Thursday, November 20, 2014

እነ ሀብታሙ አያሌው ዋስትና ተከለከሉ

10527316_10204144290838261_6938853363501625654_n

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው አራቱ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች እና በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ሌሎች ስድስት ተከሳሾች ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄ ፍርድ ቤቱ ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡
ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ እና ዳንኤል ሺበሽ በሚገኙበት የክስ መዝገብ የተከሰሱት አስሩም ተከሳሾች ዛሬ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት፣ ተከሳሾቹ ህገ መንግስቱን በመጥቀስ ያቀረቡትን የዋስትና መብት ጥያቄ ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ የጸረ ሽብር አዋጁን በመጥቀስ ዋስትናው እንዳይፈቀድ ያቀረበውን መከራከሪያ በመቀበል የዋስትና ጥያቄውን አልተቀበለውም፡፡ በመሆኑም ተከሳሾች ፍርድ ቤቱ ክሱን መርምሮ በሂደት ውሳኔ እስኪያሳልፍ ድረስ በእስር ላይ ሆነው ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ ወስኗል፡፡
በሌላ በኩል ፍርድ ቤቱ በተከሳሽ ጠበቆች የቀረበውን ማስረጃ አለመሟላት በመመርመር አቃቤ ህግ ለህዳር 17 ቀን 2007 ዓ.ም ማስረጃዎችን አሟልቶ እንዲቀርብ በሚል አጭር ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በዛሬው ዕለት ተከሳሾች ከላይ ሙሉ ነጭ ሸሚዝ ለብሰው ፍርድ ቤት የቀረቡ ሲሆን፣ ነጭ ማድረጋቸውም ‹ሰላማዊ ነን› የሚለውን መልዕክት ለማስተላለፍ በማለም እንደሆነ መረዳት ተችሏል፡፡
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment