Thursday, January 1, 2015

ፖሊስ የደብረማርቆስ ተማሪዎችን እያፈሰ እያሰረ ነው



ነገረ ኢትዮጵያ // ኢካዴፍ  
Protest in Bahirdar, Ethiopia


ፖሊስ የደብረ ማርቆስ ተማሪዎችን እየደበደበ ነው፡፡ የትናንትናው ተቃውሞ በኢሳትና በሌሎች ሚዲያዎች መተላለፉን ተከትሎ ‹‹ማን ነው ከኢሳትና ከሌሎች ሚዲያዎች ጋር እየተደዋወለ መረጃ የሚሰጠው?›› እንዲሁም ‹‹የተቃዋሚ ፓርቲ አባል ካለ ተናገሩ››  በሚል ተማሪዎቹን አሳልፈው እንዲሰጡ ከፍተኛ ደብደባ እየፈጸመ መሆኑን ከቦታው የደረሰን መረጃ ይጠቁማል፡፡
 ፖሊስ አሁንም ተማሪዎችን እየፈለገ እያሰረ መሆኑም ተገልጾአል።
——————

• ‹‹ኢህአዴግ አይገዛንም!›› ተማሪዎቹ
 ፖሊስ የ‹‹አብዮታዊ ዴሞክራሲ›› ስልጠናን የተቃወሙ የደብረማርቆስ የመለስተኛ ሁለተኛ እና የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ (መሰናዶ) ተማሪዎችን እያፈሰ እያሰረ እንደሚገኝ የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገለጹ፡፡ ተማሪዎቹ በትናንትናው ዕለት ኢህአዴግን የሚተቹ አስተያየቶችንና ጥያቄዎችን በማንሳታቸው ይሰለጥኑበት ከነበረው ሰፊ አዳራሽ ወጥተው 20፣ 20 ሆነው በጠባብ ክፍል እንዲሰለጥኑ ከመደረጉም ባሻገር ጥያቄ የሚያነሱት ላይ ማስፈራሪያ እንደደረሰባቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
ዛሬ ጠዋት ጥያቄ ያነሳሉ የተባሉት ተማሪዎች ስልጠና ወደሚሰጡባቸው ትምህርት ቤቶች ግቢ እንዳይገቡ ከመደረጉም ባሻገር የድብዛ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ስልጠናውን መቃወማቸውን ተከትሎ ፖሊስ እርምጃ እየወሰደ መሆኑን የሰሙ የተክለሀይማኖት መልስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች እርምጃውን በመቃወም ለድብዛ ተማሪዎች ድጋፍ መስጠታቸው ተገልጾአል፡፡
የሁለቱም ትምህርት ቤት ተማሪዎች በጋር በመሆን ከተማው አደባባይ ላይ በመውጣት ‹‹አህአዴግ አይገዛንም፣ ኢህአዴግ ሌባ፣…›› የመሳሰሉ መፈክሮችን በማሰማት ተቃውሟቸውን መግለጻቸውን ተከትሎም ፖሊስ ተማሪዎቹን እያፈሰ ወዳልታወቀ ቦታ መውሰዱ ተሰምቷል፡፡ ከዚህም ባሻገር ጥያቄ የሚጠይቁና ፖሊስ ተቃውሞውን አደራጅተዋል ብሎ የሚጠረጥራቸውን ተማሪዎች እየፈለገ እያሰረ መሆኑን ተማሪዎቹ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
በምስራቅ ጎጃም ዞን በ17ቱም ወረዳዎች የሚገኙ ተማሪዎች ስልጠናውን ካልወሰዱ ከትምህርት ቤት እንደሚባረሩና ፈተና ላይ እንደማይቀመጡ ማስጠንቀቂያ ቢሰጣቸውም ስልጠናውን መቃወማቸውን ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment