ ጋዜጠኛዉ ማስታወሻ ይዘት ላይ ገባ፡፡ ስለ ሥነፅሁፋዊ ዉበቱ ወይንም ክህሎቱ መነጋገር አላሻንም፡፡ አልቃጣንምም፡፡ አቅማችን ስላይደለ ብቻም ሳይሆን ዋናዉ ሊያነጋግረን የሚገባዉ ጉዳይ ይዘቱ ስለሆነ ፡፡ በተለይ ደህንነቱ ወዳጄ ኢትዮጵያ ዉስጥ በከፍተኛ ልኡክነት የሰራና የፕሬዚዳንት ኢሳያስ አካሂያድና የወቅቱ የኢትዮጵያ ነገሮች የገባዉ በመሆኑ ጭዉዉቱ ይመቸኛል። በኢትዮጵያ ጉዳይ ሚዛናዊ አስተያየት ያለዉ ከመሆኑ ባሻገር የእኛ ፕሮግራሞችን በተመለከተ በትኩረት ከሚከታተሉና አስተያየታቸዉን ከሚለግሱን ነዉ፡፡
“መፅሃፍን አንብበኸዋል እንዴት አገኘኸዉ?” የኔ ጥያቄ ነበር።
“ክላዕ ሀለዉ ለዉ እዩ ዝብል ዘሎ!” “ዝም ብሎ ነዉ የሚቀባጥረዉ” ሲል በንቀት አይነት መለሰልኝ።
የእኔን አስተያየት ቆጥቤ የእሱን ሙሉ ሃሳብ መስማት ስለመረጥኩ ጥያቄየን ቀጠልኩ፡፡ “ማለት .. አላመንከዉም”
“እንዴት ነዉ የሚታመነዉ፡፡ መለስና ሰዬ ሲነጋገሩ፣ የአቦይ ስብሃት የአባዱላን ..እንትና እንዲህ አለዉ እንዲህ አሉት፡፡ በአጠቃላይ ስለ ወያኔ ባለስልጣኖች የቢሮ ጨዋታ የት ሆኖ ሰማና ነዉ ሊነግረን የሚሞክረዉ፡፡ ተፈራ ዋልዋ የትግል አጋሮቹን እነደዚያ ወርዶ ይናገራል ፍፁም፡፡ቢያንስ እኮ እነዚህ ሰዎች የኢትጵያ ከፍተኛ ባለስልጣናት ናቸዉ፡፡ የተስፋየ ጉዋደኞች አይደሉም፡፡ ከመፅሃፉ አብዛኛዉ ታሪክ ያልነበረበት ቦታ እንደነበረ ሆኖ ነዉ የሚያወራዉ። ድርሰት ከሆነ ጥሩ፤ ያለበለዚያ ለኔ አሉባለታ ነዉ። ለኔ የሚሰማኝ ስለ ከፍተኛዎቹ ባለስልጣናት የቢሮ ጨዋታ ከሆነ ቦታ ከተነገረዉ በሁዋላ ያንተ ገጠመኝ አድርገህ ፃፈዉ ያለዉ አካል አለ። አሁን ከወያኔ ጋር ስለተጋጨን ልቅቃሚ የማይታመን ወሬ ሁሉ በእኛ ሚዲያ ማስተጋባቱ ደግሞ በዉነት ለኤርትራ ህዝብ ሀፍረት ዉርደት ነዉ፡፡ ለሱ መተዳደሪያዉ ይሆናል፡፡ ለኛ ግን ዘላቂ ጥቅም የለዉም፡፡ በተስፋየ ወሬ የኢትዮጵያ ህዝብ ህወሓት ከኢህዴን አማራ ከኦሮሞ እርስ በርስ ይጋጫል ተብሎ ከሆነ ትርፉ ትዝብት ነዉ፡፡ ለነገሩ ምን ተስፋየ ብቻ፤ እናንተስ ወሬ እየተነገራችሁ ታማኝ ምነጮች እንደጠቀሱት እያለችሁ ወሬ ታራግቡ የለ” አለና ከት ብሎ ሳቀ፡፡ ( መቼም ኮ/ሉ ወዳጂ ተስፋየ ኤርትራ ከገባ ጀምሮ ከህግደፍ ባለስልጣናትና ከወታደራዊ የስለላ ኮ/ሎች ጋር የተልእኮ ቅንጅት መፍጠሩን ኣያዉቅም አልልም፡፡ እንዲያዉ ያረረ ቆሽቱን በጨዋ ወግ እኔ ላይ መተንፈስ ቢከጅል እንጂ፡፡ እንዲያዉም ግምገማዉ የሱ ብቻ ነዉ ሳልል በኢሳያስ አምባገነንነትና በሁለቱም ህዝቦች ዘላቂ ጥቅም ላይ እጅግ ጎጂ የሆነ አሻራ እያሳረፈ ባለዉ በኢትዮጵያ ፖለቲካ አያያዝ የተበሳጩ በሳል ኤርትራዊያንን አቁዋም ያንፀባርቃል ብየ ገመትኩ ) የሆኖ ሆኖ ስለተግባባንና አባባሉ በጣም ስለተመቸኝ እኔም በሳቅ አጀብኩት፡፡ እረ የልቤንም ስለዘረገፈዉ ነዉ ፡፡ እነ ኮ/ል ፍፁም(ሌኒን)ና ኮ/ል ጠዐመ (መቀለ) እያመጡልንና ታማኝ ምንጮች እንዳሉት እያልን ያራገብናቸዉ አያሌ ወሬዎች ዓይነ ህሊናዬ ላዬ ሲመላለሱ ይታወሰኛል፡፡ በሀፍረት እያሸማቀቁኝ፡፡ አቦ ዋሽቶ ከሚያስዋሽ ይሰዉራችሁ ይባል የለ! ትልቅ ምርቃት ነዉ ወገኖቼ፡፡ ላሁኑ የወሬዎቹን ነገር ትተን ወደ ተስፋየ እናተኩር  
ከኮ/ል ወዳጄ የተሰነዘሩት ትችቶች ዓይነት እየተበራከቱ ይደርሱን ገባ፡፡ በተለይም ከአምቼዎች፡፡ ( ከኢትዮጵያ ወደ ኤርትራ በፈቃዳቸዉ የገቡና እኔን መሰል ከተባረሩ አምቼዎች ) በሳልና ጠንከር ያሉ ትችቶች፡፡ እኔ ላገኛቸዉ ከቻልኩዋቸዉ ማለቴ ነዉ፡፡ ከሁሉም አላልኩም፡፡ እንዴትስ እላለሁ፡፡ ተስፋየ እኔ ብ/ጄል ከማል ገልቹ እና አሁን ስሙን ከማልጠቅሰዉ (ጎበዝ ስማቸዉን የማትጠቅሳቸዉ በዙሳ እንደማትሉኝ አምናለሁ፡፡ የኤርትራን አኗኗር ማን የማያዉቅ አለና !) ወዳጃችን ጋር ሆነን ያደረግነዉ የተሲያት በሁዋላ ጨዋታ ከረር ያለ እንደነበረ አስታዉሳለሁ፡፡ ያስታዉሳሉ፡፡ ቦታዉ ሳቫና ሆቴል፡፡ የጨዋታችን ጉዳይ ያዉ የጋዜጠኛዉ ማስታወሻ መፅሃፍ ነበር፡፡
እንግዲህ እንዲህ ነዉ ፡፡ ተስፋየ የጋዜጠኛዉ ማስታዎሻን አስመራ ሆኖ ገና እየፃፈ እያለ በኦነግ አመራር መካከል ልዩነቱ ይፋ ሆኖ የብ/ጄ ከማልና የአቶ ዳዉድ ኢብሳ ቡድን ጎራ ለዩ፡፡ ቪላና ማዕዳቸዉንም ከፈሉ፡፡ ይህንን ተከትሎ (በወቅቱ በአስመራ ኦነጎች መካከል ዱላ ያማዘዘዉና በኤርታራዊያን ጎረቤቶቻቸዉ ሆስፒታልና ፖሊስ ጣቢያ .. ትዝብት ላይ የጣላቸዉን ነገር አሁን አናነሳዉም ፡፡) የተፈጠረዉን ክፍፍል በተመለከተ እኛ ትንፍሽ እንዳንል ጥብቅ መመሪያ ከህግድፍ ፖለቲካ ቢሮ ሃላፊ ከአቶ የማነ ገብረአብ ተሰጠን ፡፡ የነ ብ/ጄል ከማል ስም እንዳይነሳ ምስላቸዉም በቴሌቭዥን እንዳይታይ ጭምር ፡፡ (በነገራችን ላይ በኦነግ ዜና ጉዳይ ከዚህ በፊትም ከአቶ የማነ ገ/አብ ለእኛ ክፍል ጥብቅ መመሪያ ስለመሰጠቱ እማኝ ነኝ፡፡) ምክንያት የህግደፍ ወዳጅነት ከአቶ ዳዉድ ኢብሳ ቡድን ጋር በመሆኑ፡፡ በእኛ ስር በሚገኘዉ የኦሮሚኛ ክፍል የሚሰሩት የኦነግ አባላት ግን ሁሉም የዳዉድ ቡድን ደጋፊ ስለነበሩ መመሪያዉ ተመችቱዋቸዋል ማለት ይቻላል፡፡ ለጊዜዉም ቢሆን ገበናን ላለማዉጣት፡፡ ለኦነግ አባላቶች በርግጥ ድብቅ አልነበረም፡፡ ለዉጩ እንጂ። ይሁንና ጉዳዩን በቅርብ የተከታተልነዉ ሳንተነፍስ የሩቆቹ ሚዲያዎች ወዲያዉኑ ይፋ አወጡት፡፡ እንደ ሙያተኛ እኛን  አስቆጭቶናል፡፡ያሳዝናልም ፡፡
የአቶ ዳዉድ ቡድን ሁለት ራዲዮ ጣቢያዎች አንዱ በኤርትራ ማስታዎቂያ ስር የሚገኘዉና ሌላኛዉ ከመኖሪያ ቪላቸዉ የሚሰራጭ ሲኖረዉ የቴሌቭዥን ፐሮግራም ደግሞ ከኤርትራ ማስታወቂያ ሚኒስቴር ስቱዲዮ ያሰራጫል፡፡ የዚያኛዉ የእነ ብ/ጄ ከማል ቡድን ግን ከኤርትራ የሚያሰራጨዉና አቁዋሙን የሚገልፅበት ሚዲያ ስለሌለዉና የኤርትራን ማስታወቂያ ሚኒሰቴር ሚዲያ በእኩልነት
እንዳይጠቀምበት ከህግደፍ በመነፈጉ የራሱን ሚዲያ መፈለጉ ግድ ነበር ፡፡ በግሌ በሁኔታዉ እጅግ በማዘኔ የፖለቲካ ልዩነቶቻቸዉን ለነሱ በመተዉና ገለልተኛ በመሆን (ሁሉም ለኔ ወገኖቼ ናቸዉና) በሙያዬ በትንሹ ለነከማል ቡድን ድጋፌን አበርከተኩ፤ ራዲዮ ጣቢያቸዉን በማቋቋሙ ረገድ፡፡ ብሎም ከአስመራዉ የጀርመን ድምፅ ወኪል ከወዳጄ ጎይቶም ቢሆን ጋር በማገናኘትና ድምፃቸዉን
እንዲያሰሙ በማድረግ በመሳሰሉት ሙያነክ ነገሮች፡፡
የነ ብ/ጄ ከማል ቡድን ከህግደፍ ፊት እየተነሳዉ መሄዱ መታወቅ ጀመረ፡፡ ቀለብና ቤት ካለሆነ በቀር እንቅስቃሴያቸዉ ተገደበ፡፡ የብ/ጄ ከማል ቡድን አመራሮች ከአስመራ ዉጭና ከኤርትራም እንዳይወጡ ታገዱ ( የሁዋላ ሁዋላ ደብዛዉን እንዳጠፉት እንደ ኮ/ሌ ታደሰ ሙሉነህ ማለት ነዉ) ብዙም ሳይቆይ ብ/ጄ ከማል ከኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ይዘዋቸዉ የመጡትን 400 አካባቢ ሌ/ኮ እና ሻለቆች የሚገኙባቸዉን ወታደሮቻቸዉን በጠራራ ፀሀይ ተዘረፉ፡፡ ዘራፊዉ ደግሞ ያመኑት ህግደፍ ሆነ ፡፡
ይህ ታሪካዊ የኦነግ ክፍፍል፣ የህግደፍ አድልዎ፣ የአደባባይ ዝርፊያ ሲከናወን እዚያዉ በቅርብ ሆነዉ ለማየትም ለመስማትም ከበቁትና ለኦሮሞ ህዝብ ቅርብ ከሆኑት ወገኖች አንዱ ተስፋየ ገ/አብ ነዉ፡፡ ታዲያ በዚያ በሳቫና ሆቴል ቆይታችን በጋዜጠኛዉ ማስታዎሻ መፅሃፍ ዙሪያ እያነሳን ከጣልናቸዉ ግምገማ ቢጤዎች መሃል ድነገት ብ/ጄ ከማል “የኦሮሞ ህዝብ ወዳጅ ነኝ ትላለህ፣ በኦሮሞ ህዝብ ታሪክ ላይም ትፅፋለህ። ግን በኦነግ ላይ ይሄ ሀሉ ፍፃሜ ሲከናወን እዚሁ ሆነህ አንድም ቀን ሁኔታዉን ለማወቅም ሆነ ብትፅፈዉም ባትፅፈዉም በገለልተኛነት እኛን አላነጋገርክም፡፡ ምክንያቱም እነሱም ለኦሮሞ ህዝብ ነዉ የሚታገሉት እኛም እንዲሁ፡፡ አንተ ግን የነአቶ ዳዉድ ቤተኛ ሆነህ እኛን ከነመፈጠራችን ረሳኽን፡፡ ግን ለምን?” ሲል የሂስ ዶፉን አወረደበት፡፡ ከኦነግ ክፍፍል በሁዋላ ተስፋዬ ለሰላምታም እንኩዋን ቢሆን ከነ ብ/ጄ ከማል እየራቀ መሄዱን ታዝበነዉ ነበር፡፡ ቀጠለ ዶፉ “እንዲያዉም ስለ ኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ስትፅፍ የጠቀስከዉ ሌ/ኮ ገመቹ አያና እኔ ይዣቸዉ ከመጣሁዋቸዉ አንዱ መሆኑን ታዉቃለህ፡፡ መፅሃፍህ ዉስጥ አካተትከዉምክንያቱም ገመቹ ብቸኛዉ ኮ/ል የነ ዳዉድ ቡድንን የወገነ ስለሆነ፡፡ እኔንና ብ/ጄ ሀይሉ ጎንፋን ማነጋገር አልፈለግክም፡፡ ላንተ መፅሃፍየሚበቃ ታሪክ ስለሌለን ይሆን? የእኔነት ጉዳይ አይደለም የሚያናግረኝ፣ ስለ ኦሮሞ ስለ ኢትዮጵያ ስታስብ ገለልተኛ ለምን አትሆንምለምን ትወግናለህ ነዉ ትችቴ፡፡(ከልጅ ልጅ ቢለዩ…) ምክንያቱን ግን አንተም እኔም ሁላችንም እናዉቀዋለን ፡፡” ብ/ጄ ከማል እኔም ሌላኛዉ የዉዉይቱ ማዕድ ታዳሚም እንደወረደ ወረድንበት ነዉ የሚባለዉ፡
ተስፍሽ ለምን ከነ አቶ ዳዉድ ቡድን ጋር እንደተቆራኘ እንዲያብራራልን አልጠበቅነዉም፡፡ ሆድ ሲያዉቅ ዶሮ ማታ እንዲሉ.፡፡ ከመፅሃፉ ዉስጥ እየነቀስን ለሰነዘርንበት ትችትም ምላሽ አልነበረዉም፡፡ በድምድሙ በሌላ ገጠመኝ ሊነሱ የሚችሉ ህፀፆችን የቻልነዉን ያህል ነቀስንለት፡፡ እባክህ እባክህ ሚዛናዊ ለመሆን ሞክር ተማፅኖአችን ነበር ፡፡ ቆዳዉ ወፍራም ቢሆንም ያኔ በበቃኝ ሲዘረር አየነዉ፡፡ ከአፍታ ፀጥታ በሁዋላ ተስፍሽ በደመ ነፍስ በሚመስል ስሜት ሀሳብ አመጣ ፡፡ “ቀጣዩ መፅሃፌ የደራሲዉ ማስታወሻ ነዉ፡፡ በዚህ መፅሃፍ ላይ የነ ብ/ጄ ከማል ጦር ድንበር ተሸግሮ የወጣበትና የዮናታን ዲቢሳ ከኦህዴድ – ኦነግ ታሪክን አካትታለሁ፡
ሊፃፉ ስለሚገባቸዉ የትዉልዳችን የትግል ታሪኮች አንስተን እንወያያለን በአጋጣሚ ሁላችሁም በኢህዴንና ኦህዴድ የትጥቅ ትግል ዘመን ያለፋችሁ ስለሆነ የምታስታዉሱት የታሪክ አላባ ይኖራል” ሲል ግብዣዉን አቀረበ፡፡
በነገራችን ላይ ዮናታን ዲቢሳ ነባር የኢህዴን ታጋይ በሁዋላም የኦህዴድን መስራች ጉባኤ የመራ ኤርትራ ነፃነትዋን ስታዉጅ ከአቶ ሌንጮ ለታ ጋር ኢትዮጵያን ወክለዉ ከመጡት ሁለት የክብር እንግዶች አንዱ ሆኖ የተገኘ አሁን ደግሞ በስደተኛነት የተጠለለ ነዉ፡፡ ኤርትራን ሁለቴ ታይቶባታል ማለት ነዉ፡፡ በክብር እንግድነትና በስደተኝነት፡፡ በህይወቱ ዙሪያ የቴሌቭዥን ቃለመጠይቅና
ዶክመንታሪ ፕሮግራም ሰርቸበታለሁ፡፡ ሁላችንም በታሪክ ዉስጥ ለለዉጥ ሲሉ ለተሰዉ ለታገሉ ለሚታገሉ ለሁሉም አክብሮት ያለን መሆናችንን ገልጠን የሁሉም ህዝቦች ታሪክ ያለአድልዎ ሊወሳ ይገባል በሚል በይሁንታ ተሰነባበትን ፡
ተስፍሽ በቅርቡ እየተገናኘን ገጠመኞቻችሁን አሰባስባለሁ ብሎ ከተለያየን በሁዋላ ብ/ጄል ከማልንም ብ/ጄ ሀይሉ ጎንፋን ሆነ ዮናታንን አላገኘም፡፡ አልፎ አልፎ ከኔ ጋር በአጋጣሚ ኒያላ ሆቴል እንገናኛለን። ከሰላምታ በቀር ቁምነገር ሳናወራ እንለያያለን፡፡ ከዚያ ሰንበትበት ብሎ ከሌ/ኮ አለበል አማረ እና ሌ/ኮ አበበ ገረሱ ጋር በተደጋጋሚ የቢራና ጂን ወግ ላይ አየሁዋቸዉ፡፡ ከሌላ ኤርትራዊ አምቼ ጋርም እንዲሁ፡፡ አንድ ቀን እንደዘበት “የመፅሃፉ ዝግጅት እንዴት ነዉ?” ስል ጠየቅሁት ፡፡ “ጥሩ እየሄደ ነዉ” መለሰልኝ ፡፡
በዚያኑ ሰሞን ደዉሎልኝ ተገናኘን፡፡ እነ ከማልን የፈለገ ነበር የመሰለኝ፡፡ ግን “የጋዜጠኛዉ ማስታወሻን በሲዲ እንድትተርክልኝ እፈልጋለሁ፡፡ ዉጪ አገር በሲዲ ቢሆን ብዙ ተደራሽነት ይኖረዋል ብለዉኛልና እንቅረፀዉ” ሲል ጠየቀኝ፡፡ “ደስ ይለኛል ግን ትከፍለኛለህ፡፡ በነፃ አታስበዉ አልኩት” ቢዘነስ ስለሆነ፡፡ “ከናንተ ቢሮ እኮ በነፃ መዉሰድ እችላለሁ” “ከቻልክ ሞክር ግን አይመስለኝም” አልኩት። “እሺ ስቱዲዮ ፈልግና ንገረኝ” አለና በዚሁ ተለያየን፡፡ የሙዚቃ አቀናባሪና የግሉ ስቱዲዮ ያለዉ ጉዋደኛየን የማነ ኪዳኔን (አብዛኛዉን የሄለን መለስ ሙዚቃ የሰራ ባለሙያ ነዉ) ጠየቅኩት። “እሺ አንተ እንድትጠቀም ስል በመጠነኛ ክፍያ እሰራላችሁዋለሁ” አለና ፕሮግራም አስያዘኝ፡፡ ለተስፋየ ነገርኩት፡፡ አልተስማማዉም፡፡ ምክንያት ደረደረና አያዋጣም አለ፡፡ 5ሺህ ናቅፍ (100 ዶላር) ነበር ለስቱዲዮ የተጠየቀዉ። ቢዝነሱን አንተ ታዉቃለህ አልኩና ለሱ ተዉኩት፡፡
እነሆ የደራሲዉ ማስታወሻ እዚያዉ አስመራ ታትሞ ወጣ ፡፡ ለባለታሪክነት የተመለመሉት እነ ብ/ጄ ከማልና ሌሎች አልተካተቱበትም፡፡ ይሄዉ መፅሃፍ ለትረካ ወደ እኛ ፐሮግራም መምጣቱ ፡ከመፅሃፉ ባለታሪኮች ጋር ያደረግሁት ጭዉዉት ለቀጣይ ወግ ይሁነን፡፡ የዚያ ሰዉ ይበለን!
ሠናይ ገብረመደህን (ጋዜጠኛ)
አዉስትራሊያ፣ ሜልበርን

No comments:

Post a Comment