Thursday, November 20, 2014

ኢህአዴግ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችን ለማሰር መዘጋጀቱ ታወቀ:የኢህአዴግ አመራሮች መካከል ልዩነት ተፈጥሯል

MINILIK SALSAWI

Image

ገዥው ፓርቲ የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችን ለማሰር ዝግጅት እያደረገ መሆኑን የነገረ ኢትዮጵያ ታማኝ ምንጮች ገለጹ፡፡ ሰሞኑን የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች ባደረጉት ስብሰባ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃልን ወይንስ ሌሎች ከፍተኛ አመራሮችን ማሰር ያዋጣል በሚል ልዩነት እንደተፈጠረ የገለጹት ምንጮቻችን በስተመጨረሻም የኢንጅነር ይልቃል መታሰር ትኩረት የሚስብ በመሆኑ ንቁ እንቅስቃሴ የሚያደርጉ ሌሎች ከፍተኛ አመራሮችን ማሰር አዋጭ ነው የሚለው ቡድን ተደማጭነት እንዳገኘ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

በተመሳሳይ የሰማያዊና ሌሎች ፓርቲዎች አመራሮችን ‹‹ከኢሳት ጋር ግንኙነት ያደርጋሉ›› በሚል በሽብር ስም ለመክሰስ ዝግጅት እየተደረገ እንደሆነ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮችንም ሆነ ሌሎችን ‹‹ከኢሳት ጋር ግንኙነት አላቸው›› በሚል ይከሰሳሉ የተባሉት እስከህዳር ወር መጨረሻ ሊታሰሩ ይችላሉ ሲሉ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል በዚሁ ስብሰባ ኢንጅነር ይልቃል ወይንም ሌሎች ከፍተኛ አመራሮችን በማሰር ከተፈጠረው ልዩነት በተጨማሪ አመራሮችን በተለያዩ ሰበቦች ለማሰር በተዘጋጀውና ‹‹በዚህ መንገድ መሄዱ እስከመቼ ያዋጣናል?›› የሚሉ ጥያቄ በሚያነሱ ከፍተኛ የኢህአዴግ አመራሮች ልዩነት መፈጠሩንም ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከዚህም ባሻገር በሌሎች የፓርቲው አካሄዶች ላይ ልዩነት በመፈጠሩ ፓርቲው ውስጥ አደጋ ተፈጥሯል ያሉት የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች በአቶ አባይ ፀሐዬ የሚመራ ቡድን ‹‹ልዩነታችን ቢያንስ እስከ ምርጫው ድረስ ማቻቻል አለብን›› በሚል በሁለቱ ቡድን መካከል ያለውን ልዩነት ለመፍታት እየጣረ ነው ብለዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ከሌሎች 8 ፓርቲዎች ጋር በመተባበር የአዳር ሰልፍን ጨምሮ የአንድ ወር መርሃ ግብር ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ የሚገኝ ሲሆን የወሩ የመጀመሪያ መርሃ ግብር የሆነው የአደባባይ ስብሰባ ለማድረግ ሲቀሰቅሱ የተገኙ የፓርቲው አራት አመራሮች መታሰራቸው ይታወቃል፡፡

No comments:

Post a Comment